ቅዱስ ቶማስ - አትሮንስ ሚዲያ - Atrons Media

አትሮንስ ሚዲያ - Atrons Media

ስብኩ ወንጌለ ለኩሉ ፍጥረት ማቴ 16፤15


በቅርብ የተጻፉ

Post Top Ad

Wednesday, April 15, 2020

ቅዱስ ቶማስ


ሥራ መሥራት የማይሰለቸው ታታሪ ሰራተኛ የሆነ አንድ ጎልማሳ ሰው ነበር:: ይህ ጎልማሳ ሰው አብዝቶ ኃጢአትን ይሰራ ነበር:: ከእለታት በአንዱ ቀን በሐዋርያው ቅዱስ ቶማስ እጅ የተባረከ እንጀራ ከሕዝብ ጋር አብሮ ተቀበለ:: ወደ አፉም ሊጨምረው በወደደ ጊዜ እጆቹ ደረቁ:: በዚህን ጊዜ አብረውት የነበሩት ሰዎች በነገሩ ተገርሙ ደነገጡም:: ወዲያውኑን ያዩትን ድንቅ ተአምር ለሐዋርያው ቅዱስ ቶማስ ነገሩት:: ሐዋርያው ቅዱስ ቶማስም ነገሩን ከሰማ በኋላ ልጁን ጠርቶ ልጄ ሆይ የሆንከውን ነገር ሳታፍር ሳትፈራ እውነቱን ንገረኝ የ እግዚአብሔር ቸርነት በግልጽ ዘልፎሃልና አለው:: ያም ሰው ኃጢአቱን ያውቃልና ወዲያውኑ ከሐዋርያው ቅዱስ ቶማስ እግር ስር ሰገደና እንዲህ በማለት ኃጢአቱን መናዘዝ ጀመረ:: እኔ መልካም ሥራ የሰራሁ መስሎኝ ክፉን ሥራ ሰርቻለሁ:: አንዲት ሴት ነበረች:: አስቀድሞ ወደ እርሷ እኔ እገባ ነበር:: አንተም በንጽሕና እንድንኖር አስተማርከን መከርከን ያች ሴት ግን ከ እርሷ ጋር እተኛ ዘንድ ኃጢአትን እሰራ ዘንድ ነዘነዘችኝ:: በነገሩ ተናድጄ ሰይፍ አነሳሁና አንገቷን ቀላኋት (አረድኳት) አለው:: ቅዱስ ቶማስም እንዴት እንዲህ ያለ ቁጣና የአውሬ የእንስሳ ሥራ ትሠራለህ? አለው:: ይህንን ነገር ለሚሰሙትም በሙሉ ውኃ ያመጡ ዘንድ አዘዛቸው:: እነሱም በፍጥነት ውሃውን ይዘው መጡ:: ቅዱስ ቶማስም በውሃው ላይ ጸለየ:: ጎልማሳውንም በ እግዚአብሔር ታምነህ እጆችህን ታጠብ አለው:: ቅዱስ ቶማስ የነገረውን አምኖ ሲታጠብም ዳነ:: ከዚህ በኋላ ቅዱስ ቶማስ ለጎልማሳው ሰው የዚያች ሴት አስከሬን የት ነው? ቦታውን ምራኝ ብሎ ጠየቀው:: ያም ጎልማሳ መርቶ ወደ ቦታው አደረሰው:: በደረሱም ጊዜ ቅዱስ ቶማስ በልጅቱ ላይ የደረሰውን ግፍና ጭካኔ አይቶ እጅግ አዘነ:: ወደ ውጭም አውጥተው በአልጋ ላይ ያኖሯት ዘንድ አዘዘ:: እነሱም ቅዱስ ቶማስ እንዳዘዛቸው አደረጉ:: እጁንም አንስቶ በላይዋ ጭኖ ጸለየ:: ጸሎቱንም በፈጸመ ጊዜ ጎልማሳውን ሂድ እጇን ይዘህ እኔ ቀድሞ በእጄ ገደልኩሽ አሁን ግን በሃይማኖት በእኔ እጅ ክርስቶስ ያስነሳሽ በላት አለው:: እሱም ቅዱስ ቶማስ እንዳዘዘው አደረገ:: እጇንም ይዞ ሳባት:: ፈጥናም ተነሳች:: ሐዋርያው ቅዱስ ቶምስን አየችው:: አልጋዋንም ትታ ከቅዱስ ቶማስ እግር ስር ሰገደች:: የልብሱንም ጫፍ ይዛ በአንተ ዘንድ አደራ ያስጠበቀኝ ባልንጀራህ ወዴት አለ? ብላ ጠየቀችው:: ሐዋርያው ቅዱስ ቶማስም ወደ የት ደርሰሽ ነበር ንገሪኝ? አላት:: እርሷም አንተ ከእኔ ጋር እያለህ እንዴት ንገሪኝ ትለኛለህ? አለችው:: ያየሽውን ንገሪ አላት:: ከሥጋዬ በተለየሁ ጊዜ አንድ ልብሱ የቆሸሸ: ሽታውም የሚከረፋ: ጠቋራ ተቀበለኝ:: የ እሳት ጉድጓድና የ እሳት መንኮራኩር ወደ አለበት ቦታ ወሰደኝ:: ደግሞም እድፍንና ትልን የተመላ ጉድጓድን አየሁ:: ነፍሳትም በውስጡ ይንከባለላሉ:: በዚያም በምላሳቸው የተንጠለጠሉ አሉ:: በጸጉራቸውም የተንጠለጠሉ አሉ:: በእጆቻቸውም በእግሮቻቸውም የተንጠለጠሉም አሉ:: በላያቸውም ድኝ ይጤስባቸዋል ያስጨንቋቸዋልም:: ያ የሚመራኝም እኒህ ነፍሰ ገዳዮች: በዝሙት የረከሱ: ዘራፊዎች (ሌቦች): በሐሰት እየመሰከሩ አምላክን ሲያሳዝኑ የኖሩ: በእግዚአብሔር መንገድ ያልተመላለሱ: የእግዚአብሔርን ሕግ የጣሱ: የእግዚአብሔርን ሕልውና የካዱ: እነዚህ ሁሉ በንስሐ ያልተመለሱ ናቸው ስለዚህ እንደ ሥራቸው ይቀጣሉ አለኝ አለችው:: ሐዋርያው ቅዱስ ቶማስም ከዚያ ለተሰበሰበው ሕዝብ ይህች ሴት የምትለውን ሰማችሁ ከደቂቆች በፊት ሞታ ነበር በ እግዚአብሔር ቸርነት ተነሳች ያየችውን ነገረቻችሁ:: ይህች ሴት ያለችውን ሰማታችኋል ነገር ግን ያለው ስቃይ ይህ ብቻ አይደለም ነገር ግን ከዚህ የሚከፋ አለ:: እናንተም የኃጢአትን ሥራና ክፉ ሃሳብን ትታችሁ ወደ ፈጣሪያችሁ ወደ አምላካችሁ በፍጹም ልብ ወደ እግዚአብሔር ተመለሱ:; የተፈጠራችሁበት ዋና ዓላማ ስሙን ለመቀደስ ክብሩን ለመውረስ ነውና ከልባችሁ በንስሐ ወደ እግዚአብሔር ተመለሱ:: ትህትናን የዋህነትንና ፍቅርን ንጽሕናንም ጠብቁ ከ እግዚአብሔርም ዘንድ ጸጋን ትቀበላላችሁ አላቸው:: ክብር ይግባውና በጌታችን በመድኃኒታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ሁሉም የተሰበሰው ሕዝብ በሙሉ አንድም ሳይቀር አመኑ:: ለድኆችም ምጽዋትን ሊሰጡ ብዙ ገንዘብ ሰብስበው አመጡ:: ለድኆች ምጽዋት መስጠት ለሐዋርያው ቅዱስ ቶማስ ልማዱ ነበርና:: ይህም ታላቅ ተአምር በየሃገሩ በተሰማ ጊዜ በተለያዩ በሽታ የሚሰቃዩትንና በአጋንንት የሚሰቃዩትን በሽተኞች በሙሉ አምጥተው በጎዳና (በመንገድ) ዳር አኖሯቸው:: ቅዱስ ቶማስም የእግዚአብሔርን ቸርነቱን ምህረቱን እያስተማሩ እነዚህን በሽተኞች በሙሉ በእግዚአብሔር ሃይል ፈወሳቸው አዳናቸው:: ወስብሐት ለእግዚአብሔር የእግዚአብሔር ቸርነቱና ምሕረቱ የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም አማላጅነቱና ርህራሄዋ የቅዱሳን በረከታቸው ረድኤታቸው ጸሎታቸው አይለየን:: እግዚአብሔር አምላካችን በቅዱስ ቶማስ ጸሎት ይማረን በረከቱና ረድኤቱም አይለየን አሜን::

No comments:

Post a Comment

Post Bottom Ad

Pages