ስንክሳር_ዘወርኀ_መጋቢት 24 - አትሮንስ ሚዲያ - Atrons Media

አትሮንስ ሚዲያ - Atrons Media

ስብኩ ወንጌለ ለኩሉ ፍጥረት ማቴ 16፤15


በቅርብ የተጻፉ

Post Top Ad

Monday, April 3, 2023

ስንክሳር_ዘወርኀ_መጋቢት 24

 አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም

መጋቢት ሃያ አራት በዚች ቀን የኢትዮጵያ ብርሃኗ የሆኑ አቡነ_ተክለ_ሃይማኖት የተጸነሱበት ነው፣ በእስክንድርያ ሀምሳ ዘጠነኛ ሊቀ ጳጳሳት የሆነ ቅዱስ_አባ_መቃርስ አረፈ፡፡


መጋቢት ሃያ አራት በዚህች ዕለት ጌታችን በቃሉ ''ሐዲስ ሐዋርያ'' ብሎ የሾማቸው የኢትዮጵያ ብርሃኗ የሆኑ የደብረ ሊባኖሱ አቡነ ተክለ ሃይማኖት የተጸነሱበት ነው፡፡
እግዚአብሔር አምላካችን ለኢትዮጵያ ሐዲስ ሐዋርያ አድርጎ የመረጣቸው ጻድቁ አባታችን ተክለ ሃይማኖት በሊቀ መላእክት በቅዱስ ሚካኤል አብሳሪነት ከአባታቸው ከካህኑ ጸጋ ዘአብና ከእናታቸው ከቅድስት እግዚእ ኀረያ መጋቢት 24 ቀን ተፀንሰው ታኅሣሥ 24 ቀን 1197 ዓ.ም ተወለዱ፡፡ ጻድቁ በተወለዱ በሦስተኛው ቀን ከእናታቸው ዕቅፍ ወርደው ‹‹አሐዱ አብ ቅዱስ አሐዱ ወልድ ቅዱስ አሐዱ ውእቱ መንፈስ ቅዱስ›› ማለትም ‹‹አንዱ አብ ቅዱስ ነው አንዱ ወልድ ቅዱስ ነው አንዱ መንፈስ ቅዱስ ቅዱስ ነው›› በማለት የፈጠራቸውን አምላክ አመስግነውታል፡፡ ወላጆቻቸውም ስማቸውን ፍሥሐ ጽዮን አሏቸው፡፡ ይኸውም የጽዮን ተድላዋ ደስታዋ ማለት ነው፡፡ የወላጆቻቸው የቀድሞ ስማቸው ዘርዐ ዮሐንስና ሣራ ይባል ነበር፡፡
ቅዱሳን አባቶቻችን እነ አቡነ ተክለ ሃይማኖትና እነ አቡነ ዜና ማርቆስ ሌሎቹም እነ አቡነ ሳሙኤል ዘወገግ፣ አቡነ ሕፃን ሞዐ፣ አቡነ አኖሪዮስ (ትልቁ)፣ አቡነ ገላውዲዮስ፣ አቡነ ማትያስ ዘፈጠጋርና አቡነ ቀውስጦስ ዘመሐግል የትውልዳቸው መሠረት ኢያሱ ለሌዋውያን ክፍል ትሆን ዘንድ ከለያት ከኢየሩሳሌም ነው፡፡ ስማቸውን የጠቀስኳቸው እነዚህ ቅዱሳን አባቶቻችን የወንድማማቾች ልጆች ሲሆኑ ከአዳም ጀምሮ 61ኛ ትውልድ ናቸው፡፡ ይኸውም እንዴት ነው ቢሉ ትውልዱ ከአዳም ጀምሮ በካህኑ አሮን በኩል የሆነውና የሌዋዊያን ሊቀ ካህን የነበረው የሳዶቅ ልጅ አዛርያስ በንጉሥ ሰሎሞን ዘመን ከታቦተ ጽዮንና ከብዙ ሌዋዊያን ካህናት ጋር ሊቀ ካህን ሆኖ ከኢየሩሳሌም ወደ ኢትዮጵያ መጥቶ አክሱም ተቀምጦ ኖረ፡፡ የኦሪትንም ሕግ እየዞረ ለኢትዮጵያ ሰዎች አስተማረ:: ትውልዱም በአብርሃ ወአጽብሓና በአባ ሰላማ ዘመን እስከነበረው እንበረም የሚባለው ጻድቅ ድረስ ደረሰ፡፡ የእንበረምም ትውልድ ደገኛው ሕይወት ብነ በጽዮን ድረስ ደረሰ፡፡ ሕይወት ብነ በጽዮንም የደማስቆ ምድር ከሚሏት ከወለቃ ሀገር የመኮንን ልጅ የሆነችውን ወለተ ሳውልን አግብቶ አበይድላን ወለደ፡፡ አበ ይድላም በንጉሡ ድልዓዥን ዘመነ መንግሥት ለ150 ካህናት አለቃ ሆኖ በወለቃ ሀገር የክርስቶስን የወንጌል ሕግ እያስተማረ ብዙዎችን አጠመቀ፡፡ እስከ ሸዋ ምድር ድረስ እያስተማረ መጥቶ በሸዋ ምድር ተቀመጠ፡፡ ብዙ አብያተ ክርስቲያናትንም አሳነጸ፡፡ እጅግ አስደናቂ ተአምራትንም ያደርግ ነበር፡፡ ‹‹በሸዋ ጽላልሽ ተቀምጦ ሲያስተምርም በአንዲት ቀን እስከ ሁለት መቶ ሺህ ሕዝብ ያጠምቅ ነበር›› በማለት ገድለ አቡነ ተክለ ሃይማኖት ይመሰክርለታል፡፡
አበይድላ በመጨረሻ በፈቃደ እግዚአብሔር ከሸዋ ጽላልሽ ምድረ ዞረሬ ሚስት አግቶ ሀበነ እግዚእን ወለደ፤ ሀበነ እግዚእም በኩረ ጽዮንን ወለደ፤ በኩረ ጽዮንም ሕዝበ ቀድስን ወለደ፤ እርሱም ነገደ እግዚእ የተባለ ነው፡፡ ሕዝበ ቀድስም ብርሃነ መስቀልን ወለደ፤ እርሱም ዐቃቢነ እግዚእ የተባለ ነው፡፡ ብርሃነ መስቀልም ሕይወት ብነን ወለደ፤ እርሱም ሴትን ወለደ፡፡ ሴትም ወረደ ምሕረትን ወለደ፡፡ ወረደ ምሕረትም ዘካርያስን ወለደ፡፡ ዘካርያስም የእነ አቡነ ተክለ ሃይማኖት አባት የሆኑ 6 ወንድማማች ልጆችን ወለደ፡፡ እነርሱም እንድርያስ፣ አርከሌድስ፣ ዘርዐ አብርሃም፣ ዘርዐ ዮሐንስ ወይም ጸጋ ዘአብ፣ ቀሲስ ዮሐንስና ቀሲስ ዮናስ ናቸው:: እንድርያስም ሳሙኤል ዘወገግን ወለደ፤ አርከሌድስም ሕፃን ሞዐን ወለደ፤ ዘርዐ አብርሃምም ታላቁን አኖርዮስን ወለደ፤ ዘርዐ ዮሐንስ ወይም ጸጋ ዘአብም ተክለ ሃይማኖትን ወለደ፤ ቀሲስ ዮሐንስም ዜና ማርቆስን ወለደ፣ ቀሲስ ዮናስ ደግሞ የፈጠጋሩን ማትያስንና ገላውዲዮስን ወለዳቸው፡፡ ገላውዲዮስም የመሐግሉ ቀውስጦስን ወለደ፡፡ እነዚህ ደጋግ ቅዱሳን በእናታቸውም በኩል እንዲሁ በዝምድና የተሳሰሩ ናቸው፡፡ ማቴዎስ የተባለው ደገኛ ክርስቲያን የሸዋ ገዥ የነበረ ሲሆን አንድ ወንድ ልጅ መድኃኒነ እግዚእንና ሦስት ሴቶች ልጆችን ወለደ፡፡ ሶስቱ ሴቶች ልጆችም እምነ ጽዮን፣ ትቤ ጽዮንና ክርስቶስ ዘመዳ ይባላሉ፡፡ ሦስቱ እኅትማማቾችም ደጋጎቹን አባቶቻችንን ወለዱልን፡፡ እምነ ጽዮን የእነ ዜና ማርቆስን እናት ማርያም ዘመዳንና ወለደች፡፡ ትቤ ጽዮንም ሕፃን ሞዐን ወለደች፡፡ ክርስቶስ ዘመዳ ደግሞ ታላቁን አኖሬዎስን ወለደች፡፡ የፈጠጋሩ ገዥ መድኃኒነ እግዚእ ደግሞ የተክለ ሃይማኖትን እናት እግዚእ ኀረያን ወይም በሌላ ስሟ ሣራን ወለደ፡፡
አቡነ ተክለ ሃይማኖት ከልጅነታቸው ጀምሮ በወላጅ አባታቸው በካህኑ ቅዱስ ጸጋ ዘአብ ግብረ ዲቁናን ሥርዓተ ቤተ ክርስቲያንን ሲያጠኑ ቆይተው በ15 እና በ22 ዓመታቸው ከእስክንድርያው ሊቀ ጳጳስ ከአቡነ ቄርሎስ (ጌርሎስ) ዲቁናንና ቅስናን ተቀብለዋል፡፡ ብፁዕ ወቅዱስ አባታችን ቅድስት ቤተክርስቲያንን በወጣትነት ዕድሜያቸው ያገለግሉ እንደነበር በዚህ ይታወቀል፡፡
ከዕለታት በአንዱ ቀን አባታችን ከጓደኞቻቸው ጋር ለአደን ወደ ዱር ሄደው ሳለ ሊቀ መላእክት ቅዱስ ሚካኤል ተገልጦ ታያቸው፡፡ ቅዱስ አባታችንም ‹‹እንደዚህ ባለ ገናንነት የማይህ ጌታዬ ማነህ?›› ባሉት ጊዜ ቅዱስ ሚካኤል ‹‹ዘወትር የምጠብቅህ ካንተ የማልለይ እናትህንና አባትህንም ስላንተ ከውኃ ስጥመትና ከምርኮ ያዳንኳቸው እኔ ሚካኤል ነኝ፡፡ ከእንግዲህ አውሬ አዳኝ አትሁን፤ ሰውን ወደ እግዚአብሔር ለመመለስ ሰውን በትምህርት የምታድን ሁን እንጂ፡፡ እነሆ እግዚአብሔር ጽኑዕ ሥልጣን ሰጥቶሃልና፤ ሙት ታስነሣለህ፤ ድውያንን ትፈውሳለህ፤ አጋንንትም አንተን በመፍራት ይሸሻሉ፡፡ ስምህ ፍሥሐ ጽዮን አይሁን፤ ተክለ ሃይማኖት ይሁን እንጂ፡፡ ትርጓሜውም ተክለ አብ፥ ተክለ ወልድ፥ ተክለ መንፈስ ቅዱስ ማለት ነው›› አላቸው፡፡
ቅዱስ ሚካኤል ይህን ሲነግራቸው ጌታችን በሥጋ ከደቀ መዛሙርቱ ጋር እንደነበር ሆኖ መልከ መልካም ጎልማሳ መስሎ ታያቸው፡፡ ጌታችንም ‹‹ወዳጄ እንዴት ሰነበትክ? ቸር አለህን?›› አላቸው፡፡ አቡነ ተክለ ሃይማኖትም ‹‹ጌታዬ ሆይ አንተ ማነህ?›› ብለው ሲጠይቁት ጌታችንም ‹‹እኔ የዓለም መድኃኒት ኢየሱስ ነኝ፤ በናትህ ማኅፀን ፈጥሬህ ያከበርኩህ እኔ ነኝ፡፡ በተወለድክ በሦስተኛው ቀን አሐዱ አብ ቅዱስ አሐዱ ወልድ ቅዱስ አሐዱ ውእቱ መንፈስ ቅዱስ ብለህ ታመሰግነኝ ዘንድ የምስጋና ሀብት ያሳደርኩብህ እኔ ነኝ፡፡ በርሃብ ዘመን በቤት የሚያሻው ምግብ ሁሉ ቅቤው፣ የስንዴው ዱቄት በእናት በአባትህ ቤት ይመላ ዘንድ በእጅህ ሀብተ በረከት ያሳደርኩብህ እኔ ነኝ፡፡ ያንን ሰው አንተን በተጣላ ጊዜ በነፋስ አውታር የሰቀለኩት በመዓት ጨንገር የገረፍኩት እኔ ነኝ፡፡ ውኃ ጠምቶህ በለመንከኝ ጊዜ ከደረቅ መሬት የጣፈጠ ውኃ ያመነጨሁልህ እኔ ነኝ፡፡ ከልጅነትህ ጀምሮ እስከ ዛሬ ድረስ ብዙ ተአምራት እያደረግሁ በአንተ እጅ የታመሙትን ያዳንኳቸው እኔ ነኝ፡፡ ወደፊትም አደርግልሃለሁ›› አላቸው፡፡ ይህንን ብሎ በእጆቹ ባረካቸውና ‹‹ንሣእ መንፈስ ቅዱስ›› ብሎ የሹመትን ሀብት አሳደረባቸው፡፡ ዳግመኛም ‹‹በምድር ያሰርከው በሰማይ የታሰረ ይሁን፤ በምድርም የፈታኸው በሰማይ የተፈታ ይሁን፤ አንተን የሰማ እኔን መስማቱ ነው፤ የላከኝ አባቴንም መስማቱ ነው፡፡ አንተን እንቢ ያለ እኔን እንቢ ማለቱ ነው፡፡ የላከኝ አባቴንም እንቢ ማለቱ ነው፡፡ ይህን ሥልጣን ቀድሞ ለሐዋርያት ሰጥቻቸው ነበር፡፡ ከሐዋርያትም ሹመትን የተቀበለ ጳጳሱ ትሾምና ትሽር፣ ትተክልና ትነቅል ዘንድ ሥልጣንን ሰጠህ፡፡ ይህንንም ያደረኩልህ የጳጳሱን ቃል በመናቅ አይደለም፡፡ የፍቅሬን ጽናት ባንተ እገልጽ ዘንድ ነው እንጂ፡፡ ሐዋርያት ወዳልደረሱበት ሕዝብ በመምህርነት እልክህ ዘንድ በሚካኤል ቃል አዲስ ስም አወጣሁልህ፡፡ አንተም በማናቸውም ሥራ ከእነርሱ አታንስም፣ ሐዲስ ሐዋርያ አድርጌሃለሁና፡፡ ሰውን ሁሉ በእኔ ስም እያስተማርክ ታሳምን ዘንድ፣ ሚካኤልም ባሰብከው ሥራ ሁሉ ረዳት ይሁንህ፣ ሁል ጊዜ ካንተ አይለይም፤ በምትሄድበትም ጎዳና ሁሉ እርሱ መሪ ይሁንህ፤ እኔም ባለ ዘመንህ ሁሉ አልለይህም›› ካላቸው በኋላ ሰላምታ ሰጥቷቸው ዐረገ፡፡
ብፁዕ አባታችንም እጅ ነሥተው ‹‹ለእኔ ለኀጥኡ የማይገባኝ ሲሆን ይህን ሁሉ ጸጋ የጠኸኝ ስምህ በሰማይ በምድር የተመሰገነ ይሁን›› አሉ፡፡ ከዚያች ቀን ጀምሮ ሀብተ ኃይልን የተመሉ ሆኑ፡፡ ወደቤታቸው ተመልሰው ያላቸውን ሀብት ንብረት ሁሉ ለቤተ ክርስቲያን፣ ለድኆችና ለጦም አዳሪዎች ሰጥተው ጨረሱ፡፡ ከዚያም ‹‹አቤቱ ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ! የመንግሥተ ሰማያትን በር ትከፍትልኝ ዘንድ እነሆ ቤቴን እንደተከፈተ ተውኩልህ›› ብለው ቤታቸውን እንደተከፈተ ትተው ወንጌልን ለማስተማር ወጡ፡፡ ጻድቁ አባታችን በሀገራችን ኢትዮጵያ እየተዘዋወሩ ሕዝቡን ከኃጢአት ወደ ገቢረ ጽድቅ፣ ከክህደት ወደ ኃይማኖት ስለመለሱት በዚህም የተነሣ ለኢትዮጵያውያን ብርሃን ተብለዋል፡፡
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
በዚህች ቀን በእስክንድርያ ለተሾሙ አባቶች ሊቃነ ጳጳሳት ሀምሳ ዘጠነኛ የሆነ ቅዱስ አባት የእስክንድርያ ሊቀ ጳጳሳት አባ መቃርስ አረፈ።
ይህም የከበረ አባት ሳብራ ከምትባል አገር ነው ከታናሽነቱ ጀምሮ ይህን አለም ንቆትቶ የምንኲስናን ልብስ ሊለብስ ወደደ። ወደ አስቄጥስ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ መነኰሰ።
በተጋድሎም ተጠመደ ከእርሱም በጉ ስራዎችና ትሩፋቶች ተገለፀው ታዩ። ከእርሱ አስቀድሞ የነበረ ሊቀ ጳጳሳት አባ ቆዝሞስ በአረፈ ጊዜ ኤጲስቆጶሳቱ ይሾሙት ዘንድ በአንድ ምክር ተስማምተው ለእስክንድርያ ሊቀ ጳጳሳት አድርገው ያለ ፈቃዱ ሳይወድ በግድ ሾሙት።
ወደ እስክንድርያም ይዘውት ሲሄዱ እግረ መንገዱን ከተወለደባት አገር ደረሰ እናቱም በዚያ በህይወት አለች እርሷም የዚህን የኃላፊውን አለም ክብር የምትጠላ እግዚአብሔርን የምትፈራ እውነተኛ ሰው ናት።
ወደ ርሷም እንደመጣ ስለርሱ በሰማች ጊዜ ልትቀበለው አልወጣችም ። ነገር ግን እርሱ ራሱ እርሷ ወዳለችበት ቤት ገባ ተቀምጣም ትፈትል ነበር በሰላምታ ልትገናኘው ያልተነሳችው ያላወቀችው መስሎት እኔ እገሌ ልጅሽ አይደለሁምን ለምን ሰላምታ አትሰጪኝም ወይስ አላወቅሺኝም አላት።
እርሷም እኔስ አውቄሀለሁ ራስህን ያላወቅህ አንተ ነህ በዚህ በሊቀ ጵጵስና ክብር ሆነህ ከማይህ ሞተህ ተገንዘህ ባይህ በወደድኩ ነበር ። ከአሁን በፊት የምትጠየቀው በራስህ ኃጢአት ብቻ ነበር ከዛሬ ጀምሮ ግን በምእመናን ሁሉ ኃጢአት ነው ብላ መለሰችለት።
ከዚህ በኋላ ሁለቱም በአንድነት አለቀሱ ይህም እናቱ የተናገረችው ነገር በልቡ አደረ ስለ ራሱ ድኀነትና የምእመናኑንም ነፍሳቸውን ለማዳን መፃህፍትን በማስነበብ በመምከርና በመገሰፅ እያነቃ ሲታገል ኖረ።
ደግሞ በእውነተኞች ካህናት ምስክርነት በቀር ካህናትንና ኤጲስቆጶሳትን ከመሾም የሚጠነቀቅና የሚጠበቅ ሆነ። ከቤተ ክርስቲያንም ገንዘብ የማይገባውን ምንም ምን አይውስድም ነበር። ኤጲስቆጶሳትንና ቀሳውስትን ወገኖቻቸውን ጥቅም በአላቸው በቅዱሳት መፃህፍት ቃል በመምከር ይጠብቋቸው ዘንድ ያዛቸው ነበር።
በሰላምና በፀጥታ ሆኖ በማርቆስ ወንበር ሀያ አመት ኖረ በሹመቱም ወራት አብያተ ክርስቲያናት ተቃንተው ተስተካክለው ያለ መቋረጥም በፀሎትና በቅዳሴ ተሰርተው አገልግሎት ሲሰጡ ኖሩ። ከዚህም በኃላ በሰላም አረፈ፡፡
ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በከበሩ ቅዱሳን ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ለዘለዓለሙ ይሁን አሜን፡፡

No comments:

Post a Comment

Post Bottom Ad

Pages