ስንክሳር_ዘወርኀ_የካቲት 5 - አትሮንስ ሚዲያ - Atrons Media

አትሮንስ ሚዲያ - Atrons Media

ስብኩ ወንጌለ ለኩሉ ፍጥረት ማቴ 16፤15


በቅርብ የተጻፉ

Post Top Ad

Friday, March 3, 2023

ስንክሳር_ዘወርኀ_የካቲት 5

 አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም

የካቲት አምስት በዚች ቀን የእስክንድርያ አገር ሊቀ ጳጳሳት የከበረ አባት #ቅዱስ_አክርጵዮስ አረፈ፣ አባት ጴጥሮስ የተባለ #አባ_ብሶይ አረፈ፣ አስቀድሞ ራሱን ለኃጢአት አስገዝቶ የነበረ ጽኑዕ ተጋዳይ #አባ_ዕብሎይ አረፈ፣ ኢትዮጵያዊ የሆኑ ጻድቃን #አቡነ_አሞኒ የተወለዱበት ነው፡፡


የካቲት አምስት በዚች ቀን የእስክንድርያ አገር ሊቀ ጳጳሳት የከበረ አባት አክርጵዮስ አረፈ። እርሱም ለአባቶች ሊቃነ ጳጳሳት ዐሥረኛ ነው።
ይህም አባት እግዚአብሔርን የሚፈራ ንጹሕ ቅዱስ ነው ። በእስክንድርያ አገርም ቄስ ሁኖ የሚያገለግል ነበር ከእርሱ በፊት የነበረ ሊቀ ጳጳሳት አባ ከላድያኖስ በአረፈ ጊዜ የእስክንድር አገር ሕዝቡና ኤጲስቆጶሳቱ መረጡት በወንጌላዊ ማርቆስ ወንበርም ላይ ሊቀ ጵጵስና ሾሙት።
ከዚህም በኋላ እንደ ሐዋርያት መልካም ጉዞን ተጓዘ የእግዚአብሔርን ሃይማኖት ሕይወት የሆነ ሕጉንም እያስተማረ ቅዱሳት መጻሕፍትንም እያነበበላቸውና እያስተማራቸው መንጋዎቹን ይጠብቃቸው ነበር ሁል ጊዜም ይመለከታቸዋል አንድ የብር አላድን ወይም አንድ የወርቅ ዲናርን ጥሪት አላኖረም ከዕለት ምግቡ ከቁርና ከሐሩር ሥጋውን ከሚሸፍንበት ልብስ በቀር ምንም አላከማቸም።
በዚህም ተጋድሎ ዐሥራ ሁለት ዓመት ኑሮ ጌታችንንም አገልግሎ በሰላም አረፈ።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
በዚችም ዕለት ተጋዳይ የሆነ አባት ጴጥሮስ የተባለ አባ ብሶይ አረፈ እርሱም ከላይኛው ግብጽ አክሚም ከሚባል ከተማ ነው። በጐልማሳነቱም ጊዜ የከፉ ሥራዎችን የሚሠራ ሁኖ ነበር በመብላትና በመጠጣትም ይደሰት ነበር። እግዚአብሔርም የነፍሱን ድኅነት ሽቶ ጽኑ ደዌ አመጣበትና ለመሞት ተቃረበ።
ነፍሱንም በተመሥጦ አውጥተው የሥቃይ ቦታዎችንም ጥልቅ የሆነች ጕድጓድንም አሳዩት፡፡ በዚያም ብሩህ ልብስ የለበሱ ሰዎች አሉ በእጆቻቸውም የሰው በድን ነበረ አራት ክፍል አድርገው ለያዩትና የሰውን ገንዘብ የሚሰርቀውን ሁሉ እንዲህ ያደርጉበታል አሉት። ይህንንም ነገር በሰማ ጊዜ ጮኸ ከልቡም አዝኖ አለቀሰ ከዚህም በኋላ ነፍሱ ተመለሰች ዐይኖቹንም ወደ ሰማይ አቅንቶ ጌታዬና ፈጣሪዬ ከዚህ ደዌ ከአዳንከኝ እኔ ስለ ኃጢአቴ ንስሐ በመግባት በፍጹም ልቡናዬ አመልክሃለሁ ከእንግዲህም ከቶ ለዘላለሙ የሴት ፊት አላይም አለ።
በዚያንም ጊዜ ከደዌው አዳነውና ተነሥቶ ብንዋይ ወደሚባል ገዳም ሔደ መነኰሳቱም ከፈተኑት በኋላ የምንኲስናን ልብስ አለበሱት በግብጽ አገር ሁሉ እስከሚሰማ ታላቅ ተጋድሎን በጾም በጸሎት በመስገድም ተጋደለ ከሁሉ በላይም ከፍ ከፍ አለ ለመነኰሳትም ትምህርት የሚሆኑ የሚጠቅሙ ድርሳናትንና ተግሣጻትን ደረሰ አንድ ጊዜም እንጀራ ሳይቀምስ ውኃ ሳይጠጣ አንድ ወር ጾመ እንዲህም እየተጋደለ ሠላሳ ስምንት ዓመት ያህል ኖረ።
መላዋንም ሌሊት በጸሎትና በስግደት በመትጋት ቁሞ ያድራል ሰዎች የሚሠሩት ሁሉ ጻድቅም ቢሆን ኃጢአተኛም ቢሆን በፊቱ ግልጥ ሆነ ከዚህም በኋላ ጥቂት ታመመና በሰላም አረፈ።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
በዚህችም ቀን አስቀድሞ ራሱን ለኃጢአት አስገዝቶ የነበረ ጽኑዕ ተጋዳይ አባ ዕብሎይ አረፈ። ይህም የበጎች አርቢ ራሱን ለሰይጣን በማስገዛት ከኃጢአት ሥራ ምንም የቀረው የለም ያመነዝራል ይሰርቃል ይቀማል ይገድላል በዚህም የሰይጣንን ሥራ እየፈጸመ አርባ ዓመት ያህል ኖረ።
በአንዲትም ዕለት ከቀኑ እኩሌታ ከበጎቹ ጋር በዱር ውስጥ ሳለ እነሆ የመውለጃዋ ጊዜ የደረሰ ያረገዘች ሴትን አየ ሰይጣንም በልቡ ክፉ ሐሳብን ጨመረ እንዲህም አለ የተረፈችኝ ኃጢአት አንዲት አለች እርሷም ያረገዘች ሴት ሆዷን ሠንጥቄ በእናቱ ሆድ ሕፃኑ የሚተኛበትን አይ ዘንድ ነው።
ያን ጊዜም ተወርውሮ ሔደ በራስዋ ጠጕር ይዞ ከምድር ላይ ጣላት ሾተልም አንሥቶ ሆዷን ሠነጠቀ ሕፃኑንም በማሕፀኗ ውስጥ እንዴት ሁኖ እንደተኛ አየው እርሷም በጻዕር ተጨንቃ አስቀድማ ሞተች ሕፃኑ ግን በጻዕር እየተሠቃየ ብዙ ቆይቶ ሞተ። በግ አርቢውም የሠራውን ይህን ታላቅ ኃጢአት ተመልክቶ ደነገጠ እጅግም አዘነ መራራ ልቅሶንም በማልቀስ ታላቅ ኃጢአትን ሠርቻለሁና ወዮልኝ አለ።
በዚያንም ጊዜ በጎቹን እንደተበተኑ ትቶ በእጁ በትሩን ብቻ ይዞ ወደ አስቄጥስ ገዳም እስከሚደርስ እያለቀሰ ተጓዘ ወደ አረጋውያን መነኰሳትም አልገባም ከእርሳቸው ዐሥር ምዕራፍ ያህል ርቆ ወደ በርሀ ውስጥ ገባ እንጂ በቤት ውስጥም አያድርም ነበር ከአራዊት ጋር የሚኖር ሆነ እንጂ ከዕፀዋትም ፍሬ በየጥቂቱ ይመገብ ነበር ከዕንባ ጋርም እየጮኸ አቤቱ በደልኩ ክፉ ሥራንም ሠራሁ ይቅር በለኝ እኔ ኃጢአተኛ የሆንኩ ክፉ ባርያ ነኝና አንተም ቸር አምላክ ይቅር ባይ አባት ነህና የማይበድል ባሪያ የማይምር ጌታ የለምና ይቅር በለኝ እንዲህም እየተጋደለ አርባ ዓመት ኖረ።
ከሌሊት ቍር ከቀን ፀሐይ ሐሩርና ትኩሳት የተነሣ ሥጋው ደርቆ ጠቆረ ከዚህም በኋላ እንዲህ የሚለውን ቃል ሰማ ስለ ሴቲቱ ደም ጌታ ይቅር ብሎሃል ጽና በርታ ይህንንም ያለው እንዳይታክትና ዳግመኛ በኃጢአት ውስጥ እንዳይወድቅ ነው።
ይህንም በሰማ ጊዜ ከሦስት ቀን ብቻ በቀር ያቺን ዓመት እስከሚፈጽም መሪር ልቅሶ እያለቀሰ ተጋድሎውን ጨመረ እነሆ የእግዚአብሔር መልአክ ከእርሱ ዐሥራ አምስት ምዕራፍ ያህል ርቆ የሚገኝ ከቶ ሰውን ሳያይ በዚያች በረሀ ሰባ ዓመት የኖረውን አንዱን ገዳማዊ አንተ ካለህበት ቦታ ወደ ውጭ ሒድ ሽማግሌ ሰው ታገኛለህ ኃጢአቱን ከአመነልህ አጽናናው ኃጢአትህ ሁሉ ስለ ሕፃኑም መገደል ተሠርዮልሃል በለው በማለት አዘዘው።
በዚያንም ጊዜ ያ ገዳማዊ ሒዶ አገኘው አርስበርሳቸውም ሰላምታ ተሰጣጡ እርሱ ዕብሎይ ግን ያለማቋረጥ ያለቅስ ነበር ገዳማዊውም የሠራኸውን ንገረኝ በምን ምክንያትስ ወደዚህ መጣህ አለው። እርሱም ሁሉንም ነገረው ያረገዘችዋንም ሴት ሆድዋን እንደሠነጠቀ ነገረው ገዳማዊውም ኃጢአትህ ሁሉ ተሠርዮልሃል አባቴ ሆይ ደስ ይበልህ ነገ የእግዚአብሔር መልአክ ወዳንተ መጥቶ የክርስቶስን ሥጋና ደም ያቀብልሃል አለው።
የቀዳሚት ሰንበት ዕለትም በነጋ ጊዜ ከቶ እንደርሱ ሁኖ የማያውቅ ጣፋጭ ሽታ ሸተተ አባ ዕብሎይም ገዳማዊውን አባቴ ሆይ ከፍርሀት የተነሣ ነፍሴ ከሥጋዋ ልትለይ ደረሰች አለው ይህንንም ባለ ጊዜ በመነኰስ አምሳል ከአጠገቡ ቁሞ መልአኩን አየው እርሱም ተቸገርኩ እግዚአብሔርም አዳነኝ:: ነፍሴ ሆይ ወደ ዕረፍትሽ ተመለሽ:: እግዚአብሔር ረዳትሽ ነውና፡፡ ነፍሴን ከሞት አድኗታልና። ዐይኖቼንም ከእንባ እግሮቼንም በዳጥ ከመሰናከል። በሕያዋን አገር እግዚአብሔርን አገለግለው ዘንድ እያለ ይዘምር ነበር።
የበጎች ጠባቂ የነበረ አባ ዕብሎይም ይህን ነገር በሰማ ጊዜ በምድር ላይ ወድቆ እንደ በድን ሆነ መልአኩም በሰው አምሳል እጁን ዘርግቶ አነሣው ልቡም ጸንቶ በመልአክ እጅ ከሰማይ የወረደለትን ሥጋውንና ደሙን ተቀበለ መልአኩም ወደ ሰማይ ዐረገ።
አባ ዕብሎይም ቍርባኑን በተቀበለ ጊዜ ሰውነቱ ሁሉ እንደ በረድ ፀዓዳ እንደ ፋናም ብሩህ ሆነ በዚያችም ዕለት ሁለቱም ደስ እያላቸው እግዚአብሔርንም እያመሰገኑ እስከ ማታ ዋሉ።
እብሎይ ግን የቀድሞ ጸሎቱን አላቋረጠም እንዲህም እያለ እኔ ክፉ ባሪያ በየሰባቱ ሰባ ጊዜ በደልኩ ቸር ጌታ ሆይ መሐሪ አባት ሆይ ይቅር በለኝ የማይበድል ባሪያ የማይምር ጌታ የለምና። በዚችም ዕለት እስከ ሌሊቱ እኩሌታ እግዚአብሔርን እያመሰገኑ አደሩ እርሷም እሑድ ናት:: በዚያችም ጊዜ ከፊተኛው የሚበልጥ የሽቱ መዓዛ ሸተተ ገዳማዊውም ወንድሜ ዕብሎይ ና በውኃ ታጠብ ደስ ይበልህም በዚች ሰዓት ከተቀበልከው መከራ ታርፋለህና አለው:: በዚያንም ጊዜ ከእግዚአብሔር የታዘዘ መልአክ ለሁለቱም ቍርባኑን አቀበላቸው አባ ዕብሎይም አረፈ መላእክትም ነፍሱን ተሸክመው እስከ አርያም በረሩ።
ያ ገዳማዊም እኔ ሽማግሌ ነኝ ሥጋውን መሸከም አልችል የምቆፍርበትም የሌለኝ ምን አደርጋለሁ ብሎ የሚያስብ ሆነ በዚያንም ጊዜ ሁለት አንበሶች መጥተው ለሥጋው ሰገዱ መቃብሩንም ቆፍረው ሥጋውን እንደ ሰው ተሸክመው ወስደው ቀበሩት ገዳማዊውንም እጅ ነሱት እርሱም ባረካቸውና በሰላም ሔዱ።
ከዚህም በኋላ ያ ገዳማዊ የሚቀብረኝ አገኝ ይሆን ብሎ አሰበ ወደርሱም እንዲህ የሚል ቃል መጣ አትዘን ሥጋህን እኔ አስቀብራለሁ ያለ ሦስት ቀንም አልቀረህም ወዳንተም ሦስት ሰዎችን እልካለሁ የበግ ጠባቂው የአባ እብሎይን ገድል ንገራቸው እነርሱም ለሌሎች ይንገሩ ከእግዚአብሔር ምሕረት ተስፋ እንዳይቆርጡ በኃጢአት ለወደቁ አለኝታ ይሆን ዘንድ።
በማግሥቱም ሦስት ሰዎች መጡ እርሱም የበግ ጠባቂውን የአባ ዕብሎይን ተጋድሎ ነገራቸው እነርሱም እጅግ አድንቀው ጻፉት ከገዳማዊውም ዘንድ እስከ ሦስት ቀን ተቀመጡ ከዚህም በኋላ ገዳማዊው ተነሥቶ ጸለየ ነፍሱንም በእግዚአብሔር እጅ ሰጠ እነዚያ ሁለት አንበሶችም መጡ መቃብርንም ቆፍረው እንደ ሰው ወስደው ቀበሩትና ከእነዚያ ሦስት ሰዎች ጋር ተጓዙ ወደ አስቄጥስ ወደ አባ መቃርስ ገዳም እስከሚአደርሷቸው መርተው ወሰዱአቸው ሰዎቹም የሆነውን ሁሉ ለመነኰሳቱ ነገሩአቸው። እነርሱም እጅግ አደነቁ የበግ አርቢው የአባ ዕብሎይን ገድል ጻፉ ሁል ጊዜም በእሑድ ዕለት የሚያነቡት ሆኑ።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
በዚህችም እለት ኢትዮጵያዊ የሆኑ ጻድቃን አቡነ አሞኒ የተወለዱበት በዓልና ለልጃቸው አቡነ ዮሐኒም መታሰቢያቸው ነው፡፡ አባታችን የካቲት5 ቀን አክሱም ውስጥ ሲወለዱ ሰይጣናት የወላጆታቸውን ቤት ከበው በማየታቸው እንደተወለዱ በእጃቸው ቢያመለክቱ በአንድ ጊዜ 60 ሰይጣናት ተሸንፈው እንጢስ በነው ጠፍተዋል። አሞኒ ማለት አሸናፊ ማለት ነው። አባ አሞኒ የራስ ፀጉራቸው ልብስ መጎናጸፊያ ሆኖቸው የኖሩ ታላቅና ቀደምት አባት ናቸው።
በደመና ተጭነው ኢየሩሳሌም ደብረ ዘይት ድረስ በመሄድ ከአባ ዕብሎይ ጋር ተገናኝተው ብዙ ምሥጢርን አውርተዋል። አባ ዮሐኒንያ ሳደጉት አስተምረው ያሳደጓቸው አባ አሞኒ ናቸው፡፡ የእናቱን ጡት ፈጽሞ ጠብቶ የማያውቀውን የመንፈስ ቅዱስ ልጃቸውን አባ ዮሐኒን እሳቸው እያጫወቱት የታዘዘ አሞራ በክንፎቹ እያለበሰው ቶራ (ሰሳ) እያጠባችው ነው ያደገው፡፡
አባ አሞኒ ልጃቸው አባ ዮሐኒ አድጎ 12 ዓመት ሲሆነው ከዚህም በኋላ ዲቁና ሊያሾሙትና አክሱም ጽዮን ወስደው ሊያስባርኩት ቤተ ካህናት ከተባለው ቦታ ይዘውት ሲሄዱ ልዩ ስሙ ሲሂታ ከሚባለው ቦታ ሲደርሱ ከወገባቸው በላይ እራቁታቸውን የሆኑ እንስራ የተሸከሙ ዐሥር ሴቶች አገኙ፡፡ አባ ዮሐኒም አባታቸውን "አባቴ እነዚህ ደረታቸው ላይ ቀንድ ያላቸው ጽጉራቸው የረዘመ ምንድን ናቸው? እንደ እኛ የሆኑ መስህታን የሚባሉት እነዚህ ናቸውን?" አሏቸው፡፡ አባ አሞኒም "አይደሉም ልጄ ዝም ብለህ ሂድ" አሏቸው፡፡ በኋላ ግን ትዝ ሲላቸው "በዱር እንስሳት ያሳደኩት ልጄ ወንድና ሴት ለይቶ ሲያውቅ በዚያው ሊሳሳት አይደልምን?" ብለው በማሰብ ዲቁናና ክህነቱ ይቅርበት ብለው ተመልሰው ወደ በዓታቸው ይዘውት ገቡ፡፡ ከዚህም በኋላ አባ አበይዶ ወደ አባ አሞኒ መጣና እሳቸውን ከአባ ዮሐኒ ጋር እያገለገሏቸው ተቀመጡ፡፡ ዮሐኒ እየጻፈ አበይዶ የሚጻፍበትን ቆዳ እያዘጋጁ ሦስቱም በአንድነት በተጋድሎ መቀመጥ ጀመሩ፡፡
አባ ዮሐኒ ሃያ ዓመት አባ አሞኒ ደግሞ አርባ ዓመት በሆናቸው ጊዜ መልአኩ ቅዱስ ገብርኤል ለአባ አሞኒ ተገለጠላቸውና "አሞኒ ሆይ ከእንግዲህስ እግዚአብሔር ወደኔ ና ብሎሃል" አላቸው። እሳቸውም ልጆቻቸውን አባ ዮሐኒንና አባ አበይዶን ጠርተው "በሉ እንግዲህ እኔ ወደ እግዚአብሔር መሄዴ ነውና ጸልዩልኝ" አሏቸው፡፡ ከማረፋቸውም በፊት አባ ዮሐኒን ለብቻቸው ጠርተው "አንተ አባ ዮሐኒ ካሁን በፊት ሲሂታ ላይ ያየሃቸው ሴቶች ናቸው፣ አዳምንም ከገነት ያስወጡ ናቸው፡፡ ወደፊትም እንደ እነርሱ ያለ የደረሰብህ እንደሆነ ካለህበት ገደል ተወርውረህ ውደቅመ በባሕር ውስጥ ጥለቅ" ብለው ነግረዋቸው ዕለት ኅዳር5 ቀን በሰላም ዐረፉና ወደ ጠራቸው እግዚአብሔር ሄዱ፡፡
ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በከበሩ ቅዱሳን ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።

No comments:

Post a Comment

Post Bottom Ad

Pages