ስንክሳር_ዘወርኀ_ጥቅምት 9 - አትሮንስ ሚዲያ - Atrons Media

አትሮንስ ሚዲያ - Atrons Media

ስብኩ ወንጌለ ለኩሉ ፍጥረት ማቴ 16፤15


በቅርብ የተጻፉ

Post Top Ad

Friday, October 21, 2022

ስንክሳር_ዘወርኀ_ጥቅምት 9

 

 
 
አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም
ጥቅምት ዘጠኝ በዚህች ዕለት #የአባ_ሊዋርዮስ እና #የአቡነ_አትናስዮስ እረፍታቸው ነው፣ በዲዮቅልጢያኖ ዘመን የመጀመሪያ የሆነው ሰማዕት #ቅዱስ_እስጢፋኖስ_ዘአንጾኪያ በሰማዕትነት አረፈ፤ #ሐዋርያው_ቅዱስ_ቶማስ በሕንድ አገር ድንቅ ተአምር ያደረገበትም ዕለት ነው ዳግመኛም ኢትዮጵያዊው ጻድቁ #አቡነ_መዝገበ_ሥላሴ እረፍታቸው ነው።

በዚች ቀን ቅዱስ አባት የሮሜ አገር ሊቀ ጳጳሳት ሊዋርዮስ አረፈ። ይህም ዕውነተኛ ደግ ንጹሕ የሆነ ሰው በታናሽነቱ መንኲሶ የቤተ ክርስቲያንን ትምህርት እየተማረ በቤተክርስቲያን ግቢ አደገ። በሮሜ አገርም በሐዋርያት አለቃ በጴጥሮስ ወንበር ላይ ሊቀ ጳጳሳት ሊሆን መርጠው ሾሙት።
በጎ መንገድንም በመጓዝ እግዚአብሔርን አገለገለው ሕዝቡን አዘውትሮ ያስተምራቸው ነበርና ከእግዚአብሔርም ሕግና ትእዛዝ የተላለፉትን መክሮ ገሥጾ ወደ እግዚአብሔር ሕግ ይመልሳቸው ነበርና። ታናሹ ቁስጠንጢኖስም በሞተ ጊዜ ከሀ*ዲው ዑልያኖስ ነገሠ እግዚአብሔርም እስከ አጠፋው ድረስ የክርስቲያንን ወገኖች አሠቃያቸው።
ይህም ዑልያኖስ ለቈስጠንጢኖስ የአባቱ እኅት ልጅ ነው መንግሥትንም በያዘ ጊዜ የጣዖታትን ቤቶች በመክፈት የክርስቲያንን ወገኖች ሁሉ አሠቃያቸው። ይህ አባት ሊዋርዮስም ከሮሜ አገር ወደ ቂሣርያ መጣ ከቅዱስ ባስልዮስም ጋር ተገናኘ። ከታላቅ ስሕተቱና ከክህ*ደቱ መክረው ይመልሱት ዘንድ ወደ ንጉሥ ዑልያኖስ ለመሔድ ሁለቱ ተስማሙ። እነርሱ ከታናሽነታቸው ጀምረው እየተማሩ ከእርሱ ጋር በአንድነት ያደጉ ናቸውና።
ከዚህም በኋላ ተነሥተው ሔዱ ንጉሥ ዑልያኖስም ወዳለበት ደርሰው ከፊቱ ቆሙ ከስሕተቱም በሚመልሱበት ሊናገሩት ወደው ሳለ እርሱ ቀድሞ በጌታችን ላይ በመሣለቅ ክብር ይግባውና የጠራቢውን ልጅ ወዴት ተዋችሁት አላቸው። ቅዱስ ባስልዮስም አንተን በሲኦል ይቀብሩህ ዘንድ ሣጥን ሊሠራልህ ተውነው ብሎ መለሰለት። በዚያንም ጊዜ በእነርሱ ላይ ተቆጥቶ በወህኒ ቤት እንዲያሥሰሯቸው አዘዘ።
በዚያም የቅዱስ መርቆሬዎስን ሥዕሉን አግኝተው በፊቱ እያለቀሱ የክርስቶስ ምስክር ሆይ በክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ላይ የዚህን ከሀዲ መሣለቁን አትሰማምን ብለው ጸለዩ ይህንንም ሲጸልዩ ያን ጊዜ አንቀላፉ። አባ ሊዋርዮስም በእንቅልፉ ውስጥ ሳለ ቅዱስ መርቆሬዎስን ሰማይና ምድርን በፈጠረ በሕያው ፈጣሪዬ ላይ እንዲሣለቅ ይህን ከሀዲ በሕይወት አልተወውም ሲል በሕልሙ አየው።
ከእንቅልፉ ነቅቶ ያየውን ለቅዱስ ባስልዮስ ነገረው በዚያንም ጊዜ ሥዕሉን ከቦታው አጡት እርሱ ዑልያኖስ ወዳለበት ሒዶአልና በጦርም ወግቶ ገደለው ወደ ቦታውም ተመልሶ ተሰቀለ ከጦሩ አንደበትም ደም ይንጠፈጠፍ ነበር።
እሊህ ቅዱሳንም ይህን ድንቅ ሥራ በአዩ ጊዜ መፈራትንና ባለሟልነትን የተመላህ የኢየሱስ ክርስቶስ ምስክር ሆይ ዑልያኖስን ገደልከውን አሉ ። ያን ጊዜ አዎን እንደሚል ሥዕሉ ዘንበል አለ እሊህም ቅዱሳን ሊዋርዮስና ባስልዮስ ደስ አላቸው።
ከዚህም በኋላ ክብር ይግባውና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን የሚያምን ዩማንዮስ ነገሠ እሊህንም ቅዱሳን ከእሥር ቤት አወጣቸውና ወደየቦታቸው ተመለሱ። ይህም አባት ሊዋርዮስ አርዮሳውያንን እጅግ ይጣላቸው ነበር። ከክርስቲያን ወገኖችም ለይቶ ያሳድዳቸዋል።
መልካም ጒዞውንም ከፈጸመ በኋላ እግዚአብሔርን አገልግሎ በሰላም አረፈ። የሹመቱም ዘመን ሰባት ዓመት ነው።

በዚችም ቀን ዳግመኛ የከበረ የአንጾኪያ ሊቀ ጳጳሳት አባ አትናስዮስ አረፈ ። ይህም ቅዱስ ከታናሽነቱ ጀምሮ መነኰሰ ባሕታዊም ሁኖ የሚያገለግል ቅን ትሑት በበጎ ሥራ ሁሉ ፍጹም ሆነ ።
ሊቀ ጳጳሳት አባ ሚካኤልም ከአረፈ በኋላ ኤጲስቆጶሳት ሁሉም ተሰበሰቡ ይህንንም አባት ሊቀ ጵጵስና ይሾሙት ዘንድ መረጡት ። ፈጥኖም እንዲመጣና ከእነርሱ ጋር ይህን አባት እንዲሾም ወደ ሀገረ ሰልቅ ሊቀ ጳጳስ ወደ አባ እልመፍርያን ላኩ እርሱ ግን መምጣትን ዘገየ። እነርሱም ኃምሳ ቀኖች ያህል ጠብቀው አባ አትናስዮስን ሹመውት ወደየሀገረ ስብከታቸው ተመለሱ። ከዚህም በኋላ በላኩበት መሠረት ሊቀ ጳጳስ አባ እልመፍርያን መጣ ወደ ሶርያም ድንበር ሀገረ ዓምድ ደርሶ ከአንድ ጳጳስ ጋር ተገናኘ። ያም ጳጳስ እርሱ ከመምጣት በዘገየ ጊዜ አባ አትናስዮስን እንደ ሾሙት ነገረው በሰማም ጊዜ እጅግ ተቆጣ እንዲህም አለ በእኛና በእናንተ መካከል ያለውን ሕግ እንዲህ ትሽራላችሁን ይህንንም ብሎ በቊርባንም ቢሆን ወይም በማዕጠንት የአባ አትናስዮስን ስም የሚጠራውን ሁሉ አውግዞ ወደ ሀገሩ ተመለሰ።
አባ አትናስዮስም ይህን ነገር በሰማ ጊዜ እጅግ አዘነ ረዳቱንም ጠርቶ እንዲህ አለው ልቤ ትባርክህ ትመርቅህ ዘንድ ታዘዝልኝ ሕዝቡ የፈለጉኝ እንደሆነ በዋሻ ሱባዔ ውስጥ ነው በላቸው እኔ ወደ አንድ ቦታ ሔጄ አንድ ዓመት ያህል እቆያለሁና አንተም ሊሆን በሚገባ ሥራ ሁሉ እዘዛቸው በእኔም ፈንታ እሠር ፍታ ረዳቱም እሺ አለው ።
ከዚህም በኋላ አባ አትናስዮስ የድኃ ልብስ ለብሶ በሥውር ወጣ በእግሩም ሒዶ ወደ ሀገረ ሰልቅ ደረሰ ። የሊቀ ጳጳስ አባ እልመፍርያንን ደጅ አንኳኳ በረኛውም ምን ትሻለህ አለው ከአባት ሊቀ ጳጳስ ቡራኬ እሻለሁ ብሎ መለሰለት ነግሮለትም አስገባው አባ እልመፍርያን አንተ ከወዴት ነህ አለው ። እርሱም ከሶርያ አገር ነኝ የዕለት ሲሳይና ልብስ አጥቼ መጣሁ በጥላህም ሥር ሁኜ ላገለግል እሻለሁ ብሎ መለሰ ።
ሁለተኛም ቄስ ነህን ወይስ ዲያቆን አለው እርሱም አይደለሁም አለ ሹሙንም ጠርቶ ከመነኰሳቱ ጋር እንዲአኖረው አዘዘው ።
አባ አትናስዮስም የሊቀ ጳጳሱን የቤት ውስጥ ሥራ የፈረሶችንና የበቅሎዎችን ፍግ እስከሚጠርግ የሚሠራ ሆነ ይፈጫል ውኃ ይቀዳል እንጀራ ይጋግራል ወጥ ይሠራል ምንም ምን ሥራ አይቀረውም። እንዲሁም ለመነኰሳቱ ቤቶቻቸውን ይጠርግላቸዋል ውሀንም ይቀዳላቸዋል እሳትንም ያነድላቸዋል እጅግም ስለ ወደዱት እንደ ሰማያዊ መልአክ አስመሰሉት።
ከዚህም በኋላ አትናስዮስን ዲቁና ይሾመው ዘንድ ሊቀ ጳጳሱን መነኰሳቱ ማለዱት በእሑድም ቀን አባ እልመፍርያን ወደ ቤተ ክርስቲያን ገብቶ ዲቁና ሊሾመው አባ አትናስዮስን ጠራው እርሱም አልቅሶ አባቴ ሆይ ተወኝ እኔ ድኃ ነኝና አለው ባልተወውም ጊዜ አባቴ ይቅርታ አድርግልኝ ይህስ ዲቁና አለኝ አለው። ሊቀ ጳጳሱም ከትዕግሥቱና ከትሕትናው የተነሣ አደነቀ በዲቁናም እንዲአገለግል አዘዘው በዲቁና እያገለገለ ሰባት ወር ኖረ።
ሊቀ ጳጳሱም አዋቂነቱን አይቶ ቅስና ሊሾመው ወደደ በእሑድ ቀንም ወደ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ ጠርቶ መንፈስ ቅዱስ ቅስና ሊሾምህ ጠርቶሃል አለው አባ አትናስዮስም ሰምቶ አለቀሰ እንዲተወውም ማለደው። ባልተወውም ጊዜ አባቴ ይቅር በለኝ እኔ ቄስ ነኝ አለ መነኰሳቱም ሁሉ አደነቁ በእርሱም ደስ አላቸው።
አባ እልመፍርያንም አስተዋይነቱን የአንደበቱን ጣዕም የተደራረበ አገልግሎቱንም ተመልክቶ ጳጳስዋ ለሞተባት ለአንዲት አገር ጵጵስና ሊሾመው ወደደ። ጳጳሳትንና ኤጲስቆጶሳትን ቀሳውስትንና ዲያቆናትንም በእሑድ ቀን ሰበሰባቸው አባ አትናስዮስንም አቅርበው እንዲህ አሉት ለዕገሌ ሀገረ ስብከት ጳጳስ ልትሆን ዛሬ መንፈስ ቅዱስ ጠርቶሃል አሉት። እርሱም ሰምቶ አለቀሰ እንዲተዉትም አልቅሶ አማላቸው እንደማይተውትም በአወቀ ጊዜ እርሱ የአንጾኪያ ሊቀ ጳጳሳት አትናስዮስ እንደሆነ ነገራቸው የአመጣጡንም ምሥጢር ገለጸላቸው።
በዚያን ጊዜ አባ አልመፍርያን ደነገጠ አክሊሉንም ከራሱ ላይ አውልቆ በምድር ላይ ወደቀ ለረጅም ጊዜ እንደ ሞተ ሆነ በተነሣም ጊዜ እንዲህ ብሎ ጮኸ ወንድሞቼ የማደርገውን እስቲ ንገሩኝ ዛሬ እሳት ከሰማይ ወርዶ እንዳያቃጥለኝ ምድርም አፍዋን ከፍታ እንዳትውጠኝ እፈራለሁና ጌታዬ የአንጾኪያ ሊቀ ጳጳሳት አትናስዮስ ውኃ እየቀዳ የፈረሶችና የበቅሎዎች ጉድፍ እየጠረገ በቤቴ ውስጥ እንደ ባርያ ሊአገለግል አግባብ ነውን ወዮልኝ ወዮልኝ።
ጳጳሳቱና የተሰበሰቡት ሁሉ በሰሙ ጊዜ ከእግሩ በታች ወድቀው ሰገዱለት እጆቹንና እግሮቹንም ሳሙ ሊቀ ጳጳሱም ያማሩ የክህነት ልብሶችን ያለብሱት ዘንድ መስቀሎችንና አርዌ ብርቱን ያመጡ ዘንድ በመንበር ላይም ያስቀመጡት ዘንድ አዘዘ።
ከዚያም በኋላ ጳጳሳቱ ከመንበሩ ጋር ተሸከሙት ሦስት ጊዜ አክዮስ አክዮስ አክዮስ እያሉ ይህም ይገባዋል ማለት ነው ቤተ ክርስቲያኑን አዙረው ወደ መቅደስ አስገቡት ።
ከዚህም በኋላ መቀደሻ ልብስ ለብሶ መሥዋዕቱን አክብሮ ቀድሶ አቈረባቸው እነርሱንም ሀገራቸውንም ባረከ ለዚያችም አገር ምንኛ መጠን የሌለው ደስታ ሆነ ተባለ ።
በማግሥቱም አባ እልመፍርያን ተነሥቶ በቅሎ አስመጣ ለጒዞ የሚያሻውን ሁሉ አዘጋጀ አባ አትናስዮስንም በበቅሎ አስቀምጦ እርሱ በእግሩ ተከተለው ጳጳሳቱና ኤጲስቆጶሳቱ ሁሉም ከአባ እልመፍርያን ጋር አጅበዉ ወደ አንጾኪያ አገር ወሰዱት አባት አትናስዮስም አባ እልመፍርያንን አንተም በበቅሎ ላይ ተቀመጥና በአንድነት እንሒድ አለው። አባ እልመፍርያንም ጌታዬ ለእኔ አይገባኝም አንተ በእግርህ ወደ አገሬ እንደመጣህ እንዲሁ እኔም በእግሬ ወደ አገርህ አደርስሃለሁ አለው።
የአንጾኪያ አገር ጳጳሳትም የሊቀ ጳጳሳት አትናስዮስን መምጣት በሰሙ ጊዜ ከሕዝብ ሁሉ ጋር ሊቀበሉት ወጡ በታላቅም ክብር ተቀብለው ወደሹመቱ መንበር አስገቡት። ለአባ እልመፍርያንም ሁለተኛ ወንበር አድርገው በክብር አስቀመጡት በዚያችም ቀን ፈጽሞ ደስ አላቸው ተሰናብተውትም ወደ ሀገራቸው በፍቅር አንድነት ተመለሱ። ይህም አባት አትናስዮስ በጎ አኗኗርን ኖረ መንጋውንም በትክክል በእውነት ጠበቀ በጎ ጒዞውንም ፈጽሞ በሰላም አረፈ ።

በዚችም ቀን በከሀዲው ዲዮቅልጥያኖስ ዘመን በአንጾኪያ አገር የሰማዕታት መጀመሪያ ሁኖ ሌላው እስጢፋኖስ በሰማዕትነት አረፈ ።
ይህም የፋሲለደስ ወንድም ለሆነ የኒቆምዮስ ልጅ ነው በወገንም የከበረ ነው አባቱም ከአንጾኪያ ታላላቆች ወገን ሁኖ በወርቅ በብር በወንድ ባሮች በሴት ባሮች እጅግ የበለጸገ ነው ክብር ይግባውና ክርስቶስንም እጅግ ይፈራዋል ይወደዋልም ለድኆችና ለችግረኞች አብዝቶ ይመጸውታል በሰው ሁሉ ዘንድ ተወዳጅ ነው ።
ይህንንም ቅዱስ እስጢፋኖስን በወለዱት ጊዜ በበጎ ተግሣጽ በምክር አሳደጉት በጀመሪያም የዳዊትን መዝሙር ከዚያም የብሉይና የሐዲስ መጻሕፍትን የመንፈስ ቅዱስ ዕውቀት በላዩ እስቲመላ ድረስ አስተማሩት ።
ሁለተኛም ሥጋዊ ጥበብ ፈረስ መጋለብን ጦር መወርወርን በፍላፃ መንደፍን በቅዱስ ፋሲለደስ ቤት ሁኖ ከቅዱሳን ፊቅጦርና ገላውዴዎስ ጋር ተማረ ለፋሲለደስ የወንድሙ ልጅ ነውና ስለዚህም የፋሲለደስ ልጅ ይባላል ።
ዘመዶቹም ሁሉ እግዚአብሔርን የሚፈሩ ናቸው በሕጉ በትእዛዙ በአምልኮቱ ሁሉ የጸኑ ናቸው ። ከውስጣቸውም ክብር ይግባውና ከክርስቶስ የፍቅር ትኲሳት ልቡን የሚያቀዘቅዝ ወደ ቀኝ ቢሆን ወደ ግራም ፈቀቅ የሚል የለም ።
ጌታችንም ለእርሱ ያላቸውን የፍቅራቸውን ጽናት በአየ ጊዜ ዓለም ሳይፈጠር ያዘጋጀላቸውን መንግሥቱን ሊአወርሳቸው ወደደ ። ከዚህም በኋላ የግብጽ አገር ወደ ሆነ የፍየል ጠባቂ በጦርነት ምክንያት ወደ መለመሉት ስሙ አግሪጳዳ ወደ ሚባል ሰው ሰይጣን መጥቶ አደረበት ወደ አንጾኪያም በደረሰ ጊዜ የመንግሥት ፈረሶች ባልደራስ አደረጉት ።
የአንጾኪያም ንጉሥ በሞተ ጊዜ መንበሩ ከንጉሥ ተራቆተ በአንዲት ዕለትም የንጉሡ ሴት ልጅ በቤቷ ደርብ ስትመላለስ ሲዘፍን አየችው እርሱም ለፈረሶች ክራርና መሰንቆ ሲመታላቸው እንደሚዘፍን ሰው ሁነው ያሽካኩ ነበር ። ስለዚህ ወደደችውና ባል አድርጋ አነገሠችው ስሙንም ዲዮቅልጥያኖስ ብላ ሰየመችው ።
ያን ጊዜ በዘመኑ ለተደረገ ዓመፅና ግፍ ወዮ ምን ዓይነት ዓመፅና ግፍ ነው ። ክብር ይግባውና ክርስቶስን ከካደው በኋላ ጣዖታትን አመለከ በክርስቶስም ያመነውን ሁሉ ገደለ እንደ ነጣቂዎች አራዊትም የሰውን ሥጋ የሚበላ ደማቸውንም የሚጠጣ ሆነ ። የተመረጡ የመንግሥት ልጆችን ሁሉ እረኛ እንደ ሌላቸው በጎች በተናቸው ከእነርሱ ውስጥ በችንካሮች ቸንክሮ የገደላቸው አሉ በማረጃ አርዶ የገደላቸው በጦር ወግቶ በእሳትም አቃጥሎ የገደላቸው አሉ አሥሮ አፋቸውንም በልጓም ለጉሞ ወደ ግብጽ አገሮች እስከ ሰደዳቸው ድረስ ልቅሶና ዋይታም በአንጾኪያ አገር እስከመላ ድረስም ባል ስለ ሚስቱ ሚስትም ስለ ባልዋ እናትና አባት ስለ ልጆቻቸው ልጆችም ስለ ወላጆቻቸው ሰዎችም ሁሉ ስለ ወገኖቻቸው የቅዱሳን ሰማዕታትም ሥጋቸው በሀገሩ ጥጋጥግ የወደቀ ሆነ ። ለጠባቂዎች ገንዘብ ሰጥተው በሥውር ወስደው ከሚቀብሩአቸው በቀር ቀባሪ የላቸውም ።
ይህም ቅዱስ እስጢፋኖስ የምስክርነት አክሊልን ይሰጠው ዘንድ ወደ እግዚአብሔር ሲጸልይ ኖረ ።
የመጀመሪያዪቱ ቀን ንጉሥ ዲዮቅልጥያኖስ በግዛቱ ውስጥ ላሉ አገሮች ሁሉ አብያተ ክርስቲያናት እንዲዘጉ የጣዖት ቤቶች እንዲከፈቱና እንዲአመልኳቸው እነርሱ በጦርነት ውስጥ ድል አድራጊነትን ይሰጡናልና ይህንንም ትእዛዝ የሚቃወምና እምቢ የሚል ቢኖር ንብረቱ ይወረስ በየአይነቱ በሆነ ሥቃይ ይሠቃይ ርኅራኄ በሌለው አሟሟት እስኪሞት ብሎ የሚያዝ የአዋጅ ደብዳቤ ጻፈ ።
የመንግሥቱን ታላላቆች ሁሉ ሕዝቡንም ታላቁንም ታናሹንም ሰበሰባቸው ። ይቺ የረከሰች ደብዳቤም በተሰበሰቡት ፊት ትነበብ ዘንድ አዘዘ ቅዱስ እስጢፋኖስም በሰማ ጊዜ ስለ ቀናች ሃይማኖት በክርስቶስ ፍቅር እሳትነት ልቡ ነደደ ።
ዲዮቅልጥያኖስንም ተመለከተው እንደ ኢምንትም አደረገው። እንዲህም አለው ንጉሥ ሆይ አጵሎንን ያመልኩ ዘንድ የምታዝ ይቺን የረከሰች ደብዳቤ በመጻፍህ የምታሳየው ይህ ዓመፅ ምንድን ነው ይህንንም ሁሉ ያጠፋው ዘንድ ክብር ይግባውና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አለ ይህንንም ብሎ ይችን የረከሰች ጽሑፍ በያዘ ወታደር ላይ ተወርውሮ ነጠቀውና ቀደዳት በጣጥሶም ጣላት ።
ንጉሡም ቅዱስ እስጢፋኖስን ይህ የምትሠራው ምንድር ነው ለራስህ ጥፋትን አምጥተሃልና አለው ከዚህም በኋላ ሰይፉን መዝዞ መታውና ከሁለት ከፈለው የቅዱስ እስጢፍኖስም ራስ ለረጅም ጊዜ በንጉሥ ፊት ሁና በክርስቲያን ወገኞች ላይ የሚደረገውን ሁሉ ግፍ ዳግመኛም በስተኋላ በንጉሡ ላይ የሚመጠበትን ዐይኖቹ እንደሚታወሩ ምጽዋትንም እንደሚመጸወት ከዚያም በኋላ እንደሚጠፋ ተናገረች።
ከዳተኛ ንጉሥ ሄሮድስን የምጥምቁ ቅዱስ ዮሐንስ ራስ እንደ ዘለፈችው የቅድስ እስጢፋኖስም ራስ ዲዮቅልጥያኖስን ስትዘልፈው ያዩዋት ዘንድ ብዙ ሕዝቦች የሚመጡ ሆኑ ሄሮድስና ዲዮቅልጥያኖስ አንድ ጠባይ ናቸውና በከፋች ሥራቸውም አይለያዩም።
ሴቶች ከወለዱአቸው የሚመስለው የሌለ የልዑል ነቢይ የሆነ ጻድቅ ሰውን ሄሮድስ በገደለው ጊዜ ዝሙቱ እንዳይገለጽ ሽቶ ነበር ስለዚህም ተልቶ ተበላሽቶ እስኪሞት ሚስቱንም ምድር እስከ ዋጠቻት ልጅዋም እስከ አበደች ድረስ ጉስቍልና አገኘው የመጥምቁ ቅዱስ ዮሐንስ ራስም ዝሙቱን ግልጽ አድርጋ ዘለፈችው።
ይህም ጐስቋላ ዲዮቅልጥያኖስ የረከሱ የጣዖታትን አምልኮ ሊገልጥ የማይደበቅ የሕያው እግዚአብሔርን አምልኮ ሊደብቅ ወዶ የቅዱስ እስጢፍኖስን ራስ ቆረጠ የቅዱስ እስጢፍኖስ ራስ ግን ዘለፈችው አማልክቶቹም የርኩሳን አጋንንት ማደሪያዎች እንደ ሆኑ ገለጠች አሳፈረችውም ።
በምድርም ውስጥ እንዲደፍኑዋት አዘዘ ። እርሷም በምድር ውስጥ ተደፍና ሳለች ዝም አላለችም ሦስት ቀን ያህል አብዝታ እየተናገረች ትዘልፈው ነበር ሕዝቡም ሁሉ ይሰሟታል እጅግም አፈረ ከእርሳስም ሣጥን ውስጥ እንዲጨምሯትና ሣጥኑን አሽገው ከጥልቅ ባሕር ውስጥ እንዲጥሉት አዘዘ በዚያንም ጊዜ የእግዚአብሔር መልአክ ወረደ ሣጥኑንም ከባሕር አውጥቶ በባሕሩ ዳር አኖረው ።
እናቱም ሥጋውን እየፈለገች በእግዚአብሔር ፈቃድ ከዚያ ደረሰች አግኝታውም ዘመን እስቲያልፍ በሥውር ቦታ አኖረችው በፊቱም መብራት አኖረች የመከራውም ወራት ከአለፈ በኋላ ያማረች ቤተ ክርስቲያን ተሠራችለት ከእርሱም ታላላቅ ድንቆች ተአምራት ተገለጡ።

በዚችም ቀን በሕንድ አገር ቅዱስ ሐዋርያ ቶማስ ላደረገው ድንቅ ተአምር መታሰቢያ ሆነ ።
ይህም እንዲህ ነው ሐዋርያ ቶማስ እንደ ባሪያ ተሽጦ ወደ ሕንድ አገር ከአበኒስ ጋር በገባ ጊዜ አበኒስ ወደ ንጉሥ ጎንዶፎር አቀረበውና ሐናፂ እንደሆነም ለንጉሡ ነገረው ንጉሡም ስለሚችለው ሙያው ሐዋርያውን ጠየቀው ቅዱስ ሐዋርያ ቶማስም እንዲህ ብሎ ለንጉሥ መለሰለት እኔ የጥርብ ሥራን ሁሉ ቀንበሮችን ሚዛኖችን ሠረገላዎችን መርከቦችን በግንብ ሥራም ቤተ መንግሥትን እሠራለሁ ንጉሡም እጅግ ደስ አለው ።
ቤተ መንግሥቱንም እንዲሠራለት ከሚሻው ቦታ ወሰደውና በምን ወር ትሠራለህ አለው ሐዋርያውም ከኅዳር መባቻ ጀምሬ በሚያዝያ ወር እጨርሳለሁ አለው ። ንጉሡም አድንቆ ሕንፃ ሁሉ በበጋ ይታነፃል አንተ ግን እንዴት በክረምት ወር ታንፃለህ አለ ሐዋርያም ስለዚህ ነገር ችግር የለም አለ ።
ከዚህም በኋላ ንጉሡ ለራሱና ከእርሱ ጋር ለሚሠሩ ሠራተኞች የሚሆን ብዙ ገንዘብን ሰጠው ቅዱስ ሐዋርያ ቶማስም ተቀብሎ ሔደ ። የንጉሥን ለንጉሥ እሰጣለሁ እያለ ለድኆችና ለምስኪኖች መጸወተው ዳግመኛም የቤተ መንግሥቱ ግድግዳው ተፈጽሞ ጣሪያው ቀርቷል ብሎ ወደ ንጉሡ ላከ ። ያን ጊዜም ንጉሥ ብዙ ገንዘብ ላከለት ሐዋርያውም ተቀብሎ እንደ ልማዱ መጸወተው ።
ከዚህም በኋላ ንጉሡ በመጣ ጊዜ ስለ ቤተ መንግሥቱ ሕንፃ ጠየቀ ምንም የተሠራ ነገር አላገኘም ነገር ግን ገንዘቡ ለድኆች ምጽዋት ሁኖ እንደተበተነ ሰማ ። እጅግም ተቆጣ በሚገለውም ነገር እስቲመክር ድረስ ሐዋርያ ቶማስን ከአመጣው ከአበኒስ ጋር አሠረው ።
በዚያችም ሌሊት የንጉሡ ወንድም ጋዶን በደንገት ታመመና ሞተ መላእክትም ነፍሱን ወስደው ተመሳሳይ የሌለው በወርቅና በዕንቍ የተሠራ ቤተ መንግሥትን አሳዩዋት ። ጋዶንም መላእክትን ይህ ቤተ መንግሥት የማነው አላቸው መላእክትም ለጋዶን ሐዋርያ ቶማስ ለንጉሥ ጎልዶፎር የሠራለት ነው አሉት ከዚህም በኋላ ጋዶን ከሙታን ተለይቶ ተነሣ ያየውንም ሁሉ ለወንድሙ ለንጉሥ ጎልዶፎር ነገረው ። በዚያንም ጊዜ ወደ እሥር ቤት ሮጡ ቅዱስ ሐዋርያ ቶማስንም አበኒስንም ከወህኒ ቤት አወጡአቸው ። ለሐዋርያውም ሰገዱለት የሀገር ሰዎችም ሁሉ ከንጉሥ ጎልዶፎር ጋር አመኑ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም ተጠመቁ የጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስንም ቅዱስ ሥጋውንና ደሙን አቀበላቸው ። ከዚህም በኋላ ባረካቸውና ከእርሳቸው ዘንድ ወጥቶ ወደ ሌላ ቦታ ሔደ ።

አቡነ መዝገበ ሥላሴ በታሪካዊነቱና በያዛቸው ድንቅ ድንቅ ቅርሶች ከሚታወቀውና ኢትዮጵያዊውን ሀሳበ ዘመን በመቀመር ከሚታወቀው ከእውነተኛው የብህትውና ቦታ ከደብረ ገሪዛን ቅድስት ማርያም ጉንዳጉንዶ ገዳም የተገኙ ታላቅ አባት ናቸው፡፡ እነ አቡነ አበከረዙንን ጨምሮ የባሕረ ሐሳብ ፍልስፍናና የሥነ ጽሑፍ ማዕከል ከሆነው ከዚህ ገዳም የወጡ ገድል ተጽፎላቸው፣ ታቦት በስማቸው የተቀረጸላቸው ከ17 በላይ ታላላቅ ቅዱሳን አሉ፡፡ አቡነ መዝገበ ሥላሴም ከእነዚህ የበቁ ቅዱሳን ውስጥ አንዱ ናቸው፡፡ አባታቸው ሀብተ ጽዮን እናታቸው ማርያም ሞገሳ ሲባሉ እነርሱም በእግዚአብሔር ፊት ቅኖች ነበሩ፡፡
ማርያም ሞገሳ ዕለት ዕለት አምሃ(ስጦታ) እየያዘች ወደ ቤተ ክርስቲያን እየሄደች ስትጸልይ በአንደኛው ዕለት የታዘዘ መልአክ መጥቶ ‹‹በእግዚአብሔር ፊት ሞገስ ያገኘና የተባረከ ልጅ ትወልጃለሽ›› ብሎ አበሰራት፡፡እርሷም ‹‹ከማኅፀኔ እንደፀሐይ የሚያበራ ልጅ ሲወጣ አየሁ›› አለች፡፡ በዚህም መሠረት አቡነ መዝገበ ሥላሴ በምሥራቃዊ ትግራይ ዞን በገላውዴዎስ ዘመነ መንግሥት በ1532 ዓ.ም ተወለዱ፡፡ በ40ኛ ቀናቸውም ሲጠመቁ ሰጊድለአብ ተባሉ፡፡ ሰጊድለአብ ከዕለታት በአንደኛው ቀን የእግዚአብሔር መልአክ ከእናታቸው እቅፍ ውስጥ ነጥቆ ወስዶ ደብረ ከስዋ (ደብረ ገሪዛን) ጉንዳጉንዶ ቅድስት ማርያም ገዳም አደረሳቸው፡፡ ወደ ቅድስተ ቅዱሳኑም ካስገባቸው በኋላ በውስጥ የነበሩትን ንዋያት ሁሉ እያሳየ ‹‹አንተ ሕፃን ሆይ! ዕወቅ ይህ የምታየው ሁሉ የአንተ ነው፣ ትጠብቀውም ዘንድ እግዚአብሔር ሰጥቶሃል፡፡ ደግሞም የክርስቶስን በጎች ትጠብቅ ዘንድ ተሰጥቶሃልና ፈጽሞ ደስ ይበልህ›› አላቸውና ፈጥኖ ወደ እናታቸው እቅፍ መለሳቸው፡፡ ዕድሜአቸውም ለትምህርት ሲደርስ ወደ ጉንዳጉንዶ ተመልሰው የሁሉንም መጻሕፍትን ምሥጢር ጠንቅቀው ተማሩ፡፡ በገዳሙም የምንኩስናን ሥራ እየሠሩ በተጋድሎ ኖሩ፡፡ ክብርት እመቤታችንም ተገልጻላቸው ‹‹ልጄ በተፈቀደልህ ተጋድሎ አሰልጥኖሃልና ጨክን፣ በርታ እኔም ከአንተ አልለይም›› አለቻው፡፡ ከመነኮሱም በኋላ ስማቸው ‹‹አቡነ መዝገበ ሥላሴ›› ተባሉ፡፡
አቡነ መዝገበ ሥላሴ ስብከተ ወንጌልን በመላ ሀገራችን በማስፋፋት ብዙ የደከሙ ታላቅ አባት ናቸው፡፡ በዚህም ምክንያት ‹‹የሐዋርያት አምሳል›› ተብለዋል፡፡ የገዳሙ አበምኔት ሲያርፉ መነኮሳቱ በፈቃደ እግዚአብሔር አቡነ መዝገበ ሥላሴን ይዘው በግድ አበምኔትነት ሾሟቸው፡፡ እሳቸውም ከተሾሙ በኋላ በመላ ሀገራችን ተዘዋውረው ወንጌልን ሰብከዋል፡፡ ብዙ ድውያንን ፈውሰዋል፣ ሙታንን አንሥተዋል፡፡ በዓታቸውንም በማጽናት በጸሎት ተወስነው የዐይኖቻቸው ቅንድቦች እስኪላጡ ድረስ ጉንጮቻቸውም እስኪቀሉ ድረስ በጸሎት ይተጉ ነበር፡፡ 40 ቀንና 40 ሌሊትም ይጾማሉ፡፡ ስግደታቸውም በቀንና በሌሊት ያለ እረፍት እንደመንኮራኩር ፈጣን ሆነ፡፡ ወዛቸውና ዕንባቸው አንድ ላይ ተቀላቅሎ እንደጅረት እስኪፈስ ድረስ በጭንቅ ተጋድሎ እንደኖሩ ገድላቸው ይናገራል፡፡ እመቤታችንም ብዙ ጊዜ እየተገለጠችላቸው ከህመማቸው እየፈወሰች ታበረታቸው ነበር፡፡ ከዕለታትም በአንደኛው ቀን አቡነ መዝገበ ሥላሴ ራእይ ተመለከቱ፡፡ እነሆም ውበታቸው የሚያስገርም፣ መልካቸውም የሚያስደንቅ፣ የምስጋና ነፀብራቅ የከበባቸው፣ የራሳቸው ፀጉር ነጭ የሆነ ሦስት ወፎችን ተመለከቱ፡፡ አባታችንም አንድ ጊዜ ሦስት ሌላ ጊዜ ደግሞ አንድ ሲሆኑ ተመልክተው ፈጽሞ አደነቁ፡፡ እንዲህ እያደነቁ ሳለ እግዚአብሔር በቃሉ ጠርቶ ካነጋገራቸው በኋላ ብዙ ምሥጢራትን ነገራቸው፡፡ ለመረጣቸው ቅዱሳን እንዲህ መገለጥ ለእግዚአብሔር ልማዱ ነውና ለአባታችን ለአዳም፣ ለሄኖክ፣ ለኖኅ፣ ለአብርሃም በልዩ ልዩ ህብር ተገልጧል፡፡ ኦ.ዘፍ 3፡10፣ 5፡24፣ 6፡13፣ 18፡1 ፡፡ ለሕዝቅኤልም በኮበር ወንዝ፣ ለዳንኤል በሱሳ ግንብ፣ ለኢሳይያስ ሱራፌል እያመሰገኑት ተገልጦላቸዋል፡፡ ሕዝ 1፡1፣ ዳን 8፡1-3፣ ኢሳ 6፡1-3፡፡
አቡነ መዝገበ ሥላሴ በዘመን ደረጃ በኋለኛው ዘመን የተነሡ አባት ይሁኑ እንጂ በሰጡት ሐዋርያዊ አገልግሎትና ገንዘብ ባደረጉት የተጋድሎ ጽናት የከበሩ ቅዱሳን ሐዋርያትን መስለዋቸዋል፡፡ የታዘዘ መልአክ ወደ መንግሥተ ሰማያት ነጥቆ ወስዶ ማደሪያቸውን አሳይቷቸው መልሶ ወደ ምድር ካመጣቸው በኋላ የዕረፍታቸው ጊዜ እንደደረሰ ነገራቸው፡፡ ‹‹በሰኔ ወር ታርፋለህ›› ቢላቸው ‹‹በሰኔማ ልጆቼ ተዝካሬን ማድረግ አይችሉም›› አሉት፡፡ መልአኩም መልሶ ‹‹ዕረፍትህ በሐምሌ ይሁን›› ቢላቸው ጻድቁ አሁንም ‹‹አይሆንም›› ብለው ተከራከሩ፡፡ በነሐሴም እንደዚያው ሆነ፡፡ መልአኩም መስከረምን አሳልፎ በጥቅምት እንደሚያርፉ ነግሯቸው ዐረገ፡፡ ከዚህም በኋላ ለስም አጠራሩ ምስጋና ይግባውና ጌታችን ቅድስት እናቱን፣ መላእክትን፣ ቅዱሳን ጻድቃን ሰማዕታትን ሁሉ አስከትሎ መጥቶ ‹‹አንተ የዓሥራ አንደኛው ሰዓት ቅጥረኛ ወዳጄ ሆይ! (ከቅዱሳን ሁሉ በኋላ የተነሣህ-ማቴ 20፡1-5) የምስራች እነግርህ ዘንድ የድካምህም ዋጋ እሰጥህ ዘንድ መጥቻለሁ፡፡ እነሆ ከጠዋት ጀምሮ ከደከሙት ጋር አንድ አድርጌሃለሁ፡፡ ከአንተም ጋር ቃልኪዳን ገብቻለሁ፣ ስምህን በእምነት የጠራ፣ መታሰቢያህን ያደረገ፣ በጸሎትህም የታመነ እስከ ሰማንያ ሺህ ስድስት መቶ (80,600) ነፍሳት ዓሥራት ይሁኑህ…›› በማለት ቃልኪዳን ከገባላቸው በኋላ ወደ ሰማያት ዐረገ፡፡ በዚያን ጊዜም አቡነ መዝገበ ሥላሴ ፊታቸው እንደፀሐይ አበራና ጥቅምት 9 ቀን ከሌሊቱ በ6 ሰዓት እንደመልካም እንቅልፍ ዐረፉ፡፡ መላ ዘመናቸው 115 ሲሆን የደብረ ገሪዛን ጉንዳጉንዶ ቅድስት ማርያም ገዳም አበምኔት ሆነው ከመሾማቸው በፊት 62 ዓመት፣ ከተሾሙበት ጊዜ እስከ ዕለተ ዕረፍታቸው ድረስ 53 ዓመት ነው፡፡ መካነ መቃብራቸው እዚያው የደብረ ገሪዛን ጉንዳጉንዶ ቅድስት ማርያም ገዳም ይገኛል፡፡
በጉንዳጉንዶና አዲግራት በሚገኘው ገዳማቸው ውስጥ በስማቸው የፈለቁ ብዙ ፈዋሽ ጠበሎች አሉ፡፡ አዲግራት የሚገኘው ገዳማቸው ውስጥ ያለው ጠበል የትኛውንም በሽታ በአስቸኳይ ፈውስ በመስጠት ይታወቃል፡፡ ተጠማቂው ሰው የማይድንም ከሆነ ቶሎ ይሞታል እንጂ ከ7 ቀን በላይ አይቆይም፡፡ ጻድቁ ብዙ የተጋደሉበት ይህ ገዳም በግራኝ አህመድ ዘመን 44 ጽላቶች ተሰውረውበታል፡፡ ዮዲት ጉዲትም ልታገኘው ያልቻለችው ታላቅ ገዳም ነው፡፡ በአንድ ወቅት ከሃዲያን አሕዛብ ጦረኞች ወደ ገዳሙ ሲወጡ በተአምራት ወደ ፅድ ዛፍነት ተለውጠዋል፡፡ ፅዶቹ አሁንም ድረስ በገዳሙ ክልል ውስጥ የሚገኙ ሲሆን ፅዶቹን በእሳት አቃጥለው ከሰል ቢያደርጓቸው ደም ሆነው ይፈሳሉ እንጂ ፈጽሞ ከሰል መሆን አይችሉም።
ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።

 

No comments:

Post a Comment

Post Bottom Ad

Pages