ተድባበ ማርያም ገዳም - አትሮንስ ሚዲያ - Atrons Media

አትሮንስ ሚዲያ - Atrons Media

ስብኩ ወንጌለ ለኩሉ ፍጥረት ማቴ 16፤15


በቅርብ የተጻፉ

Post Top Ad

Monday, May 18, 2020

ተድባበ ማርያም ገዳም

የርእሰ አድባራት ወገዳማት ተድባበ ማርያም ቤተክርስቲያን አጭር ታሪክ
መግቢያ


ከክርስቶስ ልደት በፊት982ዓ.ዓ 2990 ዓመት እድሜ አስቆጥራለች፡፡ ከአክሱም ጺዮን ገዳም ቀጥሎ ጥንታዊ የሚባለው የተድባበ ማርያም ገዳም በኢትዮጵያ መስዋተ ኦሪት ከተሰዋባቸው 4 ጥንታዊ አብያተ ክርስቲያናት አንደኛዋ! ቅዱስ ሉቃስ እንደሳላት የሚነገርላት ጸደንያ የቅድስት ድንግል ማርያም ስዕል መገኛ! የአማራ ህዝብ የታሪክ እና የቅርስ እምብርት የሆነችው አማራ ሳይንት (ቤተ-አማራ) በ1270 አጼ ይኩኖአምላክ የአማርኛን ቋንቋ ብሄራዊ ቋንቋ እንዲሆን አውጀውበታል።
ርእሰ አድባራት ወገዳማት ተድባበ ማርያም ገዳም በደቡብ ወሎ ዞን አማራ ሳይንት ወረዳ ከዞኑ ርዕሰ ከተማ ደሴ 228 ኪ.ሜ ርቀት ላይ ትገኛለች፡፡
ወደ ቤተ ክርስቲያኗ ከወረዳው ዋና ከተማ አጅባር 25 ኪ.ሜ በተሸከርካሪና ቀሪው 3 ኪ.ሜ በእግር ያስኬዳል፡፡
ቤተ ክርስቲያኗ የምትገኝበት አምባ 11፡06፡87 ከምድር ወገብ ሰሜን እና 30.45.2 ምስራቅ ጂ.ፒ.ኤስ ከባህር ጠለል 8458 ጫማ ከፍታ ላይ ይገኛል፡፡ አምባው ዙሪያውን በጥርብ አለት ገደል የታጠረ ሆኖ 12 የተፈጥሮ መግቢያና መውጫ በሮች ብቻ ሲኖሩት አምባው ገዥ መሬት ላይ የሚገኝ በመሆኑና የአባይና የበሽሎ ገባር ወንዞች ጉንዳና ገዳማይ በግራና በቀኝ ከምስራቅ ወደ ምእራብ ስለሚፈሱ ከፍተኛ ውበትን አጎናጽፈውታል፡፡
1/ ስርወ መሰረት
ርእሰ አድባራት ወገዳማት ተድባበ ማርያም ቤተ ክርስቲያን በኢትዮጵያ መስዋተ ኦሪት ከተሰዋባቸው አራት ጥንታዊ አብያተ ክርስቲያናት ማለትም አክሱም ጽዮን፣ ተድባብጽዮን፣ መርጦ ለማርያም እና ጣና ቂርቆስ መካከል አንዷ እንደሆነችና በአመሰራረት ቅደም ተከተልም ከአክሱም ጽዮን ቀጥሎ በሁለተኛነት የምትገኝ ጥንታዊና ብቸኛ ባለታሪክ ደብር እንደሆነች መረጃወች ያስረዳሉ፡፡
ታቦቷ በ10ኛው መቶ ክፍለ ዘመን ቅድመ ልደተ ክርስቶስ ማለትም በ982 ዓ.ዓ ከእስራኤል ወጥታ አሁን ካለችበት ቦታ ተመስርታለች፡፡
የተመሰረተችውም ከቀዳማዊ ሚኒሊክ ጋር ከእስራኤል ወደ ኢትዮጵያ ህገ ኦሪትን ለማስፋፋት ከመጡት ነገደ እስራኤላዊያን መካከል አንዱ በሆነው በሊቀ ካህን አዛርያስ መሆኑን የቤተ ክርስቲያኗ ታሪክ ያስረዳል፡፡ የመጀመሪያ መጠሪያዋም ተድባበ ጽዮን ይባል ነበር፡፡
ተድባበ የሚለው ቃል ከግእዝ የተወረሰ ሲሆን ትርጓሜውም ድባብ ወይም ጫፍ ማለት እንደሆነ ሊቃውንቱ ይናገራሉ፡፡
በክብረ ነገስት መጽሀፍ እንደተገለጸው አዛርያስ ሳዶቅ የተባለው እስራኤላዊ ሊቀ ካህን ልጅ ሲሆን ከቀዳማዊ ሚኒሊክ ጋር ወደ ኢትዮጵያ የመጡ ነገደ እስራኤላዊያንን እንድመራ በንጉስ ሰለሞን ታዞ የመጣ እና ህገ ኦሪትን በኢትዮጵያ ከመሰረቱትና ካስፋፉት ካህናት አንዱ ነው፡፡
እንደ ክብረነገስት ገለጻ ከሆነ ከኦሪት ጀምሮ እስከ ሀድስ የክርስትና እምነትን በኢትዮጵያ የመሰረቱና ያስፋፉ ዋና ዋና ካህናት /አቡነ ተክለሃይማኖትን ጨምሮ የሊቀ ካህን አዛርያስ ዘሮች ናቸው፡፡
ወደ ኢትዮጵያ ከሚኒሊክ ጋር የመጡ ነገደ እስራኤላዊያን ካህናት ህገ ኦሪት ርእሰ ርኡሳን እና የጣና ቂርቆስ ሊቀ ካህናት የሚል ማእረግን የሚመሩ አራት መናብርትን ይዘው የመጡ ሲሆን እነሱም ከላይ እንደተገለጸው የአክሱም ንቡረ እድ፣ የተድባበ ጽዮን ፓትርያርክ፣ የመርጦለ ጽዮን የተሰጣቸው ናቸው፡፡
የሰለሞን ስርወ መንግስት በኢትዮጵያ ከተመሰረተበት ወቅት ከቀዳማዊ ሚኒሊክ ዘመነ መንግስት ከ982 ዓ.ዓ ጀምሮ እስከ ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ድረስ የነበሩ ነገስታት በሚነግሱበት ጊዜ የሲመቱ ስርአት የሚፈጸመው በእነዚህ 4 መናብርት ጸሎትና ቡራኬ እየተሰጠ ሲሆን ስነስርአቱም የአክሱም ንቡረ እድ ለነጋሲው ዘውድ በመድፋት፣ የተድባበ ጽዮን ፓትርያርክ ሰይፍ በማስታጠቅ፣ የመርጦለ ጽዮን ርእሰ ርኡሳን ልብሰ መንግስት በማጎናጸፍ እንድሁም የጣና ቂርቆስ ሊቀ ካህን ቅብዐ መንግስት በመቀባት ፣ በትረ መንግስት በማስጨበጥ እንደሆነ በፍትሀ ነገስት ተደንግጎ ይገኛል፡፡
ተድባበ ማርያም ደብር በምትገኝበት አምባ ዙሪያ ያሉ ቀበሌወች ቢታንያ፣ ደብረ ዘይት፣ ኮሬብ፣ ደብረ ሲና፣ ቅድስ፣ ኬብሮን፣ ኢያሪኮ፣ ኢየሩሳሌም፣ የጌላት፣ ደብረ ታቦር፣ ደብረ ፋጌህ፣ ደብረ ፍራህ፣ ጎሎጎታ፣ ፣ ፍልስጤም፣ ሊባኖስ፣አርሞኒየም፣ እና ደማስቆ ተብለው የሚጠሩ ናቸው፡፡ እነዚህ ቀበሌውች ይህን ስያሜ ያገኙት ከተድባበ ማርያም ምስረታ ጋር በተያያዘ ለ12ቱ ነገደ እስራኤላዊያን መታሰቢያ ተብሎ እንደሆነ እና የነዚህ የቦታወች ስያሜ በአካባቢው መኖሩ በወቅቱ ቤተ ክርስቲያኗ መስዋእተ ኦሪት እንደተሰዋባት የሚያመላክት መሆኑን የቤተ ክርስቲያኗ ሊቃውንት ይናገራሉ፡፡
2/ የቤተ ክርስቲያኗ ህንጻ አመሰራረት ታሪክ እና የኪነህንጻ ጥበብ
የርእሰ አድባራት ወገዳማት ተድባበ ማርያም ቤተ ክርስቲያን ህንጻ በ982 ዓ.ዓ እንደታነጸ የቤተ ክርስቲኗ ታሪክ ያስረዳል፡፡ ከዚያን ጊዜ ጀምሮ አሁን እስካለንበት ዘመን ባሉት 3000 ዓመታት ውስጥ የገዳሙ ህንጻ ለ9 ጊዜያት ፈርሶ የተሰራና ለበርካታ ጊዜያትም ጥገናና እድሳት የተደረገለት መሆኑን የገዳሙ አባቶች በጽሁፍ በተደገፈ መረጃ ያስረዳሉ፡፡
ይህም ከልደት ወድህ ብቻ በአብርሀ ወአጽብሃ /ኢዛና/ ዘመነ መንግስት በ340 ዓ.ም ፣ በ897 ዓ.ም ንጉስ አንበሳ ውድም ፣ በአጼ ባካፋ ዘመነ መንግስት፣ በአጼ እያሱ ዘመነ መንግስት እና በአጼ ገላው ደወስ ዘመነ መንግስት በ1550ዎቹ ፈርሶ የተሰራ ሲሆን አሁን ያለው ግብረ ህንጻ በንጉስ ሚካኤል በ1907 ዓ.ም እንደተሰራ መረጃወች ያስረዳሉ፡፡
በቤተ ክርስቲያኗ ውስጥ የሚገኙ ተንቀሳቃሽ ቅርሶች
የርእሰ አድባራት ወገዳማት ተድባበ ማርያም ቤተ ክርስቲያን በርካታ ታሪካዊ፣ ሃይማኖታዊና ባህላዊ ቅርሶች ይገኙበታል፡፡ ከነዚህ ቅርሶች መካከል፣ አንዳንዶቹ በተቀረው የሀገሪቱ ክፍል ይቅርና በሌላው ዓለምም በጣም ውሱን የሆኑ እጅግ ጥንታዊና ታሪካዊ ናቸው፡፡ እነዚህንም በሚከተለው መልኩ ከፋፍሎ መመልከት ይቻላል፡፡
ሀ/ የብራና መጽሐፍት፡-
በቤተ ክርስቲያኗ በርካታ ጥንተዊ የብራና መጽሐፍት ያሉ ሲሆን እነዚህም ከፊሎቹ በጥንታዊ የአክሱም ዘመነ መንግስት የተጻፉ ሲሆን ሌሎቹ ደግሞ በመካከለኛው ዘመን የተጻፉ ናቸው፡፡
ከነዚህ መጽሀፍት መካከል ገድለ አዳም፣በአረበኛና በግእዝ ቋንቋወች የተጻፈ ወንጌል፣በአረማይክ ቋንቋ የተጻፈ የገበታ ቅዳሴ ና ሌሎችም ውድ መጽሀፍት ይገኛሉ፡፡ከዚህም በተጨማሪ በአንዳንዶቹ መጽሀፍት ገበታ ላይ የብርና የወርቅ ፈርጥ ይገኝባቸዋል፡፡
ለ/ ስዕለ አድህኖ፡- የቤተ ክርስቲያኗ የመቅደሱ
ግድግዳ በሙሉ በስዕል የተሸፈነ ሲሆን ስዕላቱ ከፍጥረት አስከ ትንሳኤ ያለውን የመጽኃፍ ቅዱስ ታሪክ የሚያስረዱ እንድሁም በየዘመኑ የነገሱ ነገስታትን ታሪክና ነገረ ሃይማኖትን የያዙ ናቸው፡፡
የስዕሎቹ ንድፍ የቀለም አጣጣልና አቀማመጥ ጥንታዊ የቤተ ክርስቲያን የስዕል አሳሳል ስልትን የተከተሉ ናቸው፡፡በተጨማሪም በቤተ ክርስቲያኗ በርካታ ጥንተዊ የገበታ ሥዕላትና የብራና ሥዕላት ይገኛሉ፡፡
ከነዚህም መካከል ፡-
 የኢየሱስ ክርስቶስን ታሪክ ከህማማቱ እስከ ትንሳኤው የሚያሳይ የብራና የሉህ ሰዕላት፣
 ቅዱስ ሉቃስ እንደሳላት የሚነገርላት ጸደንያ የቅድስት ድንግል ማርያም ስዕል
 ሀፈ ድንግል ስዕለ አድህኖ ዋናዋናወቹ ሲሆኑ ቅዱስ ሉቃስ እንደሳላቸው የሚነገርላቸው ስእላት በአጼ ዳዊት ዘመነ መንግስት ከግማደ መስቀሉና አጽመ ቅዱሳን ጋር ከግብጽ ወደ ኢትዮጵያ እንደገቡ አማርኛ የቤተ ክህነት መዝገበ ቃላት ሀብት በሚለው መጽኀፍ ላይ /ገጽ 115 ተጽፎ ይገኛል፡፡/
ሐ/ መስቀል፡-
በቤተ ክርስቲያኗ በርካታ ጥንተዊ የመጾርና የእጅ መስቀሎች ይገኛሉ፡፡ከነዚህም መካከል፡-
 የመጀመሪያው የኢትዮጵያ ጳጳስ አባ ሰለማ ከሳቴ ብርሀን የቀደሱበት የእጅ መስቀል፣
 መጥምቀ መለኮት ዮሐንስ ወንጌል የሰበከበት ንዋ በግዑ መስቀል፣
 የእጨጌ ዮሐንስ በትረ ሆሳዕና የእጅ መስቀል፣
 የአቡነ አኖሪወስ የእጅ መስቀል፣
 የአቡነ ቄርሎስ የእጅ መስቀል እና ሌሎች ከብር፣ከወርቅና ነሀስ የተሰሩ የተለያዩ ጥንታዊ መስቀሎች ይገኛሉ፡፡
መ/ አውድ
በቤተ ክርስቲያኗ በርካታ ጥንተዊ አውዶች ይገኛሉ፡፡ከነዚህ መካከል ከግብጽ ፓትርያርክ በስጦታ እንደመጡ የሚነገርላቸውና በላያቸው ላይ በአረበኛ የተጻፈባቸው ጥንታዊ አውዶች ይገኛሉ፡፡
ሠ/ አልባሳት
በቤተ ክርስቲያኗ በርካታ ጥንታዊ የነገስታት አልባሳት ይገኛሉ፡፡ለአብነትም የሚከተሉትን መጥቀስ ይቻላል፡፡
 የወርቅ ዝምዝም ያለባቸው የሙካሽ ሥራ አልባሳተ ተክህኖ፣
 የወርቅ ፈርጥ ያለባቸው ካባ ላንቃ ለምድና ከለሜዳ፣
 የአጼ ምኒልክና የአጼ ዮሐንስ ልብሰ መንግስት፣
 የንግስት ዘውድቱ ልብሰ መንግስት ፣
 የወርቅ ፈርጥና መርገፍ ያለባቸው ድባብና ጥላወች፣
 ከወርቅና አልማዝ የተሰራ ንጉስ ሚካኤል ያበረከቱት ዘውድ እና ሌሎችም ከብርና ወርቅ የተሰሩ በርካታ ጥንታዊ አክሊሎችና ዘውዶች እንድሁም የክብር አልባሳት ይገኛሉ፡፡
ረ/ የጦር መሳሪያ
. አጼ ሰርጸ ድንግል ከይፋት ሱልጣኖች ማፍድ ላይ እንደማረኩት የሚነገርለት የነሀስ ነጋሪት፣
. የፖርቹጋል ወታደሮች ይዘውት የመጡት እና አጼ ገላውድወስ የተዋጉበት ሳበው ጠመነጃ፣
. የወርቅ ጣፋና ሙጣ ያለባቸው ጋሻዎች ይገኛሉ፡፡
ሰ/ አጽመ ቅዱሳን
 የቀዳማዊ ቴወድሮስ አጽም፣
 የይስሐቅ አጽም፣
 የአጼ ገላውዴወስ አጽም፣
 ከ1551-1555 የነገሰው የአጼ ሚናስ አጽም፣
 የአጼ እስክንድር አጽም፣
 የሸዋና የጎንደር ነገስታት አባት ጸሀፌ ላህም ብስራተ ሚካኤል አጽም፣
 የእጨጌ አባ ዮሐንስ አጽም፣
 የቴጌ ሮማነወርቅ አጽም ዋናዋናዎቹ ናቸው፡፡
ሸ/ሌሎች አስደናቂ ቅርሶች
 ዘይቄድስ ኩሎ ተብሎ የተነገረለት ከአባ አትናቴዎስ ሊቀ ጳጳስ ዘእስክድርያ ከሳቴ ብርሃን አቡነ ሰላማ ቅባ ሜሮን፣ንጉሥ ሄሮድስ ካስፈጃቸው ህጻናት መካከል የአምስቱ ህጻናት አጽም፣
ስዕርተ ሀና/የቅድስት ማርያም እናት የቅድስት ሃና ጸጉር እጅግ ጥንታዊና በስነ ጥበባዊ ይዘቱ በተለየ የሸክላ ገንቦ ውስጥ ይገኛል፣
 ከአኅመድ ግራኝ አጼ ገላውዴዎስ የማረኩት ቃጭል፣
 መንበረ ዳዊት፣
 በ1329ዓ.ም እንደተሰራ የሚገመተው 18 ነገስታት የነገሱበት ግዙፍ ጎዶ ድንኳን እና በዚህ አጭር ጽሁፍ ተዘርዝረው የማያልቁ ሌሎች ጥንታዊና የታሪክ አሻራ የሆኑ ቅርሶች ተከማችተው ይገኛሉ፡፡
ቤተ ክርስቲያኗ የጥንቱ የኢትዮጵያ ቤተክርስቲያን ስርአት ተጠብቆ ያለባት፣ በ365ቱም ቀናት ስርዓተ ቅዳሴ ሳይጓደል የሚፈጸምባት፣ሰዓታት የሚቆምባት፣ስብሀተ ነግህ በየቀኑ የሚከናወንባት ጥንታዊ ቤተክርስቲያን ናት፡፡አሁንም የጥንቱን ስርዓት ለማስቀጠል በርካታ ተማሪዎች የሚማሩባትና በየደረጃው ያለው የቤተ ክህነት ትምህርት/የአብነት ትምህርት/ የሚሰጥባት ናት፡፡
የቤተ ክርስቲያኗ ዓመታዊ ክብረ በዓል የቅድስት ድንግል ማርያምን የልደት ቀን ምክንየት በማድረግ ግንቦት 1 ቀን ፣የአጼገላውድዎስ የልደት ቀንና ከግራኝ አህመድ ጋር ባካሄደው ጦርነት ድል በማድረጉ ምክንየት ግንቦት 2 ቀን በየዓመቱ በደማቅ ሁኔታ በርካታ እንግዶች በሚገኙበት ይከበራል፡፡
የተደበቀው የአምሐራ ሳይንት፣የኢትዮጵያ እንድሁም የዓለም ታሪክ ይህንን ይመስላል።
የኢትዮጵያንም ገናናነት ማስመስከሪያ የታሪክ ጎተራ ነው።

No comments:

Post a Comment

Post Bottom Ad

Pages