ስንክሳር_ዘወርኀ_ሚያዝያ 9 - አትሮንስ ሚዲያ - Atrons Media

አትሮንስ ሚዲያ - Atrons Media

ስብኩ ወንጌለ ለኩሉ ፍጥረት ማቴ 16፤15


በቅርብ የተጻፉ

Post Top Ad

Thursday, April 20, 2023

ስንክሳር_ዘወርኀ_ሚያዝያ 9

 አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም

ሚያዝያ ዘጠኝ በዚህች ቀን ታላቁ ጻድቅ አቡነ_እስትንፋሰ_ክርስቶስ እረፍታቸው ነው፣ የከበረ ቀሲስ_ዘሲማስ አረፈ፣ በእስክንድርያ ሊቀ ጳጳሳት በአባ_ስንትዩ እጅ ታላቅ ምልክት ታየ።


ሚያዝያ ዘጠኝ በዚህች ቀን ታላቁ ጻድቅ አቡነ እስትንፋሰ ክርስቶስ እረፍታቸው ነው። አቡነ እስትንፋሰ ክርስቶስ አባታቸው መልአከ ምክሩ እናቱ ወለተ ማርያም ይባላሉ፡፡ የተወለዱበት ልዩ ቦታው ወሎ ክፍለ ሀገር ዳውንት ነው፡፡ በተወለዱ ዕለት ተነሥተው በእግራቸው ቆመው ሦስት ጊዜ ስብሐት ለአብ ስብሐት ለወልድ ስብሐት ለመንፈስ ቅዱስ ብለው ፈጣሪያቸውን አመስግነዋል፡፡ የስማቸው ትርጓሜ የአብ የወልድ የመንፈስ ቅዱስ እስትንፋስ አንድም የክርስቶስ እስትንፋስ ማለት ነው፡፡ ቅዱስ ሚካኤል እየጠበቃቸውና በመንገዳቸው ሁሉ እየመራቸው ነው ያደጉት፡፡ መንፈስ ቅዱስ ልቡናቸውን ብሩህ አድርጎላቸው በ5 ዓመታቸው የቅዱሳት መጻሕፍት ቃላትን፣ ብሉያትንና ሐዲሳትን፣ ድርሳናትንም ጠንቅቀው ዐውቀዋል፡፡
በተወለዱ በ14 ዓመታቸው ወደ አቡነ ኢየሱስ ሞዐ ደብረ ሐይቅ ገዳም ሄደው ከባሕር ዳር ቆመው የሙሴን ጸሎት ወደ እግዚአብሔር በጸለዩ ጊዜ የታዘዘ መልአክ መጥቶ ባሕሩን አሻግሯቸው ወደ ቤተ ክርስቲያን ገብተዋል፡፡ ለ3 ዓመታት ያህል በኃይቅ ገዳም ለመነኮሳት እንጨት በመልቀምና ውሃን በመቅዳት ለአባቶች መነኮሳት ምግብ የሚሆናቸው ዓሣ ከባህር ውስጥ በማውጣት አገልግለዋል፡፡
አባታችን እስትንፋሰ ክርስቶስ 40 መዓልትና 40 ሌሊት ከጾሙ በኋላ ምንም እህል ሳይቀምሱ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አስቀድሞ ለሙሴ በደብረ ሲና እንደሰጠው ለአባታችንም ወደ እርሳቸው መጥቶ ዓሥሩን ቃላተ ኦሪትና ስድስቱን ቃላተ ወንጌል በውስጣቸው የተጻፈባቸው ሁለት ጽላቶችን ሰጥቷቸዋል፡፡ አቡነ እስትንፋሰ ክርስቶስ ቤተ ክርስቲያን ከሠሩ በኋላ ዕለቱን ስንዴ ዘርተው፣ ወይን ተክለው፣ ጽድን ወይራንና ግራርን ተክለው በአንዲት ቀን ለቤተክርስቲያን አገልግሎት ዕለቱን አድርሰዋል፡፡ ስንዴውን ለመሥዋዕት ወይኑን ለቍርባን በተአምራት አድርሰዋል፡፡
አባታችን በጸሎት ላይ እንዳሉ መልአኩ ቅዱስ ሚካኤል ተልኮ መጥቶ አባታችንን በደመና ጭኖ ወስዶ ከጌታችን ከመድኃኒታችን ከኢየሱስ ክርስቶስ ፊት አቆማቸው፡፡ ጌታንም በቅዱሳኑ ሁሉ እንዲባረኩ ካደረጋቸው በኋላ መልአኩን ‹‹ወደ ተወለድኩባትና ወደ ኖርኩባት ቦታ ወደ ኢየሩሳሌም አድርሰው›› ብሎት ኢየሩሳሌምን አሳልሞ ሀገራችን መልሶ አምጥቷቸዋል፡፡
አባታችን ሁሉንም የኢትዮጵያን ቅዱሳት ገዳማትን ተዘዋውሮ ሲጎበኙ በሕይወተ ሥጋ የሌሉት የየገዳማቱ ቅዱሳን ሁሉ በአካል ይገለጡላቸው ነበር፡፡ ጎጃም ውስጥ እያስተማሩ፣ እያጠመቁ፣ የታመሙትን እየፈወሱ፣ የዕውራንን ዐይን እያበሩና ሙታንን እያሥነሱ ብዙ ካገለገሉ በኋላ ለዘጠኝ ዓመታት በባሕር ውስጥ ገብተው ቁልቁል ተዘቅዝቀው ለኢትዮጵያ ጸልየው የምሕረት ቃልኪዳን ተቀብለዋል፡፡ ከዘጠኝ ዓመት በኋላ ጌታችን መጥቶ ‹‹ከመነኮሳት ሁሉ ብልጫ ያለህ ወዳጄ ሆይ ኢትዮጵያንና ሕዝቦቿን ምሬልሃለሁ ከዚህች ባሕር ውጣ›› በማለት በሞት የሚያርፉበትን ቦታ ነግሯቸዋል፡፡
ጻድቁ ወደ ደብረ አሰጋጅ በሚሄዱበት ጊዜ ጸሐይ ልትገባ ስትል ‹‹በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ስም አውግዤሻለሁ ለመስፍን ኢያሱ በገባኦን እንደቆምሽ አሁንም ቀጥ ብለሽ ቁሚ›› ብለው ገዝተው ፀሐይን አቁመዋል፡፡ አቡነ እስትንፋሰ ክርስቶስም ደብረ አሰጋጅ ሲደርሱ ፀሐይ አፍ አውጥታ ‹‹አቡነ እስትንፋሰ ክርስቶስ ሆይ እገባ ዘንድ ፍታኝ›› ስትላቸው ‹‹እግዚአብሔር ይፍታሽ›› ባሏት ጊዜ ጠልቃለች፡፡ ጻድቁ ሌላው በእጅጉ የሚታወቁበት አንድ ትልቅ ቃል ኪዳን አላቸው፡፡ በአምላክ ልቡና የሚገኝ፣ በእመቤታችን በቅድስት ድንግል ማርያም ልቡና የሚገኝ፣ በቅዱስ ሚካኤልና በቅዱስ ገብርኤል ልቡና የሚገኝ እንደ መልክአ መድኃኔዓለም ያለች እጅግ አስገራሚ ጸሎት አለቻቸው፤ እርሷን ጸሎት በጸለዩ ጊዜ እልፍ ነፍሳትን ከሲኦል ያወጣሉ፡፡
ጸሎቷም የመድኃኔዓለምን የሰውነት ክፍሎች በሙሉ እየጠቀሰች እያንዳንዱ የሰውነት ክፍሎቹ የተቀበሉትን ጸዋትዎ መከራዎች ሁሉ ታዘክራለች፡፡ በእያንዳንዱ ክፍልም የጸሎት ማሳረጊያ አቡነ ዘበሰማያት ይደግማሉ፡፡ ንስሓ የገባ ኃጢአተኛ ሰው እንኳን ቢሆን ይህችን የአቡነ እስትንፋሰ ክርስቶስን ጸሎት በጸለየ ጊዜ ሺህ ነፍሳትን ከሲኦል እንደሚያወጣ ጌታችን በማይታበል ቃሉ ለአባታችን ነግሯቸዋል፡፡ እያንዳንዱን የመድኃኔዓለምን የሰውነት ክፍሎች በሙሉ እየጠቀሰች መከራዎቹን የምታዘክረውን ይህቺን በአምላክ ልቡና ያለች ግሩም የሆነች ጸሎት ነፍሳትን ከሲኦል አታወጣም ብሎ የሚጠራጠር ቢኖር መንግስተ ሰማያትን አያያትም፡፡ ጻድቁ ታኅሣሥ 8 ቀን ተወልው ሚያዝያ 9 ቀን በታላቅ ክብር ዐርፈዋል፡፡
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
በዚህች ቀን የከበረ ቀሲስ ዘሲማስ አረፈ። ይህም ፃድቅ ከፍልስጥኤም ሰዎች ወገን ነው። ወላጆቹም ደጋጎች ክርስቲያኖች ናቸው ይህንን ፃድቅ በወለዱት ጊዜ አምስት አመት አሳደጉት። ከዚያም የቤተክርስቲያን ትምህርትን የሀይማኖትንም ምስጢር ህግና ስርአትንም እያስተማረ እንዲያሳድገው ለአንድ ሽማግሌ መምህር ሰጡት።
ያ ሽማግሌም ተቀበሎ ልጁ አደረገው ትምህርቱንም ሁሉ አምላካዊ ጥበብ ሀይማኖትንም አስተምሮ አመነኰሰው ዲቁናም አሾመው በበጎ ስራም አደገ ትሩፋት መስራትንም አበዛ እግዚአብሄርንም ሁልጊዜ ያመሰግነዋል በቀንና በሌሊትም መፃህፍትን ያነባል። ስራ ሲሰራ ሲበላም ቢሆን ሁል ጊዜ ከአፉ ምስጋናዎችን አያቋርጥም።በዚያ ገዳም አርባ አምስት አመት በተፈፀመለት ጊዜ ቅስና ተሾመ ተጋድሎውንም ጨመረ።
ከዚህ በኃላም እየተጋደለና አገልግሎት በመጨመር በቅስና ሹመት አስራ ሶስት አመት ሲሆነው በዘመኑ ካሉ ተጋዳዮች ሁሉ እርሱ በገድሉ ከፍ ከፍ እንዳለ ተቃራኒ ጠላት ዲያብሎስ በልቡ ክፉ ሀሳብ አሳደረበት በልቡም ከበጎ ስራ እኔ ያልሰራሁት የቀረኝ አለን ይል ጀመር።
ነገር ግን የክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አልተወውም መልአኩን ልኮ በዮርዳኖስ ወንዝ አቅራቢያ ወደ አለ ገዳም ይሄድ ዘንድ እንጂ። ያን ጊዜም ተነስቶ ሄዶ ወደዚያ ገዳም ደረሰ በገድላቸው ፍፁማን የሆኑ እውነተኞች አገራውያንን አገኘ እርሱ ከእርሳቸው እንደሚያንስ አወቀ እርሱ በአለም ውስጥ ነው የኖረውና ስለዚህ ከእርሱ ይሻላሉ።
በዚያ ገዳም ከሳቸው ጋር ኖረ ብዙ ዘመናትም አብሮአቸው ሲጋደል ኖረ። ለዚያ ገዳም መነኰሳትም ልማድ አላቸው ታላቁ ፆም በደረሰ ጊዜ የመጀመሪያውን አንድ ሱባኤ በአንድነት ይፆማሉ በቅድስት እሑድ ስጋውንና ደሙን ይቀበላሉ በማግስቱም ሰኞ ጥዋት ሀያ ስድስተኛ መዝሙር እግዚአብሄር ብርሀነ ረድኤቱን ሰጥቶ ያድነኛል የሚያስፈራኝ ምንድነው የሚለውን እሰከ መጨረሻው እየዘመሩ ይወጣሉ በሚወጡም ጊዜ ወደ በሩ ተሰብስበው በአንድነት ፀልየው እርስ በርሳቸው ሰላምታ ይሰጣጣሉ የገደሙ አበ ምኔትም ይባርካቸዋል።
ከዚህም በኃላ እየአንዳንዱ ወደ በረሀ ይበተናሉ አንዱም አንዱ ባልንጀራውን ያየ እንደሆነ እንዳያየው ወደ ሌላ ቦታ ይሄዳል። ቅዱስ ዘሲማስም በየአመቱ ከሳቸው ጋራ ወጥቶ በበረሀው ውስጥ ይዘዋወራል የሚፅናናበትንም ይገልጥለት ዘንድ እግዚአብሄርን ይለምነው ነበር፡፡ ሲዘዋወርም በበረሀ የምትኖር ግብፃዊት ማርያምን አገኘ ከእርሷም በልጅነቷ ወራት በእርሷ ላይ እንዴት እንደሆነና በበረሀም የሆነውን ኑሮዋን ከመጀመሪያ እስከ መጨረሻ ተረዳ።
ከዚህ በኃላም በሁለተኛው አመት ስጋውንና ደሙን ያመጣላት ዘንድ ፈለገች እንዳለችውም አደረገላት። ለዚህም ፃድቅ ብሄረ ብፁአን ይገባ ዘንድ ተገባው እርሱም ገድላቸውን ፃፈ ስራቸውንና ፅድቃቸውን ገለጠ። ዘጠና ሶስት የሚሆን መላ እድሜው በተፈፀመለት ጊዜ በሰላም አረፈ።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
በዚህችም ቀን በእስክንድርያ ሊቀ ጳጳሳት በአባ ስንትዩ እጅ ታላቅ ምልክት ታየ። ይኸውም የከበረች የጌታን ፆም ከመነኰሳት ጋራ ይፆም ዘንድ ወደ አስቄጥስ ወደ አባ መቃርስ ገዳም ወጣ።
ሰሙነ ህማማትም በሆነ ጊዜ ገዳማቱንና አድባራቱን ሊዘርፉና ሊማርኩ የአረብ እስላሞች ተሰበሰቡ። በቤተ ክርስቲያኒቱ በስተምስራቅ ሰዎችንም ይገድሉ ዘንድ ሰይፎቻቸውን መዝዘው በእጆቻቸውም ይዘው በአለት ላይ ቆሙ።
ኤጲስቆጶሳትና መነኰሳትም ወደ አባ ስንትዩ ተሰብስበው ከአረብ እስላሞች እንዴት እንደሆነ ነግረው ከዚያ ገለል እንዲል ለመኑት። የከበረ አባ ስንትዩም ጌታችን የደቀ መዛሙርቱን እግራቸውን አጥቦ አዲስ ስርአት የሰራበት የፋሲካ ፍስህ በአል ሳይፈፀም እኔ ከዚህ አልለይም አላቸው።
እነዚህ እስላሞችም እየደነፉ ጩኸታቸው ተጨመረ። አባ ስንትዩም የወገኖቹን ድንጋፄ በአየ ጊዜ በላዩ የመስቀል ምልክት ያለበት በትሩን ይዞ ከእግዚአብሄር ወገኖች ጋራ ብሞት ይሻለኛል እያለ ወደ እነርሱ ሊወጣ ተነሣ።
ኤጲስቆጶሳቱም እንዳይወጣ ያዙት። እርሱ ግን ልባቸውን በማፅናናት አረጋጋቸውና ወደ አረብ እስላሞች ወጣ። እስላሞችም መስቀል ያለበትን በትር በእጁ ይዞ በአዩት ጊዜ ብዙ ሰራዊት እንዳሳደዳቸው ሆነው ወደ ኃላቸው ተመልሰው ሸሹ። ከዚያችም እለት ወዲህ ወደ ቅዱሳት መካናት እስላሞች አልተመለሱም።
ለእግዚአብሔር ክብር ምስጋና ይሁን እኛንም በከበሩ ቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ለዘለዓለሙ ይሁን አሜን፡፡

No comments:

Post a Comment

Post Bottom Ad

Pages