ዳግም ትንሳኤ - አትሮንስ ሚዲያ - Atrons Media

አትሮንስ ሚዲያ - Atrons Media

ስብኩ ወንጌለ ለኩሉ ፍጥረት ማቴ 16፤15


በቅርብ የተጻፉ

Post Top Ad

Sunday, April 23, 2023

ዳግም ትንሳኤ



ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከሙታን ተለይቶ በተነሳ በስምንተኛው ቀን በዕለተ እሁድ ደቀ መዛረሙርቱ አይሁድን ፈርተው በተሰበሰቡበት ዝግ ቤቶ "ሰላም ለእናንተ ይሁን "ብሎ ዳግም ስለ ተገለጠ #ዳግማይ_ትንሳኤ ተብሏል ።
ሁለተኛ_ለምን_ተገለጠ?
ለሐዋርያው ቶማስ ትንሳኤውን ለማሳመን ።
የጌታችን ትንሳኤ ቶማስ ስለ ተጠራጠረ ጌታችን ቶማስ በተገኘበት ዝግ ቤት ተገልጦ ለቶማስ ና ወደኔ የተቸነከረውን እጄና ጉኔን ዳስስ ብሎታል ።
ቶማስም የተቸነከረው እጁን አይቶ የተወጋውን ጉኑ በእጁ ዳስሶ የጌታችን ትንሳኤ አምኗል ።ሃገረ ስብከቱም በሕንድ ስለ ነበረ ተጋድሎውም የፈጸመው እንዲሁም ሰማዕትነት የተቀበለው በሕንድ ነው ።
ያቺ የጌታችንን ጎን የነካች (የዳሰሰች)እጅ ሳትበሰብስ ከታቦት ጋር በመንበሩ ላይ ተቀምጣለች ።እስካሁን ድረስ የሕንድ ሊቀ ጳጳስ ሲሾም በዛች እጅ ተመርጦና ተባርኮ እንደሚሾም አንዳንድ ሊቃውንት ይናገራሉ ።
◦ሰንበትን ሊያጸናልን ።
የአይሁድ ሰንበት፣እግዚአብሔር 22 ፍጥረታትን ፈጥሮ ያረፈባትና እረፉባት ብሎ ያዘዘን ሰንበት ቀዳም(ቅዳሜ)ናት ።
በሐዲስ ኪዳንም ጌታችን የተጸነሰባት ፣ከሙታን መካከል የተነሳባት፣አንዲሁም ደግሞ ለማጽናት ሁለተኛ የተገለጠባት(ዳግማይ ትንሳኤ)፣መንፈስ ቅዱስ የወረደባትና ሐዋርያት ከመጀመርያዋቹ ክርስቲያኖች ጋር በኅብረት ሆነው መንፈሳዊ ስራዋች የሚሰሩባት ቀን ዕለተ እሁድ ነበረች ።ቤተ ክርስቲያናችን ለቅዳሜ ቀዳሚት ሰንበት ለእሁድ ደግሞ ሰንበተ ክርስቲያን እያለች ለሁለቱም ቀናት እኩል ታከብራቸዋለች
።ጌታችንም ይቺ ቀን እረፍትነቷን ለማጽናት ሁለተኛ የተገለጠባት ቀን ናት ።እረፍት ስንልም ስራችንን ትተን ቁጭ ብለን (ተኝተን)የምናሳልፈው ማለት አይደለም ።እንደውም ከማንም ቀን በላይ አብዝተን መንፈሳዊ ስራዎች የምንሰራባቸው ቀናት ናቸው እንጂ ።
◦ምትሐት አለመሆኑ ለማስረዳት።
ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ምትሐት እንዳልሆነና ቀድሞ የተዋሃደው ስጋና መለኮት ፣ፍጹም ሰው ፍጹም አምላክ መሆኑ ለማስረዳት ለሁለተኛ ጊዜ ተገልጦላቸዋል ።በዝግ ቤት መግባቱ ደግሞ መለኮት እንዳልተለየውና ስጋ ብቻው እንዳልሆነ ለማስረዳት ነው ።
"ብጹዓን እለ እንዘ ኢይሬእዩ የአምኑ"
(ዮሐ20:29)
አንድም
ዳግም ማለት ሁለተኛ ማለት ነው፡፡ ጌታ ሁለት ጊዜ አልተነሳም ፡፡ ዳግም የተባለው የትንሳኤው
ስርዓት ና ቃለ እግዚአብሔር በዚህ ቀን ስለሚደገም ነው፡፡አንድም መነሳቱን ለ11ዱ ደቀመዛሙርት እንበለ ቶማስ ቢገልጥላቸው አምነው ለቶማስ ቢነግሩት የተቸነከሩ
እግሮቹንና እጆቹን ካላየሁ ጣቴን በተወጋ ጎኑ ካላገባሁ
አላምንም ብሎ ነበርና በሳምንቱ ያምን ዘንድ ቶማስ ባለበት
ለሁለተኛ ጊዜ ተገለጠላቸው፡፡ ዮሐ 20፥26-ፍም
ቤተክርስቲያን ይህንን መገለጥ ዳግም ትንሳኤ ትለዋለች፡፡
2. ፈጸምነ ይባላል
ይህ ስያሜ ደግሞ የፋሲካን በዓል አከበርን ስርዓቱን ዛሬ ፈጸምን ለማለት ነው፡፡
3. አግብኦት ግብር ይባላል
በዮሐ 17፥ 1 ጀምሮ በተገለጠው፡መፅሀፍ ቅዱሳዊ ቃል መሠረት ጌታ " አባ ወአቡየ ግብረ ዘወሀብከኒ ፈጸምኩ " ያለውን መዘምራን በቅዳሴ ማጠቃለያ አካባቢ ስለሚዘምሩበት ነው፡፡
ቶማስ ለምን ተጠራጠረ ?
መጠራጠሩ ስለ 2 ነገር ነው፡፡
1 ሰዱቃዊ ስለነበረ፡፡ ሰዱቃውያን ደግሞ ትንሳኤ ሙታን የለም ብለው የሚጠራጠሩ ናቸውና ሳላይ አላምንም ብሎ
2 ሌሎች ሐዋርያት ትንሳኤውን ሲሰብኩ ተነስቶ አይተነዋል ሲሉ እርሱ ደግሞ መነሳቱን ሰምቻለሁ ብሎ ማስተማር ስለሌለበት ለማየት ሳላይ አላምንም አለ፡፡
ጌታ የተገለጠላቸው ደጆች ተዘግተው ሳሉ ነበር ፡፡ ዮሐ 20፥26 ገብቶ ሰላም አላችሁ አስታረቅኀችሁ አላቸው፡፡
በተዘጋው ቤት እንዴት ገባ ?
ኤልሻዳይ ስለሆነ ፡፡ ዘፍ 17፥1 ሳራ ማሕጸኗ ተዘግቶ መውለድ ባልቻለች ጊዜ ልጅ የሰጣት ኤልሻዳይ ነው፡፡

ሀና ፣ ኤልሳቤጥ ሌሎችም እንዲሁ፡፡ ሉቃ 1፥ 37 እስመ አልቦ ነገር ዘይሰአኖ ለእግዚአብሔር ፡፡ እንዲል ረቂቅ መለኮት ስጋን እንደተዋሃደ ለማጠየቅ ፦ በተዘጋ ቤት ገባ፡፡

ዛሬም ደጆች ቢዘጉም ጌታ ይመጣል፡፡ብዙ ሰዎች በሕመም ተይዘው የመዳን ደጃቸው ተዘግቶ ሳለ ጌታ የመጣው ዮሐ
5፥3-12 ነፍሳት በዲያብሎስ ቁራኝነት ተይዘው ገነት ተዘግታ ሳለ ኢየሱስ መጥቶ የለ ? ሉቃ 2፥9

እስራኤላውያን የግብጽ ባርነት ቢያይልባቸው የነጻነት ደጃቸው ቢዘጋባቸውም ጌታ መጥቶ አድኗቸው የለ ? ዘጸ 3፥1-8

ሲወጡስ ከፊት ቀይ ባህር ከኀላ ፈርኦን ከቀኝና ግራ ገደልና ዳገት ቢገጥማቸውም አምላክ ደርሶላቸው የለ ? ዘጸ14፥1

ለሶስና (መ ሶስ 1፥1-23) ከውግረት አድኗት የለ?

ለአይሁድ / ዕብራውያን/ መ አስ 1-10 ሐማ ያሳወጀውን የሞት ፍርድ ቀይሮላቸው የለ?

ለሶስቱ ሕጻናት ት ዳን 3፥17 ከእሳት አውጥቷቸው የለ ?

ለሞተው አላዛር ዮሐ 11፥1-48 ከሞት አንስቶት የለ ?

ስለዚህ ሁሉን ቻዩ ጌታ ምን ደጅ ቢዘጋ መክፈት ይችላልና እንመነው ፡፡ እርሱን አምኖ ተስፋ ሚያደርግ አያፍርም መዝ 24፥3 ተብሎ ተጽፏልና ፡፡

ስለ ማይነገር ስጦታው እግዚአብሔር ይመስገን
ወስብሐት ለእግዚአብሔር
ወለወላዲቱ ድንግል
ወለመስቀሉ ክቡር አሜን

No comments:

Post a Comment

Post Bottom Ad

Pages