ስንክሳር_ዘወርኀ_ጥር 24 - አትሮንስ ሚዲያ - Atrons Media

አትሮንስ ሚዲያ - Atrons Media

ስብኩ ወንጌለ ለኩሉ ፍጥረት ማቴ 16፤15


በቅርብ የተጻፉ

Post Top Ad

Friday, March 3, 2023

ስንክሳር_ዘወርኀ_ጥር 24

 አንድ አምላክ በሚሆን በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም

ጥር ሃያ አራት በዚህች ዕለት #አቡነ_ተክለ_ሃይማኖት በጸሎት ብዛት አንዲቱ የእግራቸው አገዳ የተሰበረበት (ስብረተ አፅማቸው) መታሰቢያ ነው፣ የከበረች ተጋዳይ #ግብጻዊት_ቅድስት_ማርያ አረፈች፣ የሸዋው #እጨጌ_መርሐ_ክርስቶስ ዕረፍታቸው ነው፡።


ጥር ሃያ አራት በዚህች ዕለት ''ሐዲስ ሐዋርያ'' ብሎ የሾማቸው የኢትዮጵያ ብርሃኗ የሆኑ የደብረ ሊባኖሱ አቡነ ተክለ ሃይማኖት በጸሎት ብዛት አንዲቱ የእግራቸው አገዳ የተሰበረበትን (ስብረተ አፅማቸው) መታሰቢያ ታከብራለች።
እግዚአብሔር አምላካችን ለኢትዮጵያ ሐዲስ ሐዋርያ አድርጎ የመረጣቸው ጻድቁ አባታችን ተክለ ሃይማኖት በሊቀ መላእክት በቅዱስ ሚካኤል አብሳሪነት ከአባታቸው ከካህኑ ጸጋ ዘአብና ከእናታቸው ከቅድስት እግዚእ ኀረያ መጋቢት 24 ቀን ተፀንሰው ታኅሣሥ 24 ቀን 1197 ዓ.ም ተወለዱ፡፡ ጻድቁ በተወለዱ በሦስተኛው ቀን ከእናታቸው ዕቅፍ ወርደው ‹‹አሐዱ አብ ቅዱስ አሐዱ ወልድ ቅዱስ አሐዱ ውእቱ መንፈስ ቅዱስ›› ማለትም ‹‹አንዱ አብ ቅዱስ ነው አንዱ ወልድ ቅዱስ ነው አንዱ መንፈስ ቅዱስ ቅዱስ ነው›› በማለት የፈጠራቸውን አምላክ አመስግነውታል፡፡ ወላጆቻቸውም ስማቸውን ፍሥሐ ጽዮን አሏቸው፡፡ ይኸውም የጽዮን ተድላዋ ደስታዋ ማለት ነው፡፡ የወላጆቻቸው የቀድሞ ስማቸው ዘርዐ ዮሐንስና ሣራ ይባል ነበር፡፡
ቅዱሳን አባቶቻችን እነ አቡነ ተክለ ሃይማኖትና እነ አቡነ ዜና ማርቆስ ሌሎቹም እነ አቡነ ሳሙኤል ዘወገግ፣ አቡነ ሕፃን ሞዐ፣ አቡነ አኖሪዮስ(ትልቁ)፣ አቡነ ገላውዲዮስ፣ አቡነ ማትያስ ዘፈጠጋርና አቡነ ቀውስጦስ ዘመሐግል የትውልዳቸው መሠረት ኢያሱ ለሌዋውያን ክፍል ትሆን ዘንድ ከለያት ከኢየሩሳሌም ነው፡፡ ስማቸውን የጠቀስኳቸው እነዚህ ቅዱሳን አባቶቻችን የወንድማማቾች ልጆች ሲሆኑ ከአዳም ጀምሮ 61ኛ ትውልድ ናቸው፡፡ ይኸውም እንዴት ነው ቢሉ ትውልዱ ከአዳም ጀምሮ በካህኑ አሮን በኩል የሆነውና የሌዋዊያን ሊቀ ካህን የነበረው የሳዶቅ ልጅ አዛርያስ በንጉሥ ሰሎሞን ዘመን ከታቦተ ጽዮንና ከብዙ ሌዋዊያን ካህናት ጋር ሊቀ ካህን ሆኖ ከኢየሩሳሌም ወደ ኢትዮጵያ መጥቶ አክሱም ተቀምጦ ኖረ፡፡ የኦሪትንም ሕግ እየዞረ ለኢትዮጵያ ሰዎች አስተማረ፡፡ ትውልዱም በአብርሃ ወአጽብሓና በአባ ሰላማ ዘመን እስከነበረው እንበረም የሚባለው ጻድቅ ድረስ ደረሰ፡፡ የእንበረምም ትውልድ ደገኛው ሕይወት ብነ በጽዮን ድረስ ደረሰ፡፡ ሕይወት ብነ በጽዮንም የደማስቆ ምድር ከሚሏት ከወለቃ ሀገር የመኮንን ልጅ የሆነችውን ወለተ ሳውልን አግብቶ አበይድላን ወለደ፡፡ አበ ይድላም በንጉሡ ድልዓዥን ዘመነ መንግሥት ለ150 ካህናት አለቃ ሆኖ በወለቃ ሀገር የክርስቶስን የወንጌል ሕግ እያስተማረ ብዙዎችን አጠመቀ፡፡ እስከ ሸዋ ምድር ድረስ እያስተማረ መጥቶ በሸዋ ምድር ተቀመጠ፡፡ ብዙ አብያተ ክርስቲያናትንም አሳነጸ፡፡ እጅግ አስደናቂ ተአምራትንም ያደርግ ነበር፡፡ ‹‹በሸዋ ጽላልሽ ተቀምጦ ሲያስተምርም በአንዲት ቀን እስከ ሁለት መቶ ሺህ ሕዝብ ያጠምቅ ነበር›› በማለት ገድለ አቡነ ተክለ ሃይማኖት ይመሰክርለታል፡፡
አበይድላ በመጨረሻ በፈቃደ እግዚአብሔር ከሸዋ ጽላልሽ ምድረ ዞረሬ ሚስት አግቶ ሀበነ እግዚእን ወለደ፤ ሀበነ እግዚእም በኩረ ጽዮንን ወለደ፤ በኩረ ጽዮንም ሕዝበ ቀድስን ወለደ፤ እርሱም ነገደ እግዚእ የተባለ ነው፡፡ ሕዝበ ቀድስም ብርሃነ መስቀልን ወለደ፤ እርሱም ዐቃቢነ እግዚእ የተባለ ነው፡፡ ብርሃነ መስቀልም ሕይወት ብነን ወለደ፤ እርሱም ሴትን ወለደ፡፡ ሴትም ወረደ ምሕረትን ወለደ፡፡ ወረደ ምሕረትም ዘካርያስን ወለደ፡፡ ዘካርያስም የእነ አቡነ ተክለ ሃይማኖት አባት የሆኑ 6 ወንድማማች ልጆችን ወለደ፡፡ እነርሱም እንድርያስ፣ አርከሌድስ፣ ዘርዐ አብርሃም፣ ዘርዐ ዮሐንስ ወይም ጸጋ ዘአብ፣ ቀሲስ ዮሐንስና ቀሲስ ዮናስ ናቸው፡፡ እንድርያስም ሳሙኤል ዘወገግን ወለደ፤ አርከሌድስም ሕፃን ሞዐን ወለደ፤ ዘርዐ አብርሃምም ታላቁን አኖርዮስን ወለደ፤ ዘርዐ ዮሐንስ ወይም ጸጋ ዘአብም ተክለ ሃይማኖትን ወለደ፤ ቀሲስ ዮሐንስም ዜና ማርቆስን ወለደ፣ ቀሲስ ዮናስ ደግሞ የፈጠጋሩን ማትያስንና ገላውዲዮስን ወለዳቸው፡፡ ገላውዲዮስም የመሐግሉ ቀውስጦስን ወለደ፡፡ እነዚህ ደጋግ ቅዱሳን በእናታቸውም በኩል እንዲሁ በዝምድና የተሳሰሩ ናቸው:: ማቴዎስ የተባለው ደገኛ ክርስቲያን የሸዋ ገዥ የነበረ ሲሆን አንድ ወንድ ልጅ መድኃኒነ እግዚእንና ሦስት ሴቶች ልጆችን ወለደ፡፡ ሶስቱ ሴቶች ልጆችም እምነ ጽዮን፣ ትቤ ጽዮንና ክርስቶስ ዘመዳ ይባላሉ፡፡ ሦስቱ እኅትማማቾችም ደጋጎቹን አባቶቻችንን ወለዱልን፡፡ እምነ ጽዮን የእነ ዜና ማርቆስን እናት ማርያም ዘመዳንና ወለደች፡፡ ትቤ ጽዮንም ሕፃን ሞዐን ወለደች፡፡ ክርስቶስ ዘመዳ ደግሞ ታላቁን አኖሬዎስን ወለደች፡፡ የፈጠጋሩ ገዥ መድኃኒነ እግዚእ ደግሞ የተክለ ሃይማኖትን እናት እግዚእ ኀረያን ወይም በሌላ ስሟ ሣራን ወለደ፡፡
አቡነ ተክለ ሃይማኖት ከልጅነታቸው ጀምሮ በወላጅ አባታቸው በካህኑ ቅዱስ ጸጋ ዘአብ ግብረ ዲቁናን ሥርዓተ ቤተ ክርስቲያንን ሲያጠኑ ቆይተው በ15 እና በ22 ዓመታቸው ከእስክንድርያው ሊቀ ጳጳስ ከአቡነ ቄርሎስ (ጌርሎስ) ዲቁናንና ቅስናን ተቀብለዋል፡፡ ብፁዕ ወቅዱስ አባታችን ቅድስት ቤተክርስቲያንን በወጣትነት ዕድሜያቸው ያገለግሉ እንደነበር በዚህ ይታወቀል፡፡
ከዕለታት በአንዱ ቀን አባታችን ከጓደኞቻቸው ጋር ለአደን ወደ ዱር ሄደው ሳለ ሊቀ መላእክት ቅዱስ ሚካኤል ተገልጦ ታያቸው፡፡ ቅዱስ አባታችንም ‹‹እንደዚህ ባለ ገናንነት የማይህ ጌታዬ ማነህ?›› ባሉት ጊዜ ቅዱስ ሚካኤል ‹‹ዘወትር የምጠብቅህ ካንተ የማልለይ እናትህንና አባትህንም ስላንተ ከውኃ ስጥመትና ከምርኮ ያዳንኳቸው እኔ ሚካኤል ነኝ፡፡ ከእንግዲህ አውሬ አዳኝ አትሁን፤ ሰውን ወደ እግዚአብሔር ለመመለስ ሰውን በትምህርት የምታድን ሁን እንጂ፡፡ እነሆ እግዚአብሔር ጽኑዕ ሥልጣን ሰጥቶሃልና፤ ሙት ታስነሣለህ፤ ድውያንን ትፈውሳለህ፤ አጋንንትም አንተን በመፍራት ይሸሻሉ፡፡ ስምህ ፍሥሐ ጽዮን አይሁን፤ ተክለ ሃይማኖት ይሁን እንጂ፡፡ ትርጓሜውም ተክለ አብ፥ ተክለ ወልድ፥ ተክለ መንፈስ ቅዱስ ማለት ነው›› አላቸው፡፡
ቅዱስ ሚካኤል ይህን ሲነግራቸው ጌታችን በሥጋ ከደቀ መዛሙርቱ ጋር እንደነበር ሆኖ መልከ መልካም ጎልማሳ መስሎ ታያቸው፡፡ ጌታችንም ‹‹ወዳጄ እንዴት ሰነበትክ? ቸር አለህን?›› አላቸው፡፡ አቡነ ተክለ ሃይማኖትም ‹‹ጌታዬ ሆይ አንተ ማነህ?›› ብለው ሲጠይቁት ጌታችንም ‹‹እኔ የዓለም መድኃኒት ኢየሱስ ነኝ፤ በናትህ ማኅፀን ፈጥሬህ ያከበርኩህ እኔ ነኝ፡፡ በተወለድክ በሦስተኛው ቀን አሐዱ አብ ቅዱስ አሐዱ ወልድ ቅዱስ አሐዱ ውእቱ መንፈስ ቅዱስ ብለህ ታመሰግነኝ ዘንድ የምስጋና ሀብት ያሳደርኩብህ እኔ ነኝ፡፡ በርሃብ ዘመን በቤት የሚያሻው ምግብ ሁሉ ቅቤው፣ የስንዴው ዱቄት በእናት በአባትህ ቤት ይመላ ዘንድ በእጅህ ሀብተ በረከት ያሳደርኩብህ እኔ ነኝ፡፡ ያንን ሰው አንተን በተጣላ ጊዜ በነፋስ አውታር የሰቀለኩት በመዓት ጨንገር የገረፍኩት እኔ ነኝ፡፡ ውኃ ጠምቶህ በለመንከኝ ጊዜ ከደረቅ መሬት የጣፈጠ ውኃ ያመነጨሁልህ እኔ ነኝ፡፡ ከልጅነትህ ጀምሮ እስከ ዛሬ ድረስ ብዙ ተአምራት እያደረግሁ በአንተ እጅ የታመሙትን ያዳንኳቸው እኔ ነኝ፡፡ ወደፊትም አደርግልሃለሁ›› አላቸው፡፡ ይህንን ብሎ በእጆቹ ባረካቸውና ‹‹ንሣእ መንፈስ ቅዱስ›› ብሎ የሹመትን ሀብት አሳደረባቸው፡፡ ዳግመኛም ‹‹በምድር ያሰርከው በሰማይ የታሰረ ይሁን፤ በምድርም የፈታኸው በሰማይ የተፈታ ይሁን፤ አንተን የሰማ እኔን መስማቱ ነው፤ የላከኝ አባቴንም መስማቱ ነው፡፡ አንተን እንቢ ያለ እኔን እንቢ ማለቱ ነው፡፡ የላከኝ አባቴንም እንቢ ማለቱ ነው፡፡ ይህን ሥልጣን ቀድሞ ለሐዋርያት ሰጥቻቸው ነበር፡፡ ከሐዋርያትም ሹመትን የተቀበለ ጳጳሱ ትሾምና ትሽር፣ ትተክልና ትነቅል ዘንድ ሥልጣንን ሰጠህ፡፡ ይህንንም ያደረኩልህ የጳጳሱን ቃል በመናቅ አይደለም፡፡ የፍቅሬን ጽናት ባንተ እገልጽ ዘንድ ነው እንጂ፡፡ ሐዋርያት ወዳልደረሱበት ሕዝብ በመምህርነት እልክህ ዘንድ በሚካኤል ቃል አዲስ ስም አወጣሁልህ፡፡ አንተም በማናቸውም ሥራ ከእነርሱ አታንስም፣ ሐዲስ ሐዋርያ አድርጌሃለሁና፡፡ ሰውን ሁሉ በእኔ ስም እያስተማርክ ታሳምን ዘንድ፣ ሚካኤልም ባሰብከው ሥራ ሁሉ ረዳት ይሁንህ፣ ሁል ጊዜ ካንተ አይለይም፤ በምትሄድበትም ጎዳና ሁሉ እርሱ መሪ ይሁንህ፤ እኔም ባለ ዘመንህ ሁሉ አልለይህም›› ካላቸው በኋላ ሰላምታ ሰጥቷቸው ዐረገ፡፡
ብፁዕ አባታችንም እጅ ነሥተው ‹‹ለእኔ ለኀጥኡ የማይገባኝ ሲሆን ይህን ሁሉ ጸጋ የጠኸኝ ስምህ በሰማይ በምድር የተመሰገነ ይሁን›› አሉ፡፡ ከዚያች ቀን ጀምሮ ሀብተ ኃይልን የተመሉ ሆኑ፡፡ ወደቤታቸው ተመልሰው ያላቸውን ሀብት ንብረት ሁሉ ለቤተ ክርስቲያን፣ ለድኆችና ለጦም አዳሪዎች ሰጥተው ጨረሱ፡፡ ከዚያም ‹‹አቤቱ ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ! የመንግሥተ ሰማያትን በር ትከፍትልኝ ዘንድ እነሆ ቤቴን እንደተከፈተ ተውኩልህ›› ብለው ቤታቸውን እንደተከፈተ ትተው ወንጌልን ለማስተማር ወጡ፡፡ ጻድቁ አባታችን በሀገራችን ኢትዮጵያ እየተዘዋወሩ ሕዝቡን ከኃጢአት ወደ ገቢረ ጽድቅ፣ ከክህደት ወደ ኃይማኖት ስለመለሱት በዚህም የተነሣ ለኢትዮጵያውያን ብርሃን ተብለዋል፡፡
አባ ተክለሃይማኖት ከበዓታቸው ሳይወጡ በጸሎት ተጠምደው ሌሊትና ቀን ይቆሙ ነበር። ከተጋድሎ የተነሳ ቁመትንም ካበዙ ወዲህ አንዲቱ የእግራቸው አገዳ ተሰበረች ደቀ መዛሙርቱ አንሥተው አክብረው በሰበን ጠቅልለው ከመንበሩ እግር በታች ቀበሯት። ከዚህም ባንዲት እግራቸው ሰባት ዓመትን ቆሙ። በዚህ ቀንም ቤተክርስቲያን በጸሎት ብዛት አንዲቱ የእግራቸው አገዳ የተሰበረበትን (ለስብረተ አፅማቸው) መታሰቢያ ታከብራለች።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
ዳግመኛም በዚህች ዕለት ከእስክንድርያ አገር ከታላላቆቿ ወገን የሆነች የከበረች ተጋዳይ ማርያ አረፈች።
የዚችም ቅድስት ወላጆቿ ክርስቲያኖች ናቸው በአደገችም ጊዜ ሊአጋቧት አሰቡ እርሷ ግን ይህን ጋብቻ አልወደደችም እናትና አባቷም በሞቱ ጊዜ የተዉላትን ገንዘብ ሁሉንም ለድኆች ሰጥታ ከእስክንድርያ አገር ውጭ ከአሉ ገዳማት ወደ አንዱ ገዳም ገባች የምንኵስና ልብስንም ለብሳ ታላቅ ተጋድሎን ተጋደለች ድል እስካደረገችውም ድረስ እንቅልፍን ዐሥራ ሁለት ዓመት ስትታገለው ኖረች ከቶ አትተኛም ነበር እንደዚያ ገዳም ሕግ በእሊህ በዐሥራ ሁለቱ ዓመታት ሁልጊዜ እስከማታ ትጾም ነበር።
ከዚህም በኋላ የከበረ አስኬማን ለበሰች ያን ጊዜ ከጥጥ ባዘቶ የተሠራውን ልብስ ከላይዋ አውልቃ ማቅ ለበሰች ትችል እንደሆነ ወይም አትችል እንደሆነ ራሷን ትፈትን ዘንድ ለመዝጋት ትፈቅድላት ዘንድ እመ ምኔቷን ለመነቻት እርሷም ፈቀደችላት በዚያንም ጊዜ በዓቷን ዘጋች ምግቧን የምትቀበልበት ትንሽ መስኮት ቀደደች ሥጋውንና ደሙን በዚያው ትቀበላለች በዚያችም በዓት ውስጥ ሃያ ሁለት ዓመት ዘግታ ኖረች።
በዚህ ሁሉ ዘመን ቁማ ትጸልያለች በመኝታ ጊዜም ጥቂት ትተኛለች የቀረውንም ሌሊት እስኪነጋ ቁማ ስትጸልይ ታድራለች። በየሁለት ቀን የምትጾም ሆነች የምትመገበውም በውኃ የራሰ ለምለም እንጀራ ነበር በከበረችም በአርባ ጾም እንጀራ አትበላም በየሦስት ቀን እየጾመች በውኃ የራሰ ሽምብራ ትመገባለች እንጂ።
ጥር ዐሥራ አንድ ቀን የከበረ የጥምቀት በዓልም በሆነ ጊዜ ከተባረከው ውኃ ያመጡላት ዘንድ ለምና አመጡላት ፊቷንና እጆቿን ታጥባ ሥጋውንና ደሙን ተቀበለች ከተባረከውም ውኃ ጠጣች ከዚህም በኋላ ታመመች እስከ ጥር ሃያ አንድ ቀንም በመኝታዋ ላይ ተኛች ዳግመኛ በዚች ቀን በሃያ አንድ ሥጋውንና ደሙን ተቀበለች።
ከዚህም በኋላ እመ ምኔቷን አስጠራቻት እግሮቿንም እንድታቀርብላት ብዙ ልመናን ለመነቻትና ስታቀርብላት ሳመቻቸው ፊቷንም አሸችባቸው ወደ ክብር ባለቤት ጌታዬ ክርስቶስ ላቀረቡኝ እግሮችሽ እገዛለሁ አለች ዳግመኛም ደናግሉን ሁሉ አስጠርታ ተሳለመቻቸውና ከሦስት ቀን በኋላ እንዲጐበኟት ለመነቻቸው ይኸውም ጥር ሃያ አራት ቀን ነው በመጡም ጊዜ ሙታ አገኟት ገንዘውም ከደናግል አስክሬን ጋር አኖሩዋት።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
ዳግመኛም በዚህች ቀን የሸዋው እጨጌ መርሐ ክርስቶስ ዕረፍታቸው ነው፡፡ ጻድቁ የገዳማት ሁሉ አባት እየተባሉም ይጠራሉ፡፡ ትውልዳቸው ሸዋ መራቤቴ ሚዳ ሲሆን ለገዳማት ብዙ የደከሙ አባት ናቸው፡፡ በተለይም በእጅጉ የሚታወቁበት አንድ ገድል አላቸው፡፡ ይኸውም እንደ ነዳይ ሆነው ለምነው ያገኙትን ለጦም አዳሪዎች በመመጽወት ይታወቃሉ፡፡ ከባለ ሀብቶች ለምነው ያገኙትን ለድሆች ይመጸውቱትና በቀረው ቤተ ክርስቲያን ይሠሩበታል፡፡ አስደናቂ ገድላቸውና ዐፅማቸው በደብረ ሊባኖስ ይገኛል፡፡ በትግራይም ትልቅ ገዳም አላቸው፡፡ ዕረፍታቸው ጥር 24 ቀን ሲሆን ሕዝቡ ግን የሚያከብረው በዓለ ልደታቸውን ነው፡፡ ረድኤት በረከታቸው ይደርብን በጸሎታቸው ይማረን!
ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በከበሩ ቅዱሳን ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ይኑር ለዘላለሙ አሜን።

No comments:

Post a Comment

Post Bottom Ad

Pages