ስንክሳር ዘወርኀ ሰኔ 24 - አትሮንስ ሚዲያ - Atrons Media

አትሮንስ ሚዲያ - Atrons Media

ስብኩ ወንጌለ ለኩሉ ፍጥረት ማቴ 16፤15


በቅርብ የተጻፉ

Post Top Ad

Monday, July 3, 2023

ስንክሳር ዘወርኀ ሰኔ 24

 አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም



ሰኔ ሃያ አራት በዚች ቀን አባ ሙሴ ጸሊም በሰማዕትነት ሞተ። ሰዎች ከገድሉ የተነሣ ይህን ቅዱስ ያደንቁታል እርሱ አስቀድሞ መንግሥተ ሰማያትን ገፍቷት ነበረና እርሱ በሥጋው ጠንካራ በሥራውም ኃይለኛ ነበር ይበላና ይጠጣ ይቀማና ያመነዝር ነበር ይገድልም ነበር ማንም ሊቋቋመው አይችልም ነበር።
አንድ በግ በአንድ ጊዜ ጨርሶ እንደሚበላና አንድ ፊቀን ወይን ጠጅ እንደሚጠጣ ስለ እርሱ ተነግሮአል። እርሱም ፀሐይን ለሚያመልኩ ሰዎች አገልጋይ ነበረ ብዙ ጊዜም ወደ ፀሐይ እያንጋጠጠ ፀሐይ ሆይ አንተ አምላክ ከሆንክ አነጋግረኝ ይል ነበር ደግሞም በልቡ የማላውቅህ ሆይ ራስህን አሳውቀኝ ይል ነበር።
ከዚህም በኋላ በአስቄጥስ ገዳም ያሉ መነኰሳት እግዚአብሔርን ያውቁታል ያዩታልም እያሉ ሲነጋገሩ ሰዎችን ሰማቸው። ያን ጊዜም ተነሣ ሰይፉንም ታጥቆ ወደ አስቄጥስ ገዳም ሔደ በደረሰም ጊዜ አባ ኤስድሮስን አገኘው። አባ ኤስድሮስም ፈራው ሙሴ ጸሊምም እውነተኛውን አምላክ ታሳውቁኝና ታስረዱኝ ዘንድ ወደ እናንተ መጣሁ አለው። አባ ኤስድሮስም ወደ አባ መቃርስ ወስዶ አገናኘው።
እርሱም ተቀብሎ ሃይማኖትን አስተማረው እንዲህም አለው ታግሠህ የማስተምርህን ከጠበቅህ እግዚአብሔርን ታየዋለህ። ከዚህም በኋላ የክርስትና ጥምቀትን አጥምቆ አመነኰሰው ከብዙዎች ገድለኞች ቅዱሳን ይልቅ ብዙና ጽኑዕ ገድልን መጋደል ጀመረ።
ሰይጣንም ቀድሞ ሲሠራው በነበረ በመብሉና በመጠጡ በዝሙቱም ይዋጋው ነበረ እርሱም በራሱ ላይ የሚደርስበትን ሁሉ ለአባ ኤስድሮስ ይነግረው ነበር እርሱም አጽናንቶ ሊሠራው የሚገባውን ያስተምረው ነበር።
ከገድሉ ብዛትም የተነሣ አረጋውያን መነኰሳት በሚተኙ ጊዜ ቤቶቻቸውን በመዞር ውኃ መቅጃዎችን ወስዶ ውኃ መልቶ በየቤታቸው ደጃፍ ያኖር ነበር። ውኃው ከእነርሱ ሩቅ ነበረና እንዲህም እያደረገ በመጋደል ለብዙ ዘመናት ኖረ።
ሰይጣንም በእርሱ ቀንቶ በእግሩ ውስጥ አስጨናቂ የሆነ አመታትን መታው ተኝቶም እየተጨነቀ ብዙ ቀን ታመመ። ከዚህም በኋላ የመታውና የሚፈታተነው ሰይጣን እንደሆነ ዐውቆ ሥጋው በእሳት ተለብልቦ እንደ ደረቀ ዕንጨት እስቲሆን ድረስ ተጋድሎውንና አገልግሎቱን አበዛ። እግዚአብሔርም ትዕግስቱን አይቶ ከደዌው ፈወሰው የሰይጣንንም ጦር ከእርሱ አራቀለት የመንፈስ ቅዱስም ጸጋ አደረበት ወደርሱም አምስት መቶ ወንድሞች መነኰሳት ተሰበሰቡ በእነርሱም ላይ አበ ምኔት ሆነ።
ከዚህ በኋላ ቅስና ሊሾሙት መረጡት በቤተ መቅደስም በሊቀ ጳጳሳቱ ዘንድ በአቆሙት ጊዜ ሊቀ ጳጳሳቱም አልፈቀደም ነበር አረጋውያኑንም ይህን ጠቋራ ለምን አመጣችሁት ከዚህ አውጡት አላቸው እርሱም መልክህ የከፋ ጠቋራ ሆይ መልካም አደረጉብህ በማለት ራሱን እየገሠጸ ወጣ ከዚህ በኋላ ዳግመኛ ሊቀ ጳጳሳቱ ጠራውና እጁን በላዩ ጭኖ ቅስና ሾመው እንዲህም አለው ሙሴ ሆይ እነሆ በውስጥም በውጭም ሁለመናህ ነጭ ሆነ።
በአንዲትም ዕለት ቅዱሳን አረጋውያን ወደርሱ መጡ በእርሱም ዘንድ ውኃ አልነበረም እርሱም ከበዓቱ ብዙ ጊዜ ወጣ ገባ ይል ነበር ከዚህ በኋላም ብዙ ዝናም ዘንሞ ጕድጓዶችን ሁሉ ሞላ። አረጋውያንም ለምን ብዙ ጊዜ ወጣ ገባ ትል ነበር ብለው ጠየቁት እርሱም እግዚአብሔርን ውኃ ካልሰጠኸኝ ቅዱሳን አገልጋዮችህን ምን አጠጣቸዋለሁ እለው ነበር በቸርነቱም ዝናምን ልኮልን ውኃን አገኘን አላቸው።
በአንዲትም ዕለት አባ ሙሴ ከአረጋውያን ጋራ ወደ አባ መቃርስ ሔደ አባ መቃርስም የሰማዕትነት አክሊል ያለው ከእናንተ ውስጥ አንዱን እነሆ አያለሁ አላቸው አባ ሙሴም አባቴ ሆይ ምናልባት እኔ እሆናለሁ በሰይፍ የገደለ በሰይፍ ይገደል ዘንድ አለው የሚል ጽሑፍ አለና ብሎ መለሰ።
ከዚህም በኋላ የበርበር ሰዎች መጡ አባ ሙሴም ከእርሱ ጋራ ያሉትን መነኰሳት እነሆ የበርበር ሰዎች ደረሱ መሸሽ የሚፈልግ ይሽሽ አላቸው እነርሱም አባታችን አንተስ አትሸሽምን አሉት እርሱም በሰይፍ የገደለ በሰይፍ ይገደላል ስለሚለው የእግዚአብሔር ቃል እነሆ ያቺን ቀን ለብዙ ዘመናት ስጠብቃት ኖሬአለሁ አላቸው።
ወዲያውኑም የበርበር ሰዎች ገብተው በሰይፍ ገደሉት መሸሽ ስለ አልፈለጉ ከእርሱ ጋራ ሰባት መነኰሳትም ተገደሉ አንዱ ግን ከምንጣፍ ውስጥ ተሠወረ የእግዚአብሔርንም መልአክ አየ በእጁም አክሊል ነበር እርሱም ቆሞ ይጠብቅ ነበር። ይህንንም በአየ ጊዜ ከተሠወረበት ወጣ የበርበር ሰዎችም ገደሉት የሰማዕትነትንም አክሊል ተቀበለ።
ወንድሞች ሆይ ከሀዲና ነፍሰ ገዳይ ቀማኛና ዘማዊ የነበረውን ለውጣ ደግ አባት መምህርና የሚያጽናና ለመነኰሳትም ሥርዓትን የሠራ ካህን እንዳደረገችው በሁሉም አብያተ ክርስቲያን ስሙ እንዲጠራ እንዳደረገችው የንስሐን ኃይሏን ተመልከቱ። ሥጋውም በአስቄጥስ ገዳም ደርምስ በተባለ ቦታ ለዘላለም ይኖራል ከእርሱም ብዙዎች ድንቆችና ተአምራት ይታያሉ።
ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን።
ምንጭ፤ ስንክሳር ዘወርኀ ሰኔ

No comments:

Post a Comment

Post Bottom Ad

Pages