ስንክሳር_ዘወርኅ_ኅዳር 24 - አትሮንስ ሚዲያ - Atrons Media

አትሮንስ ሚዲያ - Atrons Media

ስብኩ ወንጌለ ለኩሉ ፍጥረት ማቴ 16፤15


በቅርብ የተጻፉ

Post Top Ad

Friday, March 3, 2023

ስንክሳር_ዘወርኅ_ኅዳር 24

 አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም

ኅዳር ሃያ አራት በዚች ቀን #የሃያ_አራቱ_ካህናተ ሰማይ የበዓላቸው መታሰቢያ ነው፣ #አቡነ_ተክለ_ሃይማኖትም ከሃያ አራቱ ካህናተ ሰማይ ጋር የሥሉስ ቅዱስን መንበር ያጠኑበት ነው፣ #የአቡነ_ዜና_ማርቆስ ልደታቸው ነው፣ #ቅዱስ_አዝቂር_ሰማዕት ከአርባ ስምንት ሰዎች ጋር በሰማዕትነት ያረፈበት ፣ #ቅዱስ_አባ_ዮሴፍ_ዘሀገረ_ፃን ያረፈበት ዕለት ነው።


ኅዳር ሃያ አራት በዚህች ቀን በእግዚአብሔር ዙፋን ዙሪያ የሚኖሩ የሃያ አራቱ ካህናተ ሰማይ የበዓላቸው መታሰቢያ ነው ።
እሊህም ሥጋ የሌላቸው ረቂቃን የእውነት ካህናት የሆኑ ከቅዱሳን ሁሉ በላይ የሆኑና ከሰማይ ሠራዊት ሁሉ ከፍ ከፍ ያሉ ናቸው እነርሱም ለእግዚአብሔር ቀራቢዎች በመሆን ለሰው ወገን የሚማልዱ ከእጃቸው ውስጥ ካለ ማዕጠንት ጋርነ እንደ ዕጣን የቅዱሳንን ጸሎት የሚያቀርቡ ናቸው ያለእነርሱም አቅራቢነት ጽድቅና ምጽዋት ወደ እግዙአብሔር አይቀርብም።
ወንጌላዊ ቅዱስ ዮሐንስ በራእዩ እንዲህ ብሎ እንደተናገረ። በዙፋኑ ዙሪያ ሃያ አራት መንበሮች አሉ በእነዚያ መንበሮች ላይም ሃያ አራት አለቆች ተቀምጠዋል ነጭ ልብስ ለብሰዋል በራሳቸውም ላይ የወርቅ አክሊል አለ።
ሁለተኛም እንዲህ አለ ሌላም መልአክ መጥቶ በመሠዊያው ፊት ቆሞ የወርቅ ጽንሐሕ ይዟል በመንበሩ ፊት ባለ በወርቁ መሠዊያ ላይም የቅዱሳንን ሁሉ ጸሎት ያሳርግ ዘንድ ብዙ ዕጣንን ሰጡት ። የዕጣኑም ጢስ ከቅዱሳኑ ጸሎት ጋር በዚያ መልአክ እጅ ወደ እግዚአብሔር ፊት ዐረገ ።
የነበረ የሚኖር የአማልክት አምላክ እግዚአብሔር ቅዱስ ቅዱስ ቅዱስ ነው እያሉ በመዓልትና በሌሊት ዕረፍት የላቸውም ። እሊህም እንስሶቹ ለዘላለሙ ሕያው ለሚሆን በዙፋን ላይ ለተቀመጠ ለሱ እንዲህ እያሉ ክብር ምስጋና አቀረቡ ።
እሊህ ሃያ አራቱ አለቆች አክሊላቸውን በዙፋኑ ፊት አውርደው ለዘላለሙ ሕያው ለሚሆኑ በዙፋን ላይ ለተቀመጠ ለእሱ ሰገዱለት ። አክሊላቸውንም ወደ ዙፋኑ ፊት ወስደው አቤቱ ፈጣሪያችን ኃይልና ምስጋና ክብር ላንተ ይገባል ይሉታል አንተ ሁሉን ፈጥረሃል የተፈጠረውም ሁሉ በአንተ ፈቃድ ይኖራልና ።
እነርሱ በእግዚአብሔር ዘንድ በባለሟልነት እጅግ የቀረቡ መሆናቸውንና ስለሁላችን የአዳም ልጆች ስለሚለምኑና ስለሚማልዱ ከብሉይና ከሐዲስ የከበሩ መጻሕፍት ምስክር ሁነዋል ስለዚህም የበዓላቸውን መታሰቢያ እናደርግ ዘንድ የቤተ ክርስቲያን መምህራን አዘዙ ።

አቡነ ተክለ ሃይማኖትም ከሃያ አራቱ ካህናተ ሰማይ ጋር የሥሉስ ቅዱስን መንበር እንዳጠኑ፡- አቡነ ተክለ ሃይማኖት ወደ አቡነ ኢየሱስ ሞዐ መጥተው በሐይቁ ዳር ቆመው ሳለ ሊቀ መላእክት ቅዱስ ሚካኤል ተገልጦላቸው ነው በእግሩ በውኃው ላይ እየሄደ እያሳያቸው ተከትለውት እንዲሄዱ የነገራቸው። አባታችን አቡነ ተክለ ሃይማኖትም መልአኩን ተከትለው ሐይቁን በእግራቸው ተራምደው ተሻግረው አቡነ ኢየሱስ ሞዐን አገኟቸው፡፡ እርሳቸውም አቡነ ተክለ ሃይማኖት ወደ እርሳቸው እየመጡ እንደሆነ በመንፈስ ዐውቀው ነበርና ሲያገኟቸው በጣም ተደስተው ከተቀበሏቸው በኋላ አመነኩሰዋቸዋል፡፡
ከዚህም በኋላ አባታችን በዚያው በሐይቅ በታላቅ ተጋድሎ መኖር ጀመሩ፡፡ አክፍሎትንም በየሳምንቱ ያከፍላሉ፣ ከእሁድና ከቅዳሜ በቀር ምንም አይቀምሱም ነበር፡፡ በእነዚህም ዕለት የአጃ ቂጣ ወይም የዱር ቅጠል ይመጉ ነበር፡፡ ወዛቸው እንደ ውኃ ፈስሶ ምድሪቷን እስኪያርሳት ድረስ እስከ 70 ሺህ ስግደትንም በመስገድ ራሳቸውን እጅግ አደከሙ፡፡ በእነደዚህ ዓይነቱ ተጋድሎ ላይ ሳሉ ነው ሊቀ መላእክት ቅዱስ ሚካኤል ድንገት ነጥቆ ወስዶ ከሥሉስ ቅዱስ ዙፋን ፊት ያቆማቸው፡፡
ከዚህ በኋላ ስለሆነው ነገር ራሳቸው አባታችን ተክለ ሃይማኖት ሲናገሩ ‹‹…ከዚህ በኋላ መልአኩ ወደ ሰማይ አውጥቶ ከመጋረጃው ውስጥ አስገብቶ ከሥላሴ ዙፋን ፊት አቆመኝና ሰገድኩለት፡፡ ከዚያ አስቀድሞ በማላውቀው በሌላ ምስጋና አመሰገንኩት፡፡ ‹ተክለ ሃይማኖት ክፍልህ ከ24ቱ ካህናቶቼ ጋር ይሁን› የሚል ቃል ከዙፋኑ ውስጥ ወጣ፡፡ የወርቅ ጽና አምጥተው ሰጡኝና ከእነርሱ ጋር አንድነት አጠንሁ፡፡ ምስጋናዬ ከምስጋናቸው ጋር ልብሴም እንደልብሳቸው ሆነ፡፡ ፈጣሪዬንም በሦስትነቱ ተገልጦ አየሁት፡፡ በጸሎትህ የሚታመን ሰው ሁሉ ስለአንተ ይድናል አለኝ…..›› (ገድለ አቡነ ተክለ ሃይማኖት ገጽ 216-223)
ይህንን ታላቅ በዓል ነው ዛሬ የምናከብረው፡፡ አቡነ ተክለሃይማኖት እንኳን አንደበታቸው የለበሱትም ልብሳቸውም ጭምር እግዚአብሔርን በሰው አንደበት እንደሚያመሰግን በቅዱስ ገድላቸው ላይ ተጽፏል።

አቡነ ዜና ማርቆስ በወንጌላዊ በቅዱስ ማርቆስ ብስራት እንደተወለዱ፦ አባታችን ዜና ማርቆስ ሀገራቸው ጽላልሽ አውራጃ ምድረ ዞረሬ ስትሆን ትውልዳቸው ከነገደ ሌዊና ከእስራኤል ነገሥት ወገን ነው፡፡ ወላጆቻቸው ልጅ በማጣት ሲያዝኑ አንድ ዕለት ሐዋርያውና ወንጌላዊው ቅዱስ ማርቆስ ወደ እናታቸው ማርያም ዘመዳ ሌሊት መጥቶ ገድሉና ትሩፋቱ በዓለም ሁሉ የመላ ጻድቅ ልጅ እንደምትወልድ አበሰራት፡፡
ለአባቱ ለቀሲስ ዮሐንስም እንዲሁ ተገልጦለት ‹‹ሚስትህ ማርያም ዘመዳ የካቲት 24 ፀንሳ ኅዳር 24 ቀን ይኸውም በካህናተ ሰማይ በዓል ቀን ትወልዳለች፣ ስሙም ዜና ማርቆስ ይባላል›› በማለት ብስራቱን ነግሮታል፡፡
በወንጌላዊው ቅዱስ ማርቆስ ብሥራት መሠረት አባታችን ዜና ማርቆስ በዚህች ዕለት ኅዳር 24 ቀን በተወለዱ ጊዜ ቅዱስ ዑራኤልና ቅዱስ ሩፋኤል የብርሃን ልብስ አልብሰው በክንፋቸው ሲጋርዱአቸው ለሰዎች ሁሉ ታይቷል፡፡ የአቡነ ሳሙኤል ዘወገግ አባት ቅዱስ እንድርያስና የአቡነ ተክለሃይማኖት አባት ቅዱስ ጸጋ ዘአብ እስኪደነቁ ድረስ ይህን በዓይናቸው ተመልክተዋል፡፡ ሁለቱ መላእክትም አቡነ ዜና ማርቆስን ከእናታቸው ዕቅፍ ወስደው ወደ ሐዋርያው ማርቆስ መቃብር ወስደው ለማርቆስና ለቅዱሳን ጳጳሳት አስባርከዋቸው መልሰው ለእናታቸው ሰጧቸው፣ እናታቸው ግን ይህን አታውቅም ነበር፡፡ አቡነ ዜና ማርቆስ በተወለዱ በሦስተኛው ቀን በእግራቸው ቆመው ‹‹አንድ አምላክ ለሆኑ ለአብ ለወልድ ለመንፈስ ቅዱስ እሰግዳለሁ›› ብለው ሦስት ጊዜ አምላካቸውን አመስግነው ሰግደዋል፡፡
በ40 ቀናቸውም ሲጠመቁ የሚያጠምቃቸው ካህን የአባታቸው ወንድም እንድርያስ ውኃው ሲፈላ አይቶ ሸሽቷል፡፡ መልአኩም እንዳይፈራ ነግሮት ለእርሱም ተአምር እንደሚደረግለት አስረዳው፡፡ እንድርያስም ዕድሜው 72 ነበርና ራሰ በራ ስለነበር አባታችንን ባጠመቀበት በውኃው ራሱን ቢታጠብበት ጸጉር አብቅሏል፡፡ ሕዝቡም ሁሉ ይህን አይቶ አደነቀ፡፡ ያችም ውኃ ሌሎች በጣም ብዙ ተአምራትን አደረገች፡፡
አቡነ ዜና ማርቆስ አንድ ዓመት በሆናቸውም ጊዜ ቤተክርስቲያን ውስጥ እየዳኹ ሲሄዱ መልአክ በክንፎቹ አቅፎ ነጥቆ ወደሰማይ ወስዶ ጌታችንና እመቤታችን ጋር አቅርቦ አስባርኳቸዋል፡፡ እንዲሁም የ15ቱን ነቢያት፣ የ12ቱን ሐዋርያት የ72ቱን አርድእት፣ ሃይማኖታቸው የቀና የ318ቱን ሊቃውንት፣ የጻድቃንን፣ የሰማዕታትን የእነዚህን ሁሉ በረከት እንዲቀበሉ ካደረጋቸው በኋላ ወደዚያች ቤተክርስቲያን መለሳቸው፡፡ የአቡነ ዜና ማርቆስን የዕረፍታቸውን በዓል ከ9 ቀናት በኋላ ታኅሣሥ 3 ቀን ስለምናከበር አምላካቸው ከዕረፍታቸው ቀን ያድርሰንና ያንጊዜ ሙሉን ዜና ገድላቸውን እናየዋለን፡፡ በረከታቸው ይደርብን በጸሎታቸው ይማረን፡፡

በዚችም ዕለት የናግራን አገር ቄስ የከበረ አዝቂር የሐሚር ንጉሥ ሰራብሄል በነገሠበት ወራት ከእርሱ ጋር ካሉ አርባ ስምንት ሰዎች ጋር በሰማዕትነት አረፈ ።
ይህም ንጉሥ አዝቂርን ወደ ወህኒ አስገብተው እንዲዘጉበት ጠባቂዎቹንም ከሰው ወገን ማንም እንዳይገባ ብሎ አዘዘ ። ቅዱስ አዝቂርም በጸለየ ጊዜ የወህኒ ቤቱ ደጃፍ ተከፈተና ሃምሳ ሰዎች ወደርሱ ገቡ እርሱም በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም አጠመቃቸው ።
ንጉሥ ሰራብሄልም በሰማ ጊዜ ከወህኒ ቤት አውጥተው ወደሌላ አገር እንዲወስዱት አዘዘ በጉዞም ላይ ስሙ ኪርያቅ ከሚባል ሰው ጋር ተገናኘ ቀሲስ አዝቂርም ኪርያቅን ኪርያቅ ሆይ ላንተ የምሥራች ይገባል ለሰማዕትነት ይወስድሃልና አለው ። የንጉሥ ሎሌዎችም ሰምተው አሥረው ከእርሱ ጋር ወሰዱት ። ዳግመኛም ሁለት ሰዎች ተገናኙትና ስለ ክርስቶስ አጥምቀን አሉት ያን ጊዜም ቅዱስ አዝቂር ጸለየና ከበረሀ ቦታ ውኃ አፍልቆ ከኪርያቅ ጋር አጠመቃቸው ።
ከዚህም በኋላ ወደበረሀ ውስጥ በደረሱ ጊዜ ለእሳቸውም ለእንስሶቻቸውም የሚጠጡት ውኃ አጥተው ወደ እግዚአብሔር እንዲለምንላቸው ቅዱስ አዝቂርን ለመኑት በጸለየም ጊዜ ደመና መጣ በመሐል እጅ በሚታፈን መጠን በገበታ ላይ ዘነበ ሰባት መቶ ያህል ሰዎች ከእንስሶቻቸው ጋር ጠጥተው ረኩ ።
ወደ ንጉሡም በአቀረቡት ጊዜ ወደ አገራችን ያመጣኸው ይህ አዲስ ትምህርት ምንድነው አለው ቅዱስ አዝቂርም ነቢያት በኦሪት ከሰበኩት በቀር ሌላ አዲስ ትምህርት አላመጣሁም አለ ንጉሡም ይህን ሰምቶ በክርስቲያን ሃይማኖት ላይ ተዘባበተ።
ከአይሁድ መምህራንም አንዱ ተነሥቶ እንዲህ አለ ጌታዬ ሆይ ወደ አገሩ እንዲወስዱትና በዕንጨት ላይ ሰቅለው በሕይወት ሳለ በእሳት እንዲአቃጥሉት እዘዝ አለው ንጉሡም እንደ አይሁዳዊው ቃል አዘዘ።
ወደ ናግራን አገርም በአደረሱት ጊዜ በዕንጨት ላይ ሰቅለው ከበታቹ እሳትን አነደዱ ቅዱስ አዝቂርም ወደ ጌታችን ጸለየ በዚያንም ጊዜ ከማሠሪያው ተፈትቶ ከእሳት ውስጥ በደኅና ወጣ አይሁድም በደንጊያ እንውገረው ተባብለው በወገሩት ጊዜ ደንጊያዎች ተመልሰው ከአይሁድ የሚበዙትን ገደሉ ።
ከተረፉትም ሰይፍን አንሥተው የቅዱስ አዝቂርን ራስ ቆረጡ ምስክርነቱንም ፈጽሞ የሰማዕትነት አክሊልን ተቀዳጀ።

በዚችም ቀን ፃን ከምትባል አገር የሆነ አባ ዮሴፍ አረፈ። ለዚህም ቅዱስ ወላጆቹ በሃይማኖት የበለጸጉ ናቸው ነገር ግን ያለርሱ ልጅ አልነበራቸውም የቤተ ክርስቲያንንም ትምህርት መጻሕፍት ማንበብንም እያስተማሩ መልካም አስተዳደግን አሳደጉት መልኩም እንደ ያዕቆብ ልጅ ዮሴፍ ያማረ ነበር በአደገም ጊዜ ሞትን የዚህንም ዓለም ኃለፊነት ማሰብ በልቡ አደረ።
ወደ አንድ ገዳምም ሒዶ መንኵሶ በጾም በጸሎት በመስገድ በተጋድሎ የተተከለ ሆኖ ጸና በአቱንም ዘግቶ በእለተ እሑድ ከቁርባን ጊዜ በቀር አይወጣም ነበር ። ዜናውም በተሰማ ጊዜ ከእርሱ በረከቱን ይቀበሉ ዘንድ በአገር ዙሪያ ያሉ ሰዎች የሚመጡ ሆኑ አባቱና እናቱም የልጃቸውን ወሬ በአጡ ጊዜ እርሱን ያገናኛቸው ዘንድ ወደ እግዚአብሔር እየለመኑ ነበር።
ወሬውንም በሰሙ ጊዜ ስለ ልጃቸው መገኘት እንዲጸልይላቸው ወደርሱ ሔዱ እርሱ ልጃቸው እንደሆነ አላወቁምና ሰውም ገለል ባለ ጊዜ ልጃቸው መሆኑን እራሱን ገለጠላቸውና ለማንም እንዳይናገሩ አዘዛቸው ።
እግዚአብሔርም ድንቆች ተአምራትን የማድረግ ሀብትን ሰጠው ሰይጣን እስከ ቀናበት ድረስ ወደ አገረ ገዢውም ሔዶ ይህ መነኵሴ ዮሴፍ ብዙ ገንዘብ እንዳለው አስመስሎ ነገር ስራበት ። መኰንኑም በሰንሰለት ማሰሪያዎች አሰረው። በማግሥቱም ማሰሪያዎቹ ከላዩ ወደ ምድር ወድቀው ተገኙ መኰንኑም አይቶ ደነገጠ ለቅድስናውም ተገዥ ሆነ ።
ብዙ ከተጋደለና እግዚአብሔርን ከአገለገለ በኋላ በሰላም አረፈ። በክብርም ቀበሩት ከመቃብሩም ቁጥር የሌላቸው ብዙ ተአምራት ተገለጡ።
ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።

No comments:

Post a Comment

Post Bottom Ad

Pages