የአምልኮት መልክ አላቸው ኃይሉን ግን ክደዋል፡፡ 2ኛጢሞ. 3÷5 - አትሮንስ ሚዲያ - Atrons Media

አትሮንስ ሚዲያ - Atrons Media

ስብኩ ወንጌለ ለኩሉ ፍጥረት ማቴ 16፤15


በቅርብ የተጻፉ

Post Top Ad

Saturday, October 8, 2022

የአምልኮት መልክ አላቸው ኃይሉን ግን ክደዋል፡፡ 2ኛጢሞ. 3÷5

 በዳንኤል ክብረት


 

ግን በመጨረሻው ቀን የሚያስጨንቅ ዘመን እንዲመጣ ይህን ዕወቅ፣ ከእግዚአብሔር ይልቅ ተድላን የሚወዱ ይሆናሉ፣

የአምልኮት መልክ አላቸው ኃይሉን ግን ክደዋል፡፡ 2ኛጢሞ. 3÷5

ለዘብተኛነት/ሊበራሊዝም/ በ18ኛው መክዘ መጨረሻ እና በ19ኛው መክዘ መጀመርያ ብቅ ያለ አስተሳሰብ ነው፡፡ ይህ አስተሳሰብ በፖለቲካው መስክ ግራ ዘመም አስተሳሰብ በመባል ይታወቃል፡፡ በደምሳሳው ልቅ በሆነ መብት እና ነጻነት የሚያምን፤ ነባር ባሕሎችን፣ ልምዶችን እና እምነቶችን በየጊዜው በመናድ ሰዎች ራሳቸውን አማልክት አድርገው እንዲያስቡ የሚያበረታታ አመለካከት ወይም ርእዮተ ዓለም ነው፡፡

ዛሬ በፖለቲካው መስክ ያለው ለዘብተኛነት ርእሰ ጉዳያችን አይደለም፡፡ የምንወያየው ስለ ለዘብተኛ/ሊበራል/ ክርስትና ነው፡፡

ሊበራል ክርስትና የግራ ዘመምን አስተሳሰብ በመያዝ በዚያው በ18ኛው መክዘ መጨረሻ እና በ19ኛው መክዘ መጀመርያ ብቅ ያለ አስተምህሮ ነው፡፡ ይህ አስተምሮ ፕሮቴስታንቲዝምን ሳይቀር አክራሪ /conservative/ ነው ብሎ የሚያምን እና በሃይማኖት ለሰው ልጅ ልቅ የሆነ መብት እና ነጻነት ሊሰጠው ይገባል በሚል የተነሣ ነው፡፡ በአሜሪካ እና በአውሮፓ አብዛኞቹ ፕሮቴስታንቶች እና ፓስተሮቻቸው በዚህ አመለካከት የሚመሩ ናቸው፡፡

ይህ አመለካከት የፕሮቴስታንቱን ዓለም ሃይማኖት አልባ ማድረጉ ሳያንሰው የካቶሊካውያንን እና የምሥራቅ እና የኦርየንታል አብያተ ክርስቲያናትን በር በማንኳኳት ላይ ይገኛል፡፡ በመገናኛ ብዙኃን እና በኤሌክትሮኒክስ ሚዲያው በየጊዜው ስለሚለፈፍ፣ ታላላቅ የሚባሉ ፖለቲከኞች እና የተከበሩ ሰዎች በየአጋጣሚው ስለሚያነሡት የሊበራል ክርስትና አስተሳሰብ እንደ ተስቦ በየሰው እየሠረፀ ነው ማለት ይቻላል፡፡ ሊበራል ክርስትናን እንዲህ እና እንዲያ ነው ብሎ ከመበየን መገለጫዎቹን ማቅረቡ ይበልጥ ግልጽ ያደርገዋል፡፡

የሊበራል ክርስትና አመለካከት ዋና ዋና መገለጫዎቹ የሚከተሉት ናቸው፡፡

መጽሐፍ ቅዱስ የእግዚአብሔር ቃል አይደለም ይላሉ

ሊበራል ክርስቲያኖች መጽሐፍ ቅዱስ በአንድ ወቅት የነበሩ ሰዎች ስለ እግዚአብሔር ምን እንደሚያምኑ የገለጡበት መጽሐፍ እንጂ የእግዚአብሔር ቃል አይደለም ብለው ያምናሉ፡፡ በመሆኑም ሊተች፣ ሊስተካከል፣ ሊታረም እና ሊቀየር የሚችል ጽሑፍ ነው ይላሉ፡፡ በዚህ አስተሳሰባቸው ምክንያትም ዛሬ ዛሬ ብዙዎቹ የፕሮቴስታንት አስተማሪዎች በትምህርታቸው ውስጥ መጽሐፍ ቅዱስ እንዲህ ማለት አልነበረበትም እያሉ ይተቻሉ፡፡ ወይም አንድ ሰው እንዳለው they want to re-write the bible፡፡ ሃይማኖታቸውም የግድ መጽሐፋዊ መሆን እንደሌለበት እና መጽሐፍ ቅዱስ የሃሳብ መነሻ ብቻ መሆን እንደሚችል ያስተምራሉ፡፡ በመሆኑም በየጊዜው አዳዲስ እና የተሻሻሉ የመጽሐፍ ቅዱስ ቅጅዎች እንዲታተሙ ያበረታታሉ፡፡

መጽሐፍ ቅዱስ ወጥ ትርጓሜ አያስፈልገውም ይላሉ

ሊበራሎች መጽሐፍ ቅዱስን ማንም ሰው እንደተመቸው እና እንደገባው መተርጎም ይችላል፡፡ አንድ ወጥ የሆነ እና «ትክክል ነው» ተብሎ ሊመሰከርለት የሚችል ትርጓሜ የለም ይላሉ፡፡ ይህም በሃይማኖት እና በአስተሳሰብ የተለያዩ ሚሊዮን ዓይነት የክርስትና ክፍልፋዮች እንዲፈጠሩ አድርጓል፡፡ ዶግማ እና ቀኖና የሚባል ነገር ስለሌላቸው ስለሚያመልኩት አምላክ እንኳንስ ሁሉም፣ በአንድ ጉባኤ የተገኙት እንኳን ተመሳሳይ እምነት የላቸውም፡፡ በማናቸውም ትምህርታቸውም ቢሆን የቀደሙ አበውን ትምህርት፣ ትርጓሜ እና ሐተታ አያካትቱም፡፡ ምናልባት መጽሐፍ ቅዱስን ይጠቅሱ ካልሆነ በቀር፡፡ የቅዱሳንን ሕይወትም አስረጂ አድርገው አይቆጥሩትም፡፡

በሃይማኖት ጉዞ ውስጥ አንድ ሊቋረጥ የማይገባው አንድነት «አሐተኔ» አለ፡፡ ይኸውም በአንድ ዘመን በሚኖሩ ክርስቲያኖች መካከል፣በአንድ ዘመን በሚኖሩ ወይንም በነበሩ ክርስቲያኖች እና ከእነርሱ በፊት በነበሩ ክርስቲያኖች መካከል፣እንዲሁም በአንድ ዘመን በሚኖሩ ወይንም በነበሩ ክርስቲያኖች እና ከእነርሱ በኋላ በሚመጡ ክርስቲያኖች መካከል የሃይማኖት አንድነት መኖሩ ነው፡፡ እኛ ከቀደሙ ክርስቲያኖች እና ወደፊት ከሚመጡ ክርስቲያኖች ጋር የሃይማኖት አንድነት ከሌለን «አንዲት ሃይማኖት፣ አንዲት ቤተ ክርስቲያን» ብለን መጥራት አንችልም፡፡

ሊበራሊዝም መጽሐፍ ቅዱስን እያንዳንዱ ሰው በራሱ መንገድ እንደፈለገ እንዲተረጉመው በመፍቀዱ የተነሣ በአንድ ዘመን በሚኖሩ ክርስቲያኖች መካከል የሃይማኖት አንድነት የለም፡፡ በአንድ ዘመን በሚኖሩ ክርስቲያኖች እና ከእነርሱ በፊት በነበሩ፣በኋላም በሚመጡ መካከል ያለውም አንድነት ፈርሷል፡፡

ትክክለኛም ሆነ የተሳሳተ ሃይማኖት የለም ይላሉ

ሊበራሎች «አንድ ሰው ትክክል ነው ብሎ እስካመነበት ድረስ ማንኛውም እምነት ትክክል ነው» ብለው ያስተምራሉ፡፡ ከኤፌሶን ምዕራፍ ሁለት «አንዲት እምነት» ከሚለው ትምህርት በተቃራኒ «የተሳሳተ ሃይማኖት የለም፤ ሁሉም ሃይማኖት እኩል እና ትክክል ነው፡፡ ልዩነቱ የሰዎች አስተሳሰብ ነው» ብለው ያስተምራሉ፡፡ በመሆኑም ልዩ ልዩ አመለካከት ያላቸው አማኞች በአንድ ጊዜ፣ በአንድ ቦታ ፣በጋራ ማምለክ ይችላሉ ብለው ያስባሉ፡፡

ይህ አስተሳሰባቸውም ሰዎች የራሳቸውን ፍልስፍና እንደ ሃይማኖት ትምህርት እየቆጠሩ በየጊዜው እንዲበታተኑ አድርጓቸዋል፡፡ ወደ ትክክለኛዋ መንገድ ከመመለስ ይልቅ ሁላችንም ትክክል ነን በሚል ፍልስፍና በስሕተቱ ጎዳና እንዲበረቱበት ረድቷቸዋል፡፡

የሚያስፈልገው ማኅበራዊ ወንጌል ብቻ ነው ይላሉ

የመጽሐፍ ቅዱስ ትምህርት ለማኅበራዊ ኑሮ፣ ለፍትሕ፣ ለዴሞክራሲ፣ ለሰብአዊ መብት እና ለእኩልነት መዳበር ከሚሰጠው ጥቅም አንጻር እንጂ በመሠረተ እምነት/ዶግማ/ ላይ ማተኮሩን ይቃወማሉ፡፡ ለስብከቱ ማራኪነት፣ አስደሳችነት እና ሳቢነት እንጂ ለትምህርቱ ትክክለኛነት አይጨነቁም፡፡ የነገረ ሃይማኖት ጉዳዮችን ማንሣት ሊለያየን ስለሚችል «ከዚህም ከዚያም ያልሆነ አቀራረብ» /neutral approach/ መጠቀም ያስፈልጋል ባዮች ናቸው፡፡ ትምህርታቸው መንፈሳዊ ሳይሆን ሥነ ልቦናዊ፣ ለማዳን ሳይሆን ለማስደሰት፣ እውነቱን ለመመስከር ሳይሆን ሰው እውነት የመሰለውን እንዲመርጥ ለማድረግ የታሰበ ነው፡፡ የዶግማ እና የቀኖና ትምህርት አይሰጡም፡፡

ዛሬ ዛሬ ይህ በሽታ እኛም ውስጥ ገብቶ ነው መሰለኝ ሰባክያን የተባልን ሰዎች ከዶግማ ትምህርት እየወጣን በስብከት ላይ ብቻ ወደማተኮር እየቃጣን ነው፡፡ በትምህርታችን ውስጥ እንኳን መሠረታዊ የሃይማኖት ትምህርትን በተገቢው መንገድ አናቀርብም፡፡ ምእመናንም ይህንኑ ለምደው መሠረታዊ ትምህርት ሲሰጥ እንደ ባከነ ጊዜ ይቆጥሩታል፡፡ በትምህርት አሰጣጣችንም ውስጥ የአበው ትምህርት፣ ትርጓሜ እና ሐተታ እየተረሳ፣ የቅዱሳንም ሕይወት በአስረጅነት መጠቀሱ እየቀረ ነው፡፡

ቤተ ክርስቲያን አልባ ክርስትናን ያስፋፋሉ

ሊበራል ክርስቲያኖች ቤተ ክርስቲያን ለድኅነት የግድ አስፈላጊ አይደለችም፡፡ ያለ ቤተ ክርስቲያን ክርስቲያን መሆን ይቻላል፤ ብለው ያምናሉ፡፡ አንድ ሰው ካመነ ክርስቲያን ለመሆን በቂው ነው፡፡ ስለዚህም ወደ ቤተ ክርስቲያን ሄዶ መጠመቅ፣ መቁ ረብ፣ መማር፣ መዘመር ወዘተ የግድ አያስፈልገውም ብለው ያስተምራሉ፡፡ ፕሮቴስታንቲዝም ሲጀመር «ሕንፃ ቤተ ክርስቲያን ከተራ ቤት እኩል ነው» ብሎ ተነሣ፣ ቀጥሎ ደግሞ ሊበራሎቹ «ያም ቢሆን አያስፈልግም» ብለው ደመደሙት፡፡ ውሻ በቀደደው አይደል ድሮስ ጅብ የሚገባው፡፡

በዚህ የተነሣም ብዙ ፕሮቴስታንቶች ወደ ቤተ ክርስቲያን አይሄዱም፣ አይሳተፉምም፡፡ ለምሳሌ በእንግሊዝ ሀገር 10% የሚሆኑ ክርስቲያኖች ብቻ ናቸው ቤተ ክርስቲያን እሑድ እሑድ የሚሄዱ፡፡ በስካንዴኒቪያን ሀገሮች ደግሞ ከ2 እስከ 3% ብቻ ይሄዳል፡፡ በአሜሪካ 60% ክርስቲያኖች ቤተ ክርስቲያን አይሄዱም፡፡ ከሚሄዱት ከ40% ብዙዎቹ ማኅበራዊ ጥቅማ ጥቅም ለማግኘት የሚሄዱ ናቸው፡፡ እንዲያውም በአሁኑ ዘመን ደግሞ «የኮምፒውተር ቤተ ክርስቲያን» online church የሚባል እየተከፈተ ነው፡፡ ስለዚህም በዳታ ቤዙ ላይ የኃጢአት ዝርዝር አለ፤ የሠሩትን ኃጢአት ከዳታ ቤዙ ውስጥ ገብተው ክሊክ ሲያደርጉ ቅጣቱን ይነግርዎታል፡፡

መዋቅር አልባ እምነትን ያስፋፋሉ

ሊበራሊዝም ማንኛውም ክርስቲያን በፈቀደው መንገድ እንዲያምን ስለሚያስተምር ማናቸውንም ዓይነት የሃይማኖት መዋቅሮች አይቀበልም፡፡ ሃይማኖታዊ መዋቅሮች ይኑሩ ከተባለም በዲሞክራሲያዊ መንገድ በሚመረጡ የቦርድ አባላት የሚመሩ እና ለብዙኃኑ ድምጽ ተገዥ የሆኑ መሆን አለባቸው ይላል፡፡ በዚህም የተነሣ የክህነትንም ሆነ የአስተዳደር እርከኖችን አይቀበልም፡፡ ጳጳሳት በካህናት ላይ፣ ካህናት በምእመናን ላይ ያላቸውን ሃይማኖታዊ ሥልጣን፣ እንዲሁም የቤተ ክርስቲያንን ሃይማኖታዊ እና አስተዳደራዊ ጉዳይ በመወሰን ረገድ ቅዱስ ሲኖዶስ ያለውን ሥልጣን አይቀበልም፡፡

በአሜሪካን ሀገር በ1960 እኤአ መሥመራውያን አብያተ ክርስቲያናት /main line protestants/ ከጠቅላላ ክርስቲያኑ 40% ይሸፍኑ ነበር፡፡ በ40 ዓመታት ውስጥ ግን በሊበራሎች ተነጥቀው ዛሬ 12% ብቻ ናቸው፡፡

ኑፋቄ የሚባል ነገር የለም ይላሉ

ሊበራሎች «የሁሉም ሰው ሃይማኖታዊ አመለካከት ትክክል ነው» ብለው ስለሚያምኑ ኑፋቄ የሚባል ነገር የለም ይላሉ፡፡ እንዲያውም ጥንት የተወገዙ መናፍቃን መብታቸው ተነክቷል ብለውም ያስባሉ፡፡ በቤተ ክርስቲያን ጉባኤያት የተለዩ የግኖስቲኮች መጻሕፍትን እንደ ገና ወደ ቤተ ክርስቲያን ለማስገባትም ይጥራሉ፡፡ መናፍቃንን በተመለከተ ምናልባት በዚያ ጊዜ የነበሩ አባቶች ተሳስተው ከሆነ ነገሩን እንደ ገና ማየት አለብን የሚል አመለካከት አላቸው፡፡ የበርናባስ ወንጌል፣ የይሁዳ ወንጌል፣ የማርያም መግደላዊት ወንጌል ወዘተ የተባሉና በግኖስቲኮች የተጻፉ የክህደት መጻሕፍት ዛሬ ዛሬ እንደ አዲስ ግኝት በመቸብቸብ ላይ ናቸው፡፡

መናፍቃንን መናፍቃን ማለተ ሰውን ማራቅ ነው፡፡ ስለ መናፍቃን ማውራት መለያየትን ማባባስ ነው፡፡ ስለ ራሳችን ብቻ እንናገር እንጂ ስለሌሎች አናንሣ፡፡ የሚሉት አመለካከቶች የልዩነቱን ድንበር አፍርሰው ክርስቲያኖች ስንዴውን እና እንክርዳዱን መለየት እንዳይችሉ የሚያደርጉ ናቸው፡፡

ለአዳዲስ አስተሳሰቦች ክፍት በር ይከፍታሉ

ሊበራሎች ለአዳዲስ አስተሳሰቦች በራችን ክፍት መሆን አለበት፣ አንድ ነገር አሳማኝ እስከሆነ ድረስ ልንቀበለው ይገባል ይላሉ፡፡ ዋናው ነገራቸው በቅዱሳት መጻሕፍት ትምህርት መሠረት ሳይሆን ምን ያህል ሕዝቡ ይቀበለዋል? በሚለው መሠረት ነው፡፡ በዚህ የተነሣም የተመሳሳይ ጾታ ጋብቻን፣ የሴቶችን ክህነት፣ የእንስሳትን አባልነት ወዘተ በመቀበል ላይ ናቸው፡፡ የሊበራሎች አንዱ መሠረታዊ አስተሳሰብ ዘመኑን በቅዱሳት መጻሕፍት መዋጀት ሳይሆን ቅዱሳት መጻሕፍትን ለዘመኑ ማመቻቸት ነው፡፡ በዚህ የተነሣ ቤተ ክርስቲያን በቅዱሳት መጻሕፍት ቃል እና በአባቶች ትምህርት ሳይመረመሩ አዳዲስ አስተሳሰቦች እንዲሁ የሚገቡባት ቤት መሆን አለባት ይላሉ፡፡

ግዴለሽነትን ያስፋፋሉ

ሊበራሎች ለጾም፣ ለጸሎት፣ ለሥነ ምግባር እና ለባሕል ግዴለሾች ናቸው፡፡ ሥርዓታዊ እምነት አይመቻቸውም፡፡ አንድ ሰው ክርስቲያን ለመሆን ከማመን እና ከማወቅ በላይ አያስፈልገውም ስለሚሉ ሌላ ዓይነት ሥርዓተ አምልኮን እንዲፈጽም አይገደድም፡፡ ጋብቻን ማክበር፣ ከሱስ ነጻ መሆን፣ ንጽሕናን መጠበቅ፣ ድንግልናን ማክበር፣ ወዘተ የሰው በጎ ፈቃድ እንጂ የሃይማኖት ትምህርት ናቸው ብለው አይወስዷቸውም፡፡ ስለዚህም አማኞች ትክክለኛ ኑሮ እና የተሳሳተ ኑሮ፣ሥነ ምግባራዊ እና ኢሥነ ምግባራዊ የሚባለውን ለይተው እንዲያውቁ እና እንዲኖሩ አይነገራቸውም፡፡

No comments:

Post a Comment

Post Bottom Ad

Pages