"መልአከ ሰላም አባ ወልደ ማርያም በ98 ዓመታቸው ዛሬ ከዚህ ዓለም ድካም አረፉ - አትሮንስ ሚዲያ - Atrons Media

አትሮንስ ሚዲያ - Atrons Media

ስብኩ ወንጌለ ለኩሉ ፍጥረት ማቴ 16፤15


በቅርብ የተጻፉ

Post Top Ad

Monday, September 19, 2022

"መልአከ ሰላም አባ ወልደ ማርያም በ98 ዓመታቸው ዛሬ ከዚህ ዓለም ድካም አረፉ

"መልአከ ሰላም አባ ወልደ ማርያም የሚነበቡ እና የሚተረጎሙ ታላቅ መፅሐፍ ነበሩ"...ብፁዕ አቡነ መልከጼዴቅ (መስከረም 9 ቀን 2015 ዓ.ም አዲስ አበባ-ኢትዮጵያ) በ98 ዓመታቸው ከዚህ ዓለም ድካም ያረፉት መልአከ ሰላም አባ ወልደ ማርያም ግብዓተ መሬት ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት፣ የምሥራቅ ሸዋ ሀገረ ስብከት የሥራ ኃላፊዎች፤ የአድባራትና የገዳማት አስተዳዳሪዎች፣ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን፣ የሰንበት ት/ቤት ወጣቶችና የመንፈስ ቅዱስ ልጆቻቸው በተገኙበት በዝዋይ ሐመረ ኖህ ቅድስት ኪዳነ ምሕረት ገዳም ተፈጽሟል፡፡ የአዲስ አበባ እና ጉራጌ አህጉረ ስብከት ሊቀጳጳስ እንዲሁም የአዲስ አበባ ሃይማኖት ተቋማት ጉባኤና የቅድስት ሥላሴ ዩንቨርስቲ የቦርድ ሰብሳቢ ብፁዕ አቡነ መልከጼዴቅ በዕለቱ ባስተላለፉት መልዕክት መልአከ ሰላም አባ ወልደማርያም "የሚነበቡና የሚተረጎሙ ታላቅ መፅሐፍ ነበሩ " ብለዋል። ግንቦት 12 ቀን 1919 ዓ.ም በሰሜን ሸዋ ሰላሌ አውራጃ ግራር ጃርሶ ልዩ ስሙ ኤጀርሳ ካኦ ቅድስት ማርያም በተባለች ቦታ የተወለዱት መልአከ ሰላም አባ ወልደ ማርያም የዲቁናና የምንኩስና ሥርዓትን በደብረ ሊባኖስ ገዳም የፈፀሙ ሲሆን ከ1976 ዓ.ም ጀምሮ በልዩ ልዩ መንፈሳዊ አገልግሎት በዝዋይ ሐመረ ብርሃን ቅዱስ ገብርኤል ገዳም አገልግለዋል፡፡ መልአከ ሰላም አባ ወልደ ማርያም በትሕትናና በታላቅ መንፈሳዊ ተጋድሎ ቅድስት ቤተክርስቲያንን ያገለገሉ አባት ነበሩ። ብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስ የምስራቅ ሸዋ ሐገረ ስብከት ሊቀጳጳስ በበኩላቸው በመልአከ ሰላም አባ ወልደ ማርያም ኅልፈት የተሰማቸውን ሐዘን ገልፀው ታላቅ የገዳሙ ቅርስ እንደነበሩ ተናገረዋል። በቀብር ሥነ ሥርዓቱ የምሥራቅ ሸዋ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስን ጨምሮ፣ ብፁዕ አቡነ መልከጼዴቅ የአዲስ አበባና ጉራጌ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፣ ብፁዕ አቡነ ዲሜጥሮስ የተባበሩት አረብ ኤምሬትና የሊባኖስ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፣ የምሥራቅ ሸዋ ሀገረ ስብከት የሥራ ኃላፊዎች፣ ሊቃውንተ ቤተክርስቲያን፣ የመንፈስ ቅዱስ ልጆቻቸው ተገኝተዋል ሲል ሐመረ ተዋሕዶ ሚዲያ ዘግቧል።

No comments:

Post a Comment

Post Bottom Ad

Pages