ስንክሳር ዘወርኀ ጷጉሜ 3 - አትሮንስ ሚዲያ - Atrons Media

አትሮንስ ሚዲያ - Atrons Media

ስብኩ ወንጌለ ለኩሉ ፍጥረት ማቴ 16፤15


በቅርብ የተጻፉ

Post Top Ad

Friday, February 23, 2024

ስንክሳር ዘወርኀ ጷጉሜ 3

 በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን።


 ርኅወተ ሰማይ 

 ይህች ዕለት የሰዎች ሁሉ ጸሎት የሚያርግባት: አራተኛው መጋቢ ኮከብ የሚያልፍባት: ለሰው ልጆች ከፈጣሪያቸው ጸጋ በረከት የሚሰጥባት ዕለት ስለሆነች "ርኅወተ ሰማይ-ሰማይ የሚከፈትባት ቀን::" ትባላለች::

አሁን በሰማይ መዘጋት መከፈት ኑሮበት አይደለም:: የሰው ልጆችን ልመና ቅዱሳን መላእክት ያለ ከልካይ የሚያሳርጉበት: አንድም ቅዱስ ሩፋኤል የዓመቱን የጸሎት መዝገብ የሚከፍትበት ቀን ስለሆነ እንዲህ ተባለ እንጂ::

እመቤታችን ድንግል ማርያም ለአጼ ናዖድ እንደ ነገረቻቸው በዚህች ዕለት ሁሉም ቅዱሳን ስለሚታሰቡ: የእግዚአብሔር የምሕረት መዝገቡ ስለሚከፈት: ዕለቷን ክብርት ያሰኛታል:: በቅዱስ ሩፋኤል አበጋዝነት (መሪነት) በዚህች ዕለት ለዓመት የሚበቃ ምሕረት ይገኛል::

ስለዚህም አባቶቻችን በዚህች ሌሊት ሦስት መቶ ስልሳ አምስት አቡነ ዘበሰማያትን ሲጸልዩ ያድራሉ:: በሌላ ወገን ደግሞ የጌታ ዳግም ምጽዓቱ መታሰቢያ እንደ መሆኗ ትልቅ ትኩረትም ይሰጣታል::
ቸሩ ጌታችን ከተከፈተች ገነት ከተነጠፈች ዕረፍት ሁላችንንም ያድርሰን::

ቅዱስ ሩፋኤል ሊቀ መላእክት 

††† ቅዱስ ሩፋኤል በቤተ ክርስቲያን አስተምሕሮ ከሰባቱ ሊቃነ መላእክት በደረጃው ሦስተኛ ነው:: በመጀመሪያዋ ዕለተ ፍጥረት እግዚአብሔር መቶ ነገደ መላእክትን ፈጥሮ በአሥር ከተማ ሲያኖራቸው የቅዱስ ሩፋኤል ዕድል ፈንታው ራማ ሆነች::

በዚያም "መናብርት" ተብለው ለሚጠሩ አሥሩ ነገድ አለቃ (መሪ) ሆኖ በፈጣሪው ተሹሟል:: በኋላም "መጋብያን" በሚባሉ በሃያ ሦስቱ ነገድ ላይ ሹሞታል:: ይህች ዕለትም በዓለ ሲመቱ ናት::

አንድ ቀን ጌታችን ክርስቶስ በደብረ ዘይት ተቀምጦ ሳለ ሐዋርያቱ ቅዱስ ሩፋኤልን እንዲያስተዋውቃቸው ለመኑት:: ጌታም ሦስቱን ሊቃናት (ሚካኤል: ገብርኤል እና ሩፋኤል) ይመጡ ዘንድ አዘዛቸው::

ቀጥሎም ቅዱስ ሩፋኤልን "ክብርህን ንገራቸው::" አለው:: እርሱም ለጌታ ሰግዶ ለሐዋርያት ብዙ ምሥጢር ነገራቸው:: በተለይ ስሙን ለሚጠሩ: መታሰቢያውን ለሚያከብሩ የሚደረገውን ጸጋ አብራርቶላቸው ዐረገ::

በመጽሐፈ ጦቢት ላይ ተጽፎ እንደምናገኘው ቅዱሱ መልአክ ሰው (አዛርያን) መስሎ: ጦብያን ለትዳር አብቅቶ: ሣራን አስማንድዮስ ከሚባል ሰይጣን አድኖ: የጦቢትን ዓይን አብርቷል:: በገድላተ ቅዱሳን እንደምናየውም ለብዙ ቅዱሳን ረዳታቸው ሆኖ ገድላቸውን አስፈጽሟል::

ታሪክ እንደሚለው ይህች ቀን ለቅዱስ ሩፋኤል ቅዳሴ ቤቱም ናት:: በ4ኛው መቶ ክ/ዘመን በቅዱስ ቴዎፍሎስ ዘእስክንድርያ አማካኝነት ቤቱ ታንጿል:: የሚገርመው ደግሞ የታነጸው በዓሣ አንበሪ ጀርባ: ደሴት ላይ ነው:: በመልአኩ አጋዥነትም ለሦስት መቶ ዓመታት አገልግሏል::

 ቅዱስ ሩፋኤል
¤መስተፍስሒ (ልቡናን ደስ የሚያሰኝ)
¤አቃቤ ሥራይ (ባለ መድኃኒት ፈዋሽ)
¤መዝገበ ጸሎት (የጸሎት መዝገብ መክፈቻ የተሰጠው)
¤ሊቀ መናብርት (በዙፋን ላይ በክብር የሚቀመጡ መላእክት መሪ)
¤ፈታሔ ማኅጸን (የሰውንም ሆነ የእንስሳትን ማኅጸን የሚፈታ)
¤መወልድ (አዋላጅ: ምጥን የሚያቀል) ይባላል::
"ለሰብእ ወለእንስሳ ፈታሔ ማኅጸኖሙ አንተ" እንዲል::

ቅዱስ መልከ ጼዴቅ 

 ካህኑ መልከ ጼዴቅን ቅዱስ ጳውሎስ "የትውልድ ቁጥር የለውም: ለዘመኑም ጥንትና ፍጻሜ የለውም::" ይለዋል:: (ዕብ.7:3) ሐዋርያው ይህንን ያለው ለወልደ እግዚአብሔር ምሳሌ ሲያደርገው እንጂ ትውልዱ ከነገደ ካም ነው:: ወላጆቹም "ሚልኪ እና ሰሊማ" ይባላሉ::

ገና ከእናቱ ማኅጸን የተመረጠው ቅዱሱ "ካህነ ዓለም: ንጉሠ ሳሌም" ይባላል:: የዛሬ አምስት ሺ አምስት መቶ ዓመት አካባቢ ሴም ባኖረበት ቦታ (በደብረ ቀራንዮ) ለዘላለም ይኖራል:: ካህኑ መልከ ጼዴቅ ከሰው ወገን እጅግ ክቡርም ነው::

 አፄ ዘርዓ ያዕቆብ 

 ሃይማኖቱ የቀና ኢትዮጵያዊው ንጉሥ አፄ ዘርዓ ያዕቆብ በኢትዮጵያ በነገሠባቸው ሠላሳ አራት ዓመታት (ከ1426 እስከ 1460 ዓ/ም) ብዙ በጐ ነገሮችን ሠርቷል:: ላለፉት ሰባ ዓመታት ግን አንዳንድ ጥቃቅን ሰብአዊ ስህተቶችን እየነቀሱ ተሐድሶዎቹ ስሙን ሲያጠፉት ኑረዋል::

ዛሬ ዛሬ ደግሞ የእኛ ቤት ሰዎችም ተቀላቅለዋቸዋል::
እነርሱ ያሉትን ይበሉ እንጂ ለእኛ ግን ዘርዓ ያዕቆብ ማለት:-
1.ጣዖት አምልኮን ከሃገራችን ለማጥፋት ብዙ ሺህ ካህናትን አሰልጥኖ አሰማርቷል::
2.የኑፋቄ ችግሮችን ለመቅረፍ ጉባኤያትን አዘጋጅቷል::
3.ከአሥራ አንድ ያላነሱ መጻሕፍትን በመንፈስ ቅዱስ አጋዥነት ደርሶ ለአገልግሎት አብቅቷል::
4.ብዙ መጻሕፍትን ከውጪ አስመጥቶ አስተርጉሟል (በተለይ ተአምረ ማርያምን)
5.ሰው ሁሉ ለእመ ብርሃንና ለመስቀሉ ፍቅር እንዲገዛ ጥረት አድርጓል
6.እመቤታችንን በፍጹም ልቡ ከመውደዱ የተነሳ ዛሬ ድረስ በሃገራችን ድንግል ማርያም "የዘርዓ ያዕቆብ እመቤት" እየተባለች ትጠራለች::
7.ብዙ አብያተ ክርስቲያናትን አንጾ: ብዙ ሥርዓቶችም በሊቃውንት እንዲሠሩ አድርጐ: ሌሎች ብዙ በጐ ተግባራትንም ፈጽሞ በዚህች ቀን ዐርፏል::
ቤተ ክርስቲያን ስለውለታቸው ዘርዓ ያዕቆብን: እናታቸው ጽዮን ሞገሳን እና አባታቸው ዳዊትን በክብር ታስባለች::

 ቅዱስ ሰራጵዮን ዘሰንዱን 

ይህ ቅዱስ እጅግ የበዛ ሃብቱን ለነዳያን አካፍሎ: ወደ ሌላ ሃገር ሔዶ ለባርነት ተሽጧል:: በተሸጠበት ሃገርም በጸሎት ተግቶ ከክህደት ወደ ሃይማኖት መልሷቸዋል:: ክብሩን ሲያውቁበትም በተመሳሳይ ወደ ሌላ ሃገር ሒዶ አሕዛብን አድኗል:: በፍጻሜው ወደ በርሃ ገብቶ በተጋድሎ ኑሮ በዚህች ቀን ዐርፏል::

 አምላከ ቅዱሳን የወዳጆቹን ሁሉ በረከትና ጸጋ ያብዛልን:: ለዓለምም ሰላሙን ይዘዝልን::

 ጳጉሜን 3 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት
1.ርኅወተ ሰማይ (የሰማይ መከፈት)
2.ቅዱስ ሩፋኤል ሊቀ መላእክት
3.ቅዱስ መልከ ጼዴቅ ካህን
4.አፄ ዘርዓ ያዕቆብ ንጉሥ (የእመቤታችን ወዳጅ)
5.ቅዱስ ሰራጵዮን ዘሰንዱን
6.ቅዱስ አኖሬዎስ
7.ቅዱስ ቴዎፍሎስ
8.አባ ዮሐንስ
9.ቅዱስ ጦቢት
10.ቅዱሳን ጦብያና ሣራ

 ወርኀዊ በዓላት
(የለም)

 "እውነት እውነት እላችኋለሁ:: ሰማይ ሲከፈት: የእግዚአብሔርም መላእክት በሰው ልጅ ላይ ሲወጡና ሲወርዱ ታያላችሁ::" 
(ዮሐ. ፩፥፶፪)

 ወስብሐት ለእግዚአብሔር 
ስንክሳር ዘወርኀ ጷጉሜ

No comments:

Post a Comment

Post Bottom Ad

Pages