ስንክሳር ዘወርኀ ግንቦት 21 - አትሮንስ ሚዲያ - Atrons Media

አትሮንስ ሚዲያ - Atrons Media

ስብኩ ወንጌለ ለኩሉ ፍጥረት ማቴ 16፤15


በቅርብ የተጻፉ

Post Top Ad

Tuesday, June 6, 2023

ስንክሳር ዘወርኀ ግንቦት 21

 አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም

ግንቦት ሃያ አንድ በዚች ዕለት አምላክን የወለደች እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም በደብረ ምጥማቅ በስሟ በተሠራች ቤተ ክርስቲያን ጉልላት ላይ በብርሃን መርከብ ተቀምጣ ፊቷ በግልጥ ታየች፣ የከበረ አባት ባ መርትያኖስ አረፈ፣ ከልጅነቱ ጀምሮ ተጋዳይ የሆነ ባ አሮን ሶርያዊ አረፈ፣ ከዐሥራ ሁለቱ ደቂቀ ነቢያት አንዱ ቅዱስ አሞጽ ነቢይ መታሰቢያው ነው።


ደብረ ምጥማቅ
ግንቦት ሃያ አንድ በዚች ዕለት አምላክን የወለደች እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም በደብረ ምጥማቅ በስሟ በተሠራች ቤተ ክርስቲያን ጉልላት ላይ በብርሃን መርከብ ተቀምጣ ፊቷ በግልጥ ስለመታየቱ የክርስቲያን ወገኖች ሁሉም ታላቅ በዓልን ያደርጋሉ።
እርሷም በልጅዋ የመለኮት ብርሃን የተጐናጸፈች ናት በዙሪያዋም የመላእክት ሠራዊት የመላእክት አለቆችም በየማዕረጋቸው ክንፋቸውን ዘርግተው ይቆሙ ነበር ይጋርዷታልም። ሱራፌልም ማዕጠንታቸውን ይዘው ለንግሥዋ ገናናነት ይሰግዳሉ በየስግደታቸውም እንዲህ እያሉ ያመሰግኗታል። አብ በሰማይ ሁኖ ተመለከተ እንደ አንቺ ያለ አላገኘም አንድ ልጁንም ልኮ ከአንቺ ሰው ሆነ።
ሁለተኛ ሰማዕታትም በየማዕርጋቸው ረቂቃን በሆኑ ፈረሶቻቸው ተቀምጠው እየመጡ መጀመሪያ ቅዱስ ጊዮርጊስ ከአምባላይ ፈረሱ ወርዶ ይሰግድላታል እንዲሁም ባልንጀሮቹ ሰማዕታት መጥተው ይሰግዱላታል ።
ከእርሱ በኋላ የሚመጣው በዱሪ ፈረስ የሚቀመጥ ይህ መርቆሬዎስ ነው። ከዚህም በኋላ ሰማዕታት ሁሉ በመከታተል መጥተው ይሰግዱላታል ምስጋናም ያቀርቡላታል። ሁለተኛም ደግሞ የጻድቃን አንድነታቸው መጥተው በፊቷ ሰግደው ይመላለሳሉ።
ሄሮድስ የገደላቸው ሕፃናትም መጥተው ይሰግዱላታል በፊቷም እየዘለሉ አንዱ በአንዱ ላይ እየዘለለ በመተቃቀፍም ይጫወታሉ የተሰበሰቡትም በአዩ ጊዜ ደስታ ይመላባቸዋል በሰማይም ያሉ ይመስላቸው ነበር።
እናትና አባቱም የሞቱበት ቢኖር ወይም ከዘመዶቹ ወይም ባልንጀራዉ ቅድስት ድንግል እመቤቴ ሆይ ዕገሌን አሳዪኝ ብሎ በሚለምናት ጊዜ ቀድሞ በነበረበት መልኩ ያን ጊዜ ታመጣዋለች። ደግሞ መሀረባቸውን ወደላይ ይወረውሩላታል የወደደችውንም በእጇ ተቀብላ መልሳ ትጥልላቸዋለች ለበረከትም በየጥቂቱ ይካፈሉታል።
እንዲህም አምስት ቀን ሁሉ ክርስቲያንም እስላሞችም አረማውያንም ያይዋታል። ወደ ቤታቸውም ለመሔድ ሲሹ በፊቷ ሰግደው ይሰናበቷታል እርሷም ትባርካቸውና ይመለሳሉ።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
አባ መርትያኖስ
በዚህችም ዕለት የከበረ አባት አባ መርትያኖስ አረፈ። ይህም አባት በልጅነቱ ከአንድ ቅዱስ የሆነ አረጋዊ አባት ዘንድ መንኵሶ ታላቅ ገድልን ተጋደለ። ከዚህም በኋላ ሐመረ ኖኅ ወደምትባል በቂሣርያ ወደአለች ገዳም ሔደ በዚያም እጅግ በጣም የበዛ ገድልን ተጋደለ።
በጸሎት በጾም በስግደትም በሌሊትና በመዓልት በመትጋት እየተጋደለ ስድሳ ሰባት ዓመት በኖረ ጊዜ የገድሉና የትሩፋቱ ወሬ በቦታው ሁሉ ተሰማ ። እነሆ አንዲት በክፉ ሥራዋና በዝሙቷ የታወቀች ኃጢአተኛ አመንዝራ ሴት ሰማች። ጽድቁንና ቅድስናውን በመናገር የሚያመሰግኑትን እንዲህ አለቻቸው።እናንተ ታመሰግኑታላችሁ እርሱ የሚኖረው በዱር ነው የሴት ገጽ ከቶ አያይም እኔን ቢያይ ድንግልናውን አጥፍቼ ቅዱስናውን በአረከስኩት ትኀርምቱንም ባፈረስኩት ነበር። እነርሱ ግን ጥንክርናውን ስለ ሚያውቁ ተከራከሩዋት።
ስለዚህም በመካከላቸው ክርክር ሆነ ሔጄ ከእኔ ጋራ በኃጢአት ብጥለው ምን ትሰጡኛላችሁ አለቻቸውና ገንዘብ ሊሰጡአት ተስማሙ። ያን ጊዜም ተነሥታ ጌጦቿን ልብሶቿንና ሽቱዎቿን ያዘች መልኳም እጅግ ውብ ነበረች ፊቷንም ተከናንባ ጨርቅ ለብሳ ወደ በዓቱ ሔደች። ልብሷንና ጌጦቿንም ለብቻቸው በከረጢት አሥራ ያዘች። ከበዓቱም ቅርብ በሆነ ቦታ ተሠውራ እስከ ሚመሽ ቆይታ የበዓቱን ደጃፍ አንኳኳች። አራዊት እንዲበሉኝ በውጭ አትተወኝ እኔ መጻተኛ ነኝና መንገድንም ተሳስቼ ወደዚህ ደረስኩ አለችው። እርሱም በልቡ አሰበ በውጭ ብተዋት አራዊት ይበሏታል ባስገባትም ስለርስዋ ጦር በኔ ላይ ይነሣብኛል አለ።
ከዚህም በኋላ ከፈተላት በዚያችም በዓት ውስጥ ትቷት ወደ ሌላ ቦታ ፈቀቅ አለ። እርሷ ግን ልብሶቿን ለብሳ ጌጦቿንም ተሸልማ ሽቱዎቿን ተቀብታ ወደርሱ ገባች ከርሷ ጋርም እንዲተኛ ፈልጋ ከዚህ ማንም የሚያየን የለም አለችው።
ቅዱሱም የሰይጣን ማጥመጃው እንደሆነች አውቆ ጥቂት ታገሺኝ መንገድን እስታይ እግዚአብሔርን የማንፈራው ከሆነ እንደእኛ ያሉ ሰዎችን ላንፈራቸው ይገባናል አላት። ይህንንም ብሎ ከእርሷ ዘንድ ወጣ ታላቅ እሳትም እንድዶ እግሩን ከውስጡ ጨመረ ነፍሱንም የሲኦልን እሳት የምትችዪ ከሆንሽ ኃጢአትን ሥሪያ አላት።
በዘገየ ጊዜ ወደርሱ ሔደች በእሳት ውስጥም እግሩን ሲያቃጥል አይታው እጅግ ደነገጠች። ከእሳትም ውስጥ ጐትታ አወጣችው ልቧም ወደ ንስሓ ተመለሰ። ልብሷንና ጌጦቿን ከላይዋ አውጥታ ጣለች ከእግሩ በታች ሰገደች ስለነፍሷ ድኅነትም እንዲረዳት ለመነችው።
እርሱም ይህ ዓለም ፍላጎቱ ሁሉ ኀላፊ እንደ ሆነ ያስተምራትና ይመክራት ልብ ያስደርጋትም ጀመር እርሷም በጨከነ ልብ ንስሓ ገባች። ከዚህም በኋላ በአንድነት መኖር አግባብ አይደለም ብሎ ወደ ደናግል ገዳም ወሰዳት ትጠብቃትም ዘንድ እመ ምኔቷን አደራ አላት። በቀረው ዕድሜዋም በገድል ተጠምዳ እግዚአብሔርን አገለገለችው ወደ በጎ ሽምግልናም ደረሰች የመፈወስ ሀብትም አድሮባት ብዙዎች በሽተኞችን አዳነች።
የከበረ አባ መርትያኖስ ግን ሌላ ሴት እንዳያመጣበት ፈርቶ በባሕር መካከል ወዳለች ደሴት ገብቶ በዚያ የሚኖር ሆነ። አንድ ባለ ታንኳም የእጅ ሥራውን እየሸጠ ምግቡን ያመጣለት ነበር። ከብዙ ዘመናትም በኋላ መርከብ ተሰብራ ሰጠመች አንዲት ሴትም በመርከብ ስባሪ ተጣብቃ አባ መርትያኖስ ወደ አለበት ደሴት የባሕሩ ማዕበል አደረሳት በአያትም ጊዜ ደነገጠ አደነቀም። ከእርሷ ጋር በአንድነት ስለ መኖሩም አዘነ የእግዚአብሔርንም ቃል አስተምሮ የምንኲስና ልብስ አለበሳት ምግቧንም አዘጋጀላትና ለእኛ በአንድነት መኖር አግባብ አይደለም አላት። ያንንም ደሴት ትቶላት ወደ ባሕሩ ተወርውሮ ገባ አንበሪም ተሸክሞ ወደ የብስ አወጣው።
መቶ ስምንት አገሮችንም እስቲአዳርስ በአገሮች በአሉ ገዳማት ሁሉ ከዚያች ቀን ጀምሮ የሚዞር ሆነ በአንድ ቦታ እንዳይቀመጥ አስቦ ነው። ከዚህ በኋላም የዕረፍቱ ጊዜ እንደ ቀረበ አውቆ በበዓት ውስጥ ራሱን እሥረኛ አደረገ። ኤጲስቆጶሱንም ጠርቶ ከመጀመሪያ እስከ መጨረሻ ገድሉን ሁሉ ነገረው ኤጲስቆጶሱም ከጸጋው ገናናነት የተነሣ አደነቀ።
ከዚህም አስቀድሞ የእግዚአብሔር መልአክ ለኤጲስቆጶሱ ስለአባ መርትያኖስ ሥጋ እንዲአስብ ነግሮት ነበር። ከዚህም በኋላ ነፍሱን በእግዚአብሔር እጅ ሰጠ ኤጲስቆጶሱም በታላቅ ክብር ገንዞ ቀበረው።
ያቺን ሴት ግን እስከ ዕረፍቷ ቀን ባለ መርከብ የሚጎበኛት ሆነ በአረፈችም ጊዜ ሥጋዋ እንደ በረዶ ነጥቶ አገኛት ሥጋዋንም ወደ ሀገሩ ተሸክሞ ወስዶ ቀበራት።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
ቅዱስ አሮን ሶርያዊ
በዚችም ዕለት ከልጅነቱ ጀምሮ ተጋዳይ የሆነ አባ አሮን ሶርያዊ አረፈ። ለዚህ ቅዱስም የመፈወስና ድንቆች ተአምራትን የማድረግ ሀብት ተሰጥቶታል። ይኸውም እንግዶች መነኰሳት ወደ ርሱ በመጡ ጊዜ የርግብ ግልገሎችን አብስሎ አቀረበላቸው።
ሥጋ አንበላም ባሉት ጊዜ በላያቸው አማትቦ ርግቦቹን አድኖ እንዲበሩ አደረጋቸው። ደግሞ በተራራ ላይ ገዳም ሠራ ውኃው ከተራራው በታች የራቀ ነበረ በጸለየና በእጁ ባማተበ ጊዜ ስቦ ከተራራው ላይ አወጣው።
በአንዲት ቀንም ሰይጣን በክፋቱ ሊአጠፋው ወደርሱ መጣ እርሱ ግን በላዩ በአደረ መንፈስ ቅዱስ ተንኰሉን አውቆ ና ወደ በዓት ግባ አለው። በገባ ጊዜም በላዩ ዋሻውን ደፈነው ታላቅ የቋጥኝ ደንጊያም ጫነበት ሰይጣንም አፈረ።
ደግሞም ሁለተኛ የአካ አገረ ገዥ በሞተ ጊዜ በጸሎቱ አስነሣው። ደግሞ ውኃ የሚቀዳባቸውን አራት እንስራዎችን በአንበሳ እየጫነ በመውሰድ ዐሥር ዓመት ያህል ኖረ።
ከዚህ በኋላም ወደ ዘላለም ሕይወት ሔደ። ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በከበረች ጸሎቱ ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
ቅዱስ አሞጽ ነቢይ
በዚችም ቀን ከዐሥራ ሁለቱ ደቂቀ ነቢያት አንዱ አሞጽ ነቢይ መታሰቢያው ነው። አሞጽ ማለት "እግዚአብሔር ጽኑዓ ባሕርይ ነው: አንድም እግዚአብሔር ያጸናል::" ማለት ነው:: "ተወዳጅ ሰው" ተብሎም ይተረጐማል:: የነበረውም ቅድመ ልደተ ክርስቶስ በስምንት መቶ ዓመት ሲሆን አባቱ ቴና እናቱ ሜስታ ይባላሉ:: ትውልዱም ከነገደ ስምዖን ነው:: በትውፊት ይህ ነቢይ የነቢዩ ኢሳይያስ አባት ነው የሚሉ ቢኖሩም ሁለቱ አሞጾች የተለያዩ መሆናቸውን ሊቃውንት ይናገራሉ::
ይህ ዕውነተኛ ነቢይ በእስራኤል ነገሥታት በኢዮአስና በኦዝያ ዘመን አስተማረ የእስራኤልንም ልጆች የእስራኤልንና የይሁዳንም ነገሥታት ይገሥጻቸው ነበር ።
ስለ ክብር ባለቤት ስለ መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ መከራ ስለመቀበሉ በዚያችም ቀን ስለ ፀሐይ መጨለም ከዚያም በኋላ እስራኤልን ስለሚደርስባቸው መከራ፣ ኀዘን፣ ልቅሶ፣ ረድኤትም እንደሚአጡ፣ የእግዚአብሔርንም ቃል መስማትን ከማጣት የተነሣ እንደሚራቡና እንደሚጠሙ። በሀገሩ ሁሉ በአሕዛብም መካከል እንደሚበተኑ አሕዛብም እንደ አጃ ሸክሽከው እንደሚአጓልቧቸው ትንቢትን ተናገረ ትንቢቱም በላያቸው ተፈጸመ።
ቅዱሱ ነቢይ ወገኖቹን አብዝቶ ይገስጻቸው ነበር፤ ስለኃጢአታቸውና ስለ ክፉ ሥራቸው፣ ስለ ዘለፋቸው እነርሱ እንደ ገደሉት ተነገረ። የትንቢቱም ዘመን ከጌታችን ሥጋዌ በፊት በስምንት መቶ ዓመት ነው ።
ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን ለአባት እናቶቻችን የተገለጠች እመቤታችን ለእኛም በረድኤት ትገለጽልን:: ጣዕመ ስሟ በአንደበታችን: ጣዕመ ፍቅሯ በልባችን ይደርብን አሜን::
ምንጭ፤ ስንክሳር ዘወርኀ ግንቦት

No comments:

Post a Comment

Post Bottom Ad

Pages