ስንክሳር_ዘወርኀ_የካቲት 3 - አትሮንስ ሚዲያ - Atrons Media

አትሮንስ ሚዲያ - Atrons Media

ስብኩ ወንጌለ ለኩሉ ፍጥረት ማቴ 16፤15


በቅርብ የተጻፉ

Post Top Ad

Friday, March 3, 2023

ስንክሳር_ዘወርኀ_የካቲት 3

 አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም

የካቲት ሦስት በዚችም ቀን #የቅዱስ_ኤፍሬም የሥጋው ፍልሰት ሆነ፣ ተጋዳይ የሆነ #መነኰስ_አባ_ያዕቆብ አረፈ፣ የባሕታውያን አለቃ ኑሮው የመላእክትን ኑሮ የሚመስል የከበረ #ቅዱስ_አባት_አባ_ዕብሎይ አረፈ።


የካቲት ሦስት በዚችም ቀን የሶርያዊ ቅዱስ ኤፍሬም የሥጋው ፍልሰት ሆነ። ይህም ቅዱስ ከዋክብትን ከሚያመልኩ ሰዎች ሀገር ነው አባቱም ክብር ይግባውና የክርስቶስን አምልኮት የሚጠላ የጣዖት ካህን ነበር።
በዚያን ጊዜም የእግዚአብሔር ቸርነት ቀሰቀሰችውና አነሳሥታ የንጽቢን ጳጳስ ወደሆነው ወደ አባ ያዕቆብ ወሰደችው እርሱም የቤተ ክርስቲያንን ትምህርት አስተምሮ የክርስትና ጥምቀትን አጠመቀው በእርሱም ዘንድ በጾምና በጸሎት ያለማቋረጥ እየተጋደለ ለብዙ ዘመናት ኖረ።
የመንፈስ ቅዱስም ጸጋ አደረበት አሕዛብን ተከራክሮ ይረታቸው ነበር። ኒቅያ በሚባል ከተማ የሦስት መቶ ዐሥራ ስምንት አባቶች ኤጲስቆጶሳት ጉባኤ በተደረገ ጊዜ ይህ ቅዱስ ኤፍሬም ከመምህሩ ከአባ ያዕቆብ ጋራ ወደ ቅዱሳን ጉባኤው ሔደ።
ከሀዲው አርዮስንም አውግዘው ከለዩት በኋላ ይህ ቅዱስ ኤፍሬም በዚያች ሌሊት ከምድር እስከ ሰማይ የሚደርስ የብርሃን ምሰሶ ተተክሎ አየ ከዚህ ራእይም የተነሣ አደነቀ ይገልጽለትም ዘንድ ወደ ጌታ ጸለየ ይህ የቂሣርያ ሊቀ ጳጳሳት ብፁዕ ባስልዮስ ነው የሚል ቃል ከሰማይ ወደርሱ መጣ።
ቅዱስ ኤፍሬምም ያየው ዘንድ ወድዶ ወደ ቂሣርያ ሀገር ተጓዘ በደረሰም ጊዜ ወደ ቤተ ክርስቲያን ገብቶ በማእዘኑ በኩል ቆመ ቅዱስ ባስልዮስንም ወንጌልን ሊያነብ በወጣ ጊዜ ዋጋው ብዙ የሆነ ከወርቅ የተሠራ ልብሰ ተክህኖ ለብሶ አየው። ሦስት ምልክቶችንም እሰኪያይ ድረስ ተጠራጠረ ምልክቶችም እኒህ ናቸው ነጭ ርግብ መጥታ በራሱ ላይ አረፈች ሁለተኛም በልብሱ ላይ የሚያርፉ ተዋሐስያን ይቃጠሉና ይረግፉ ነበር። ሦስተኛም ከአፉ የእሳት ነበልባል ወጥቶ በምእመናን ላይ ያድር ነበር።
ከዚህም በኋላ ቅዱስ ባስልዮስ ቅዱስ ኤፍሬምን በስሙ ጠራውና እርስ በርሳቸው ሰላምታ ተለዋወጡ። በአስተርጓሚ ይነጋገሩ ጀመሩ። የየራሳቸውንም ቋንቋ ይገልጽላቸው ዘንድ ወደ እግዚአብሔር እንዲጸልይ ቅዱስ ኤፍሬም ቅዱስ ባስልዮስን ለመነው። በጸለየ ጊዜም ተገልጾላቸው ያለ አስተርጓሚ ተነጋገሩ።
ከዚህ በኋላም ቅዱስ ኤፍሬምን ዲቁና ሾመው ከጥቂት ወራትም በኋላ ቅስና ሾመው ከእርሱም ብዙ ትሩፋቶች ተገለጡ በመንፈሳዊ ተጋድሎ ሁሉ ተጋደለ። አንዲት በወገን የከበረች ባለ ጸጋ ሴት ነበረች ራስዋንም ለካህን ለማስመርመር ታፍር ነበር ከታናሽነቷ ጀምራ የሠራችውን ኃጢአቷን ሁሉ ጽፋ ወደ ቅዱስ ባስልዮስ አመጣች። አባቴ ሆይ በዚህ ክርታስ ውስጥ ያሉት ኃጢአቶቼ ይደመሰሱ ዘንድ ተናገር ብላ ለመነችው እርሱም እንዳልሺው ይሁንልሽ አላት፡፡
እርሷም ክርታሱን በገለጠች ጊዜ ከአንዲት ኃጢአትዋ በቀር ኃጢአቷ ሁሉ ተደምስሶ አገኘች ያችም ኃጢአት አስጨናቂና ታላቅ ኃጢአት ነበረች።
ባገኘቻትም ጊዜ ያቺን የቀረች ኃጢአቷን ያጠፋላት ዘንድ አልቅሳ ለመነችው እርሱም ወደ ቅዱስ ኤፍሬም ሒጂ እርሱ ይህችን የቀረች ኃጢአትሽን ያስተሠርይልሻል አላት። ወዲያውም ወደ ቅዱስ ኤፍሬም ሔዳ ከርሷ የሆነውን ሁሉ ነገረችው ። እርሱም እንዲህ አላት ፈጥነሽ ወደ ቅዱስ ባስልዮስ ሒጂ ግን ሙቶ ወደ ቤተ ክርስቲያን ሲወስዱት ታገኝዋለሽ ሳትጠራጠሪም ይህችን ክርታስ በላዩ ጣይ ይደመሰስልሻል።
ያቺም ሴት ወደ ቅዱስ ባስልዮስ ተመለሰች ሙቶ ተሸክመው ወደ ቤተ ክርስቲያን ሲወስዱትም አገኘችው ። ያንንም ክርታስ በአስክሬኑ ላይ ጣለችው ወዲያውኑም ተደመሰሰላት። ይህም ቅዱስ ኤፍሬም ብዙ ተአምራቶችን አድርጓል በዘመኑም ዲዳን የሚባል አንድ ከሀዲ ተነሣ ይህም አባት ኤፍሬም ተከራክሮ ረታው።
እጅግም ብዙ የሆኑ ዐሥራ አራት ሽህ ድርሳናትንና ተግሣጻትን ደረሰ ከእርሳቸውም ውስጥ አምላክን የወለደች የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ውዳሴዋ ነው ። አቤቱ የጸጋህን ማዕበል ግታልኝ እስከሚል ድረስ ድርሳናትን ደርሶአል ። መልካም የሆነ ገድሉንም በፈጸመ ጊዜ ወደ ወደደው ወደ እግዚአብሔር ሔደ።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
በዚህች ቀን ተጋዳይ የሆነ መነኰስ አባ ያዕቆብ አረፈ። ይህም ቅዱስ ከታናሽነቱ ጀምሮ ይህን ዓለም ትቶ መነኰሰና በአንዲት ዋሻ ውስጥ የሚኖር ሆነ ያለ ማቋረጥም በቀንና በሌሊት ሁልጊዜ ይጾማል ይጸልያል በመስገድም ይተጋ ነበር ከበዓቱም ወጥቶ ወደ መንደር አይገባም የሴት ፊትም አያይም እንዲህም ሁኖ ዐሥራ አምስት ዓመት ኖረ።
ከዚህም በኋላ ዲያብሎስን ከሚከተሉት ክፉዎች ሰዎች ውስጥ ምክንያት ፈጥረው አንዲቷን አመንዝራ ሴት ወደርሱ እንድትገባ አደረጓት በገባችም ጊዜ የኃጢአትን ሥራ እያስታወሰች በፊቱ መጫወት ጀመረች ቅዱስ ያዕቆብም ገሠጻት በገሀነም እሳትም ዘላለም ሲቃጠሉ መኖርን አሳሰባት ደንግጣም ንስሓ ገባች እግዚአብሔርንም የምታገለግል ሆነች።
ሰይጣንም መፈታተኑን አልተወውም ከሀገር ታላላቆችም በአንዱ ሰው በሴት ልጁ ላይ አደረ የሚጥላትና የሚያንከባልላት ሆነ ወደ አባ ያዕቆብም ይወስዳት ዘንድ እርሱም ሊያድናት እንደሚችል አሳሰበው አባቷም ወደ አባ ያዕቆብ አደረሳትና በላይዋ ይጸልይ ዘንድ ለመነው እርሱም በላይዋ ሲጸልይ ዳነች አባቷም ያ ሰይጣን እንዳይመለስባት ብሎ ከታናሽ ብላቴና ወንድሟ ጋር ከአባ ያዕቆብ ዘንድ ተዋት።
ከዚህም በኋላ ከእርሷ ጋር በኃጢአት እስከ ጣለው ድረስ እርሷን በማሳሰብ በሌሊትም በቀንም በዝሙት ጦር ሰይጣን ተዋጋው በኃጢአትም በወደቀ ጊዜ ስለ ርሷ እንደይገዱሉት ፈርቶ ኃጢአቱ እንዳይገለጥ ከወንድሟ ጋር ገደላት ሰይጣንም ደግሞ ቀቢጸ ተስፋ በልቡ አሳደረበት ወደ ዓለም ሊሔድ ከበዓቱ ወጣ።
የኃጢአተኛውን ሞት የማይወድ መሐሪ ይቅር ባይ እግዚአብሔርም። ጻድቅ የሆነ መነኰስ ወደርሱ ላከ በጐዳናው ሲጓዝ ተገናኘውና ሰላምታ ሰጠው እንዲህም ብሎ ጠየቀው ወንድሜ ሆይ ምን ሁነሃል አዝነህ ተክዘህ አይሃለሁና የደረሰብህስ ምንድን ነው። እርሱም የሆነውን ሁሉ ከዚያች ብላቴና ጋር በኃጢአት እንደ ወደቀና ከወንድሟ ጋር እንደገደላት ነገረው። ያ ጻድቅ መነኰስም አትፍራ ተስፋም አትቁረጥ እግዚአብሔር መሐሪ ይቅር ባይ ምሕረቱ የበዛ ነውና አለው። ከዚህም በኋላ የጾም የጸሎት የስግደት ቀኖናን እንዲይዝ አዘዘው።
እርሱም ተመልሶ ከአንድ ፍርኩታ ውስጥ ገባ በውስጡም ራሱን እሥረኛ አደረገ በታላቅ ድካምና በብዙ ችግርም ላይ ታገሠ በመጾም በመጸለይ አብዝቶ በመስገድም ሁልጊዜ ይተጋል ከምድር የሚበቅል ሥርንም የሚመገብ ሆነ አብዝቶ እያዘነ እግዚአብሔር ይቀበለኝ ብዙ በደሌንስ ይተውልኝ ይሆን ይላል እንዲህም በመጸጸት እየተጋደለ ሠላሳ ዓመት ኖረ።
እግዚአብሔርም ንስሓውን እንደተቀበለለት ሊገልጥ ወዶ በሀገር ውስጥ ረኃብን አመጣ ለዚያች አገር ኤጲስቆጶስም በፍርኩታ ውስጥ ከሚኖር ከመነኰስ ያዕቆብ ጸሎት በቀር ይህ ረኃብ አያልፍም አለው።
በዚያንም ጊዜ ኤጲስቆጶሱ ከእርሱ ጋር ካህናቱንና የዚያችን አገር ሰዎች ይዞ ተነሣ ወደ ቅዱስ ያዕቆብም ደርሰው ስለ ርሳቸው ይጸልይ ዘንድ ለመኑት እግዚአብሔር ይቅር እንዲላቸውና ዝናምንም እንዲአወርድላቸው አባ ያዕቆብም እኔ እግዚአብሔርን በኃጢአቴ ያሳዘንሁት ኃጢአተኛና በደለኛ ሰው ነኝ አላቸው ኤጲስቆጶሱም ስለርሱ እግዚአብሔር ያለውን ነገረው።
ከዚህም በኋላ ወደ ሕዝብ መካከል ወጣ እያለቀሰ ጸለየ እንዲህም አለ አቤቱ በጌትነትህ ክብር ፊት የረከሰች እፌን እንዴት እገልጣለሁ በኃጢአት ብዛት የጠቆረ ፊቴንስ እንዴት ቀና አደርጋለሁ ነገር ግን እንደ ይቅርታህ ገናናነት እንደ ቸርነትህም ብዛት ሕዝብህን ይቅር በል አንተ መሐሪና ይቅር ባይ ነህና በዚያንም ጊዜ ብዙ ዝናም ወረደ እርሱም ጸሎቱንና ንስሓውን እግዚአብሔር እንደ ተቀበለው ኃጢአቱንም እንደ ተወለት አወቀ።
ከዚህም በኋላ አስቀድሞ እንደሚሠራው ተግቶ መጸለዩንና መሰገዱን አላጐደለም ነፍሱንም ዳግመኛ በኃጢአት ውስጥ እንዳትወድቂ ተጠበቂ በማለት ይገሥጻት ነበር ከዚህም በኋላ ዕድሜውን አድርሶ እግዚአብሔርንም አገልገሎ በሰላም አረፈ።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#ቅዱስ_አባ_ዕብሎይ_ገዳማዊ (የባሕታውያን አለቃ)
በዚህችም ዕለት የባሕታውያን አለቃ ኑሮው የመላእክትን ኑሮ የሚመስል ከትሩፋቱም የሃይማኖት ፍሬ የተገኘ የከበረ አባት ዕብሎይ አረፈ።
ቅዱስ አትናቴዎስም ከተሰደደበት በተመለሰ ጊዜ ወደ ቂሣርያ ኤጲስቆጶስ ወደ አባ ባስልዮስ ዘንድ መጥቶ ሁለቱም በአቡቂር ቤተ ክርስቲያን አደሩ በግብጽ ገዳማት ስለሚኖሩ ቅዱሳን እርስ በርሳቸው ሊነጋገሩ ጀመሩ አባት ሊቀ ጳጳሳት አትናቴዎስ አባ ጳኵሚስ አለ ብሎ ተናገረ አባ ባስልዮስም አባ እንጦንዮስና አባ አሞኒ አሉ አለ በእንዲህ ያለ ነገርም ከእርሳቸው የሚልቀውን ሊረዱ ሽተው ሳሉ የካቲት አምስት ቀን በመንፈቀ ሌሊት አባ አትናቴዎስ ራዕይን አየ።
እስከ ሰማይ የምትደርስ ታላቅ ዛፍ ነበረች ቅርንጫፎቿም እስከ ባሕር ደርሰዋል ብዙ ሰዎችም ከቅርንጫፎቿ በታች ተጠልለዋል በመካከሏም ታቦት መሠዊያ አለ ከዚህም ራእይ የተነሣ እየተደነቀ ሳለ እነሆ የመላእክት አለቃ የከበረ ሚካኤል ከሰማይ ወርዶ ይህን ያየኸውን ከባስልዮስ ጋር ተነጋገር እኔም እገልጥላችኋለሁ አለው።
እንዲህ ብሎ ተረጐመላቸው ያየሃት ዛፍ በግብጽ አውራጃዎች ውስጥ የሚሠራ ገዳም ነው ቅርንጫፎቿም መነኰሳት ናቸው መሠዊያውም መላእክት የሚጐበኙት የእግዚአብሔር ማደሪያ ይህ ርኵሳን መናፍስትን የሚሽር የሐዋርያት አለቃ የጴጥሮስ አምሳል የሆነ አባ ዕብሎይ ነው።
በእስክንድርያ የሚኖር አንድ የመቶ አለቃ የአባ ዕብሎይን ዜና ሰምቶ በረከቱን ይቀበል ዘንድ ወደ አባ ዕብሎይ እንዲልከው ሊቀ ጳጳሳት አትናቴዎስን ማለደው። እርሱም ከሰባት መነኰሳት ጋር ሰደደው እነርሱም አባ ኤስድሮስ፣ አባ ዮሐንስ፣ አባ ብሶይ፣ አባ አሞኒ፣ አባ ፊቅጦር፣ አባ አግሮኒኮስና አባ ካሉናስ ናቸው። በደረሱም ጊዜ አባ ዕብሎይ በደስታ ተቀበላቸው ከመነኰሳቱም ጋር የመጣው የመቶ አለቃ አንዲቷ ዐይኑ የታወረች ናት አባ ዕብሎይን በተሣለመው ጊዜ ዐይኑ ተከፈተች እርሱም በዓለም የሚያበራ ኮከብ ብሎ ተናገረ።
ዳግመኛም አባ ዕብሎይን ለመነው እንዲህም አለው ሚስቴ በለምጽ ደዌ ትጨነቃለች እርሷም በአስኬማህ የተማጸነች ናት እኔ ያገኘሁት ጸጋህ ለርሷም ይድረሳት። አባ ዕብሎይም በክብር ባለቤትም ጌታችን ስም ፈውስ ይሁንላት አለ ይህም ቃል ከአፉ እንደወጣ ድና ጤንነትን አገኘች።
በአንዲትም ዕለት አባ ዕብሎይ ከመነኰሳት መካከል ቁሞ ቤተ ክርስቲያን የምትሠራበትን ያስገነዝበን ዘንድ መድኃኒታችን ክርስቶስ ከደቀ መዛሙርቱ ጋር ይመጣልና አንዱም አንዱ ከእናንተ አይሒድ ከዚህ ይኑር እንጂ አላቸው።
ያን ጊዜም በዚያ ቦታ ብርሃን ወጣ የክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከከበሩ ደቀ መዛሙርቱና ከመላእክቶቹ ጋር መጣ የቤተ ክርስቲያኒቱ ሕንፃዋ የሚመሠረትበትንም አሳያቸው።
እርሱም ሥራ ሁሉ ፍጹማን ይሆኑ ዘንድ ፍቅርንም ያጸኑ ዘንድ ልጆቹን ይመክራቸው ነበር እየመከራቸውም ፊቱ ተለውጦ እንደ እግዚአብሔር መልአክ ፊት ሆነ ሁለመናውም እንደሚነድ እሳት ሆነ እነርሱም ፈሩ። እርሱም ልጆቼ አትፍሩ እነሆ እኔ እሰናበታችኋለሁ አላቸው። ይህንንም ብሎ ነፍሱ ተመሠጠች በጎ መዓዛም ሸተተ ወዲያውኑ ዐይኑ ተገለጠና ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ርዳኝ ነፍሴንም ወዳንተ ተቀበል አለ ይህንንም ብሎ አረፈ። የቀረውም ዜናው በጥቅምት ሃያ አምስት ቀን ተጽፎአል።
ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።

No comments:

Post a Comment

Post Bottom Ad

Pages