‹‹ጥንተ ስቅለት›› - አትሮንስ ሚዲያ - Atrons Media

አትሮንስ ሚዲያ - Atrons Media

ስብኩ ወንጌለ ለኩሉ ፍጥረት ማቴ 16፤15


በቅርብ የተጻፉ

Post Top Ad

Thursday, April 16, 2020

‹‹ጥንተ ስቅለት››


 

 የዓለም መድኅን ኢየሱስ ክርስቶስ ከቅድስተ ቅዱሳን ድንግል ማርያም በነሣው ሥጋ በቀራንዮ መስቀል ላይ ተሰቅሎ ሕይወቱን ለዓለም ቤዛ፣ አድርጎ የሰጠው መጋቢት ፳፯ ቀን ፴፫ ዓ.ም እንደሆነ ይታወቃል፡፡
ይህ ቀን ስለክርስቶስ ሕማም፣ ስለመከራ መስቀሉና ስለሞቱ የተነገሩት ትንቢቶችና ምሳሌዎች ሁሉ የተፈጸሙበት፤ ሰማያዊ አምላክ ስለሰው ልጆች ፍቅር ሲል ልዩ ልዩ ጸዋትወ መከራዎችን የተቀበለበትና በሞቱ ሞትን ሽሮ የአዳምን ዘር ሁሉ ከሞት ሞት ያዳነበት፣ ለዓለሙ ሁሉ ፍቅሩን የገለጠበት፣ በመስቀል ላይ ባፈሰሰው ደሙም ዓለምን ነፃ ያወጣበት፣ በአጠቃላይ ዐሥራ ሦስቱን ሕማማተ መስቀል በትዕግሥት ተቀብሎ ቅድስት ነፍሱን ከቅዱስ ሥጋው በገዛ ፈቃዱ የለየበት የስቅለቱና የሞቱ መታሰቢያ የሚከበርበት ቀን በመሆኑ ጥንተ ስቅለት ተብሎ ይጠራል፡፡
በዓሉም በዓለ መድኃኔዓለም እየተባለ በየዓመቱ በመድኃኔዓለም ስም በታነጹ አብያተ ክርስቲያናት ሁሉ ታቦተ ሕጉ እየወጣና ዑደትም እየተደረገ በታላቅ ክብር ሲከበር የኖረ ታላቅ መንፈሳዊ በዓል ነው፡፡
መድኃኔዓለም ማለት ምን ማለት ነው? ክርስቶስ፣ ማለት መሲህ፤ ኢየሱስ ማለት መድኃኒት፣ አማኑኤል ማለትም እግዚአብሔር ከእኛ ጋር ነው ተብሎ እንደሚተረጎም ሁሉ መድኃኔዓለም ማለትም ዓለምን ሁሉ የሚያድን የዓለም መድኃኒት ማለት እንደሆነ ከቅዱሳት መጻሕፍት እንማራለን፡፡
ዓለም የዳነውም ከላይ እንደተገለጠው በመስቀሉ ላይ በአፈሰሰው ደሙና በሞቱ አማካይነት በተገኘው ጸጋ ነውና የጥንተ ስቅለቱና የመስቀሉም ምሥጢር ዓለምን የማዳን ምስጢር ስለሆነ የጥንተ ስቅለቱ የመታሰቢያ በዓል በሚከበርበት በመጋቢት ፳፯ ቀን ምእመናን ሁሉ በቤተክርስቲያን በመገኘት በእሱ ደም ዓለም የዳነ መሆኑን በሚገልጠው መድኃኔዓለም በተሰኘው ስሙ እየተማጸኑና ዓለምን ለማዳን የተቀበለውን መከራ መስቀል እያስታወሱ በዓሉን በድምቀት ያከብሩታል፡፡
መድኃኔዓለም የሚለው የጌታችን ስም ቃሉ ራሱ የድኅነት ወይም የመዳን ቃል እንደሆነ በምሥጢር የሚያስረዱት ቅዱሳት መጻሕፍት ብዙዎች ናቸው ከእነዚህም መካከል፡ –
፩ኛ. ‹‹እግዚአብሔርሰ ንጉሥ ውእቱ እምቅድመ ዓለም ወገብረ መድኃኒተ በማዕከለ ምድር›› ‹‹እግዚአብሔር ዓለም ከመፈጠሩና ከተፈጠረም በኋላ ዘለዓለማዊ ንጉሥ ነው፡፡ የምድር ማዕከል በሆነች ቀራንዮም መድኃኒትን አደረገ›› የሚለው የነቢዩ ዳዊት ትንቢት አንደኛው ማስረጃ ነው (መዝ. ፸፫ ፥ ፲፬)፡፡
፪ኛ. ቅዱስ ሊቃስ እንደ ጻፈው ክርስቶስ በተወለደበት ሌሊት የጌታችን ክብር በዙሪያቸው ሲያበራ ያዩ እረኞች ታላቅ ፍርሃትን ከመፍራታቸው የተነሣ፤ ሰማያዊ መልአክ ‹‹ኢትፍርሁ እስመ ናሁ እዜንወክሙ ዐቢየ ዜና ዘይከውን ፍስሐ ለክሙ ወለኵሉ ሕዝብ እስመናሁ ተወልደ ለክሙ መድኅን ዘውእቱ ክርስቶስ›› ‹‹እነሆ ለሕዝቡ ሁሉ የሚሆን ታላቅ ደስታ የምሥራች እነግራችኋለሁና አትፍሩ፡፡ ዛሬ በዳዊት ከተማ መድኃኒት እርሱም ክርስቶስ ጌታ ተወልዶላችኋልና፤›› በማለት የነገራቸው ቃል ትልቅ ማስረጃ ነው ለማለት ይቻላል (ሉቃ. ፪ ÷ ፲ – ፲፩)፡፡
መጋቢት ፳፯ ቀን የሚከበረውን የመድኃኔዓለምን በዓል ጥንተ ስቅለቱ ነው ብለን ስንናገርና የስቅለቱን መታሰቢያ በዓል ስናከብር በዚሁ ቀን በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ላይ የተፈፀሙትን ጸዋትወ መከራዎችና እሱ በመስቀል ላይ እያለ በሰማይና በምድር የተፈጸሙትን ተአምራት አብረን ልናስባቸውና ልብም ልንላቸው ይገባል፡፡
በእሱ ላይ ከደረሱት ልዩ ልዩ ጸዋትወ መከራዎች ጥቂቶቹን ለማስታወስ ያህል፡ – የአይሁድ መማክርት የመከሩበት ከንቱ ምክርና በዕለተ ረቡዕም እንደዚሁ በአይሁድ ሸንጎ የተወሰነበት ጠማማና የተዛባ ፍርድ የመጀመሪያዎቹ ሲሆኑ ቀጥሎም መጋቢት ፳፮ ቀን የጸሎተ ሐሙስ ዕለት ማታ ለ፳፯ አጥቢያ ለደቀ መዛሙርቱ የመጨረሻውን እራት መግቦ፣ ምሥጢረ ቊርባንን ከመሠረተ በኋላ ሌሊቱን በሙሉ በአይሁድ ጭፍሮችና በሊቃነ ካህናት ሎሌዎች የደረሰበት ስቃይና መንገላታት እጅግ የሚያሰቅቅ ነው፡፡
ጭፍሮቹ በይሁዳ መሪነት እሱን ይዘው በቁጥጥራቸው ሥር ከአደረጉ በኋላ እንደታሰረ በመጀመሪያ ወደ ሐና ዘንድ ከዚያም ወደ ሊቀ ካህናቱ ወደ ቀያፋ፣ ቀጥሎም ወደ ጲላጦስ ከጲላጦስ ደግሞ ወደ ሔሮድስ ከዚያም እንደገና ወደ ጲላጦስ እያመላለሱ እንዲንገላታና እንዲሰቃይ አድርገውታል፡፡ በዚያውም ላይ እየሰደቡትና እየዛቱበት ፊቱን በጥፊ ራሱን ደግሞ በዱላ ይመቱት እንደነበረ ቅዱሳት መጻሕፍት በሰፊው ያስረዳሉ (ማቴ. 27÷27-31)፡፡
መጋቢት ፳፯ ቀን በዕለተ ዓርብ ከሦስት እስከ ዘጠኝ ሰዓት የተቀበላቸው መከራዎችም እጅግ በጣም ብዙዎች ናቸው፡፡ ጥቂቶቹን ለማስታወስ ያህል፣ በሚያሰቅቅና በሚዘገንን ሁኔታ በጅራፍ ተገርፎአል፤ መስቀሉን ተሸክሞ በቀራንዮ ተራራ እየወደቀ እየተነሣ፣ የገዢው የጲላጦስ ወታደሮችም እያዳፉት፣ ርኩስ ምራቃቸውንም እየተፉበትና እያፌዙበት ወደ ተራራው እንዲወጣ ተደርጎአል፡፡
ስለእሱ የተጻፈው የነቢያት ትንቢት ይፈጸም ዘንድ ልብሱን ገፈው ከለሜዳ አልበሰውታል፡፡ በልብሱም ላይ ዕጣ ተጣጥለው ተካፍለውታል፤ የእሾህ አክሊል ጕንጕን በራሱ ላይ በማድረግ የሰማይና የምድር ንጉሥ እንዳልሆነ ሁሉ ‹‹ንጉሥ ሆይ! ሰላም ለአንተ ይሁን››! እያሉ ተሳልቀውበታል፡፡
በመጨረሻም ጐኑን በጦር ወግተውታል፡፡ እጆቹን እና እግሮቹን በ፭ ችንካሮች (ቅንዋት) ቸንክረው በመስቀል ላይ ሰቅለውታል፡፡
በመስቀል ላይ እያለም ሰባት ዐረፍተ ነገሮችን ተናግሮአል፤ ከእነዚህም በጣም የሚያስደንቀው ጠላቶቹ እያሰቃዩት፣ እያንገላቱትና እየገደሉትም ሳሉ ‹‹አባት ሆይ የሚያደርጉትን አያውቁትምና ይቅር በላቸው›› ሲል የተናገረው ቃል ሲሆን የመጨረሻውም ‹‹እነሆ ሁሉም ነገር ተፈጸመ›› በማለት ከተናገረ በኋላ ወዲያውኑ ቅድስት ነፍሱን ከቅዱስ ሥጋው በራሱ ፈቃድ ለይቶ ሞት የማይገባው አምላክ ለሰው ልጆች ሕይወት ሲል ራሱን ለሞት አሳልፎ መስጠቱ ነው፡፡
የአይሁድ ሊቃነ ካህናትና ጸሐፍት ፈሪሳውያን በክርስቶስ ላይ ያቀረቡት መሠረተ ቢስ ክስና ውንጀላ በታሪክ ሂደት በጣም ሲያስገርም የሚኖር ነው ይኸውም፡ –
፩ኛ. ለቄሳር ግብር መክፈል አይገባም በማለት አስተምሮል፤
፪ኛ. ዕለተ ሰንበትን ሽሮአል፤ ራሱንም ከእግዚአብሔር ጋር አስተካክሏል ወዘተ አያሉ በሐሰት የሚመሰክሩ ምስክሮችነ በገንዘብ አባብለውና አደራጅተው በሐሰት በማስመስከር ምንም ዓይነት ወንጀል ያልፈጸመው ንጹሐ ባሕርይ ኢየሱስ ክርስቶስ በወንጀለኞች መካከል በመስቀል ላይ ተሰቅሎ እንዲሞት፤ በርባን የተባለው ወንጀለኛ ግን ከእስር እንዲፈታላቸው ለጴንጤናዊው ጲላጦስ ያቀረቡት ልመናና ገዥው ጲላጦስም ኢየሱስ ክርስቶስ ወንጀል እንዳልፈጸመ ራሱ እየመሰከረና እያረጋገጠ፣ ሚስቱም በሕልም ተረድታ እጁን በዚህ ጻድቅና ንጹሕ ሰው ደም እንዳያስገባ እያስጠነቀቀችው ‹‹ኢየሱስን ስቀለው በርባንን ፍታው›› የሚለውን ጩኸታቸውን በመስማትና እነሱን በመፍራት ብቻ ‹‹እኔ ከዚህ ሰው ደም ንጹሕ ነኝ›› በማለት እጁን ከታጠበ በኋላ ራሱ በጅራፍ ገርፎ እናንተ እንደ ሕጋችሁ ወስዳችሁ ስቀሉት ብሎ ለጠላቶቹ አሳልፎ በመስጠት የፈጸመው ስሕተትና በፍርድ ወንበር ላይ ተቀምጦ የሰጠው የተዛባ ፍርድ እጅግ የሚያሳዝን በመሆኑ ከጥንተ ስቅለቱ ጋር በትዝብት አብሮ ሲታወስ ይኖራል፡፡
ክርስቶስ የተሰቀለው መጋቢት ፳፯ ቀን ከሆነ እንደገና በሌላ ጊዜ በዓለ ስቅለትን ማክበር ለምን አስፈለገ? የሚል ጥያቄ በአእምሮአችን ሊጉላላ ይችል ይሆናል፡፡ በእርግጥ ጥንተ ስቅለቱን ማክበር በበቃ ነበር፡፡ ሆኖም ክርስቶስ የተሰቀለው በዕለተ ዓርብ ሲሆን ከመቃብር የተነሣውም በዕለተ እሑድ በመሆኑ ስቅለት ከዕለተ ዓርብ፣ ትንሣኤም ከዕለተ እሑድ፣ ዕርገት ደግሞ ከዕለተ ሐሙስ እንዳይወጡ፤ ሌሎቹም በዓላትና አጽዋማት በተወሰነላቸው ቀን እንዲውሉ ማድረግ ይቻል ዘንድ የቀድሞ አባቶችና ሊቃውንተ ቤተክርስቲያን ሰባት አዕዋዳት አዘጋጅተው እና ቀምረው ሁሉም ሥርዓቱን ጠብቆ ድርጊቱ በተፈጸመበት ቀን እንዲከበር የወሰኑ በመሆኑ ነው፡፡ በዚህም መሠረት ጥንተ ስቅለቱ መጋቢት ፳፯ ቀን በየዓመቱ እየታሰበ በዓለ ስቅለቱ ደግሞ ከሰሙነ ሕማማቱ ጋር በዓመት አንድ ጊዜ በዕለተ ዓርብ በጾምና በጸሎት እንዲሁም በአክፍሎትና በስግደት እንዲከበር በማድረግ ሕግና ሥርዓት ስለሠሩ በዚሁ መሠረት ሲፈጸም ኖሯል፡፡ ወደፊትም ይቀጥላል፡፡
ከዘጠኙ ዓበይት በዓላት አንዱ የሆነው የጌታችን የጽንሰቱ በዓል በታላቅ ድምቀት የሚከበርበት ቀን ከመሆኑ የተነሣ በዓሉን በዓል ተጭኖት ነው እንጂ ፫ኛው ቀን መጋቢት ፳፱ኝም ክርስቶስ ከሙታን ተለይቶ የተነሣበት ጥንተ ትንሣኤ በመሆኑ እንደጥንተ ስቅለቱ ሁሉ ጥንተ ትንሣኤውም ከበዓለ ጽንሰቱ ጋር አብሮ የሚታሰብ መሆኑን ልንዘነጋው አይገባንም፡፡“ወስብሐት ለእግዚአብሔር”

ሊቀ ብርሃናት ኢሳይያስ ወንድማገኘሁ





No comments:

Post a Comment

Post Bottom Ad

Pages