ስንክሳር_ዘወርኀ_ታህሣሥ 6 - አትሮንስ ሚዲያ - Atrons Media

አትሮንስ ሚዲያ - Atrons Media

ስብኩ ወንጌለ ለኩሉ ፍጥረት ማቴ 16፤15


በቅርብ የተጻፉ

Post Top Ad

Friday, March 3, 2023

ስንክሳር_ዘወርኀ_ታህሣሥ 6

 አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም

ታኅሣሥ ስድስት በዚህች ዕለት የታላቋ ሰማዕት_የቅድስት_አርሴማ ቤተ ክርስቲያኗ የከበረችበትና የሥጋዋ ፍልሰት የተከናወነበት፣ ቅዱስ አባት የእስክንድርያ አገር ሊቀ ጳጳሳት የአባ_አብርሃም_ሶርያዊ የዕረፍቱ እና የቅዱስ_ስምዖን_ጫማ_ሰፊውም መታሰቢያው ነው።


ታኅሣሥ ስድስት በዚህች ዕለት የታላቋ ሰማዕት የቅድስት አርሴማ ቤተ ክርስቲያኗ የከበረችበትና የሥጋዋ ፍልሰት የተከናወነበት ነው፡፡ ከእርሷም ጋር አብረው የተሰየፉ 27 ደናግልም የሥጋቸው ፍልሰት ሆነ፡፡
የቅዱስት አርሴማ አባቷ ቴዎድሮስ ከሌዋውያንና ከኃያላን ነገሥታት ወገን ሲሆን እናቷ አትኖስያ ደግሞ ከጳጳሳት አለቆች ወገን ናት፡፡ ወላጆቿ በሃይማኖት በምግባር ያጌጡ በበጎ ትሩፋት የተመሰገኑ ደጋግ ቅዱሳን ናቸው፡፡ በጾም፣ በጾሎት፣ በምጽዋትና ዓሥራት በኩራትን በማውጣት በመንፈሳዊ ሥራ ሁሉ እየተጉ ቢኖሩም ነገር ግን እስክ እርጅናቸው ዘመን ድረስ ልጅ ስላልነበራቸው ያዝኑ ነበር፡፡ እናቷ ቅድስት አትኖስያ እንደ ነቢዩ ሳሙኤል እናት ሐና ጠዋት ማታ ወደ ቤተ ክርስቲያን በመሄድ በእግዚአብሔር ፊት ታለቅስ ነበር፡፡ እግዚአብሔር የልቧን ፈቃድ ይፈጽምላት ዘንድ ወደደና የቂሣርያውን ሊቀ ጳጳሳት ልድዮስን ስለ እርሷ ይጸልይላት ዘንድ አዘዘው፡፡
ሊቀ ጳጳሳቱም ስለ ቅድስት አትኖስያ ጸለየላት፡፡ እግዚአብሔር አምላክም የሊቀ ጳጳሳቱንና የቅድስት አትኖስያን ጸሎት ሰምቶ መልኳ እጅግ ያማረችን ሴት ልጅ ቅድስት አርሴማን ሰጣት፡፡ እናቷም እየተንከባከበች አሳድጋት ዕድሜዋ ከፍ ሲል አምላክን በወለደች በእመቤታችን ስም ወደተሠራች ቤተ ክርስቲያን ታገለግል ዘንድ ሰጠቻት፡፡ ቅድስት አርሴማ ወጣት በሆነች ጊዜ ወላጆቿ ባል ያጋቧት ዘንድ ወደዱ ነገር እርሷ ይህንን ፈጽሞ አልወደደችምና ወላጆቿን "እኔ የሰማያዊው የክርስቶስ ሙሽራ ነኝ እንጂ ምድራዊ ሙሽራ አይደለሁም" አለቻቸው፡፡
ቅድስት አርሴማ ከእርሷ በፊትም ሆነ ከእርሷ በኋላ በመልክና በውበት የሚመስላት የለም፡፡ ይህን ዓለም እንደትቢያ በመቁጠርና ፍጹም በመናቅ ጌታችንን ከተከተሉት ቅዱሳት ደናግል አንስት ውስጥ በመልክና በውበት ቅድስት አርሴማን የሚመስል የለም፡፡ አምላክን ከወለደች ከእመቤታችን በቀር የሚበልጣት ማንም የለም፡፡ እርሷም በምግባር በሃይማኖት ያጌጠች በመንፈሳዊ ተጋድሎ የበረታች በትሩፋት የበለጸገች ናት፡፡ ብሉይን ከሐዲስ አጠናቃ ተማረች፡፡ የአገሮችንም (የሮምያን፣ የጽርዕን፣ የሶርያን፣ የኪልቅያን) ቋንቋዎች ታውቅ ስለነበር ቅዱሳት መጻሕፍትንም ወደ ተለያዩ አገራት ቋንቋዎች ትተረጉማለች፡፡
ቅድስት አርሴማ 15 ዓመት በሆናት ጊዜ ከሃዲውን ዲዮቅልጥያኖስን ሰይጣን አስነሥቶት ነገሠ፡፡ ይኸውም ከሃዲ ንጉሥ ሚስት ያባ ዘንድ በመልኳ ውብ የሆነች ሴት ልጅን ይመርጡለት ዘንድ በሀገሩ ሁሉ እንዲሄዱ ጭፍሮቹን አዘዘ፡፡ ያገኟትንም ውብ የሆነችን ሴት መልኳን ሥለው ያመጡለት ዘንድ ሠዓሊዎችንም አብሮ ላከ፡፡ የተላኩትም ሰዎች ወደ ሮሜ አገር በደረሱ ጊዜ ቅድስት አርሴማ ያለችበትን የደናግል ገዳም አገኙ፡፡ ወደ ገዳሙም ገብተው ቅድስት አርሴማን አይተዋት በመልኳ ማማር እጅግ ተደስተው "ለንጉሡ ሚስት የምትሆነው ይህች ናት" ብለው መልኳን በሥዕል ቀርጸው ለንጉሡ ላኩለት፡፡ ንጉሡም ሥዕሏን በተመለከተ ጊዜ ፈጽሞ ተደሰተ፡፡ ስለ ሠርጉ ወደ እርሱ ይመጡ ዘንድ ሕዝቡን ይጠሩአቸው ዘንድ ወደ ነገሥታቱና ወደ መኳንንቱ ሁሉ ላከ፡፡
በገዳም ያሉ ደናግልም ይህን በሰሙ ጊዜ እጅግ አዝነው አለቀሱ፡፡ ድንግልናቸውን እንደጠበቁ ያገለግሉት ዘንድ እግዚአብሔርን እየለመኑት ከገዳሙ ወጥተው ወደ ንጉሥ ድርጣድስ የግዛት አገር ወደ አርማንያ ደረሱ፡፡ በዚያም በምድረ በዳ ዋሻ ውስጥ ተቀመጡ፡፡ ቁጥራቸውም 75 ወንዶችና 39 ደናግል ሴቶች ነበሩ፡፡ በዋሻም ውስጥ በረሃብና በጥም እየተቸገሩ ተቀመጡ፡፡ ንጉሥ ዲዮቅልጥያኖስ ቅድስት አርሴማን ፈልጎ ባጣት ጊዜ እጅግ ቢያዝንም ነገር ግን ቆይቶ በአርማንያ እንዳለች ሰማ፡፡ እርሷንም ይዞ ይልክለት ዘንድ ወደ አርማንያው ንጉሥ ድርጣድስ መልእክት ላከ፡፡ ድርጣድስም ለጣዖት የሚሰግድ ፀሐይና ጨረቃን የሚያመልክ ነው፡፡ በሰው እጅ የተጠረቡ ዕንጨቶችንና ድንጋዮችንም በቤቱ አስቀምጦ "አማልክት" እያለ በመጥራት እንደ አምላክ ያመልካቸው ነበር፡፡ በውስጡም ሰይጣን አድሮበታልና የእርሱን ጣዖታት ሕዝቡም እንዲያመለኩ ያስገድዳቸው ነበር፡፡ ክርስቲያኖችንም እያሰረ በመግረፍ ያሠቃይ ነበርና ቅድስት አርሴማ በዋሻ ውስጥ ሆና አንዱ መኮንን ክርስቲያኖችን በመግረፍ ሲያሠቃይ ታየዋለች፡፡ ስለ ሰማዕታቱም ወደ እግዚአብሔር ስትጸልይ የብርሃን አክሊል የያዙ ቅዱሳን መላእክት ሰማዕታቱ ሲሰጧቸው አየች፡፡ ይህንንም ታላቅ ምሥጢር ባየች ጊዜ "አቤቱ አምላኬ ሆይ ስለስምህ እኔም ሰማዕት እሆን ዘንድ እርዳኝ" እያለች ለመነች፡፡
ከዚህም በኋላ ወደ ሰማዕታቱ ዘንድ ስትሄድ መኮንኑ አያት ከመልኳ ማማር የተነሣ ደነገጠና "እመቤቴ ሆይ እዛው ባለሽበት ሆነሽ ተዋቸው ብትይኝ ፈትቼ እለቃቸው ነበር አንቺ ከዚህ መምጣት አያስፈልግሽም" አላት፡፡ ቅድስት አርሴማም "እኔም የእነዚህን ሰማዕታት መከራ እሸከም ዘንድ እወዳለሁ፣ የእነርሱንም የክብር አክሊል አገኝ ዘንድ እሻለሁ" አለችው፡፡ እርሱም "እመቤቴ ሆይ አንቺስ ከመንግሥት አዳራሽ ውጭ መኖር አይገባሽምና ለምን ይህን ከንቱ ነገር (ሞትን) ትወጃለሽ?" አላት፡፡ ቅድስት አርሴማም "የጎሰቆልክ ጤልሜዎስ ሆይ ለእኔስ ሰማያዊው ንጉሥ በመንገሥቱ አዳራሽ አዘጋጅቶልኛል" አለችው፡፡ ከዚህም በኋላ መኮንኑ ሰማዕታቱን ከእሥር ቤት ጣላቸውና ቅድስት አርሴማን ግን ከአጃቢዎች ጋር በክብር አስቀምጦ ምግብ መጠጡን አዘጋጀላት፡፡ እርሷ ግን ለሰማዕታቱ ስለ ሰማያዊው ስጦታቸው ትነግራቸው ነበር እንጂ ምግቡን አልቀመሰችም፡፡ ከሃዲው መኮንኑም ቅድስት አርሴማን "እሽ ብለሽኝ አንቺን ካገባሁ በቤቴ ያሉትን ሚስቶቼን ሁሉ አባርሬ አንቺን ብቻ ሚስት አድርጌ እስከ ዕለተ ሞቴ ድረስ እኖራለሁ ለዚህም በትላልቅ አማልክቶቼ ስም እምምልሻለሁ" ብሎ መልእክተኛ ላከባት፡፡ ቅድስት አርሴማም መልአክተኞቹን መጻሕፍትን እየጠቀሰች የዓለምን ከንቱነትና የክርስቶስን ፍቅር አስተማረቻቸው፡፡ እርሷም የእግዚአብሔርን ቃል ስትነግራቸው ልባቸው እየተቃጠለ ያለቅሱ ነበር፡፡ እነርሱም "በቃልሽ አምነናል ጸሎትሽ ኃይል ይሁነን" አሏት፡፡
መኮንኑም የቅድስት አርሴማን መልስ በሰማ ጊዜ በታላቅ ቁጣ ሆኖ ሰማዕታቱን ይዞ በማሠቃየት የበላዩ ወደ ሆነው ወደ አርማንያው ንጉሥ ድርጣድስ ዘንድ እንዲወስዷቸው አዘዘ፡፡ የአገሩ ሰዎችም ቅድስት አርሴማ ሰማዕት ትሆን ዘንድ ፈቅዳ ወደ ንጉሡ ዘንድ እንደሄደች ለእናቷ ለአትኖስያ ነገሯት፡፡ እናቷም መጥታ "ልጄ ሆይ ወደሞት ለምን ትሄጃለሽ? ወደ ሞት መሄድሽን እያየሁ አሁን ልቤ እንዲህ በሀዘን ከሚሰበር መነው መጀሪያውኑ ባልወለድኩሽ ይሻለኝ ነበር" አለቻት፡፡ ቅድስት አርሴማ ግን የክርስቶስን ፍቅር ለእናቷ አስረዳቻት፡፡ በኪልቂያ አጋታ ብለው የሚጠሯት ወላጅ እናቷ አትኖስያም "አስተማሪዬ ልጄ አርሴማ ሆይ! እባክሽ እሺ በይኝ…" እያለች ብዙ ብትለምናትም ቅድስት አርሴማ ግን እናቷንና የአገሯን ሰዎች ተሰናብታ ስትሄድ ሁሉም እያለቀሱ ሸኟት፡፡ በመንገድም ሳለች ቅድስት አርሴማን ወደ ንጉሥ ድርጣድስ የሚወስዷት ጭፍሮች ከሰማዕታቱ ጋር ሄዳ ሰማዕት ከምትሆን ይልቅ ወደ እናቷ መመለስ ብትፈልግ እንደሚመልሷት ነገሯት፡፡ እርሷ ግን "ከሰው ፍቅር ይልቅ የእግዚአብሔር ፍቅር ይበልጣል" አለቻቸው፡፡
ሰማዕታቱም አርማንያ አገር እንደደረሱ ጭፍሮቹ የሰማዕታቱን እግሮቻቸውንና እጆቻቸውን እንዳሠሯቸው ለንጉሥ ድርጣድስ አስረኩቧቸው፡፡ መኮንኑም ለንጉሡ "ጌታዬ ሆይ እነሆ አንተ የምታመልካቸውን ጣዖቶችህን የማያመልኩትን ብዙ ክርስቲያኖችን ሰቀልናቸው፣ ገደልናቸው፡፡ የቀሩትንም እየገረፍን ይኸው ከፊትህ አቁመናቸዋል የወደድከውን አድርግባቸው፡፡ አንዲትም ውብ ሆነች ሴት ልጅ አብራቸው መከራ መቀበልን መርጣ መጥታለች የመልኳንም ማማርና ደም ግባቷን ባየን ጊዜ ደንግጠን በእርሷ ላይ አንዳች ክፉ ማድረግ አልተቻለንም" አለው፡፡ ንጉሡም ያመጧት ዘንድ ሲነግረው መኮንኑ "ነገር ግን ጌታዬ ሆይ እርሷ በመልክ የሚስተካከላት የሌለ እጅግ ውብ ብትሆንም 'ከሕይወት ይልቅ መሞት ይሻለኛል' ይምትል ናት" አለው፡፡ ከዚህም በኋላ ሰማዕታቱን ወደ እሥር ቤት በመውሰድ ቅድስት አርሴማን ግን ይዘው ወደ ንጉሡ ዘንድ አመጧት፡፡ እርሷም ወደ ንጉሡ አዳራሽ እያማተበች ስትገባ ንጉሡ ባየት ጊዜ ልቡ ታወከ፡፡ ሰማዕቷ ግን "ከሰማያትና ከምድር ንጉሥ ከእግዚአብሔር አምላኬ ትለየኝ ዘንድ የወደድክ ሰነፍ ንጉሥ ሆይ! የሰይጣን መልአክተኛና የጥፋት ልጅ የይሁዳ ወገን ከእኔ ምን ትሻለህ? ከወደድክስ በእጅህ ሰማዕት እሆን ዘንድ እወዳለሁ" አለችው፡፡ ከዚህም በኋላ ሰማዕቷ በጸለየች ጊዜ ቅዱስ ሚካኤልና ቅዱስ ገብርኤል በታላቅ ግርማ ተገለጡላት ነገር ግን ቅድስት አርሴማ "ጌቶች ሆይ! ነፍሰ ገዳይ እንዳልባል በማንም ላይ ጥፋት አይድረስ" ብላ ለመነቻቸው፡፡ ሊይዟት የመጡት ሰዎችም ግርማዋን አይተው ፈሩ፡፡ ሰውነቷንም ቀርበው እንዳይነኳት የመለኮት ኃይል ከለከላቸው፡፡ እነርሱም "ይህች ሴት አስማተኛ ናት፣ ጥበብና ምትሃት አላት" ብለው ለንጉሡ በነገሩት ጊዜ እርሱም "ዛሬ ያሸነፍሽኝ እንዳይመስልሽ ነገ ብርቱዎች በሆኑ አማልክቶቼ ኃይል ድል አደርግሻለሁ" አላት፡፡ እርሷም "ዛሬም ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ይረዳኛል፣ በእኔ በኃጢአተኛይቱና በደካማይቱ ኃይል አይደለም፡፡ በእነዚህ ቅዱሳን ሰማዕታት የጸሎት ኃይል እንጂ" በማለት መለሰችለት፡፡ ሰማዕታቱም ከቅድስት አርሴማ ጋር በእሥር ቤት ሳሉ "የእግዚብሔርን ኃይል በአንቺ ላይ አይተናልና በጸሎትሽ አስቢን" አሏት፡፡ እርሷም "በገድላችሁ ብርታት ለእኔ ጸልዩልኝ" አለቻቸው፡፡ ቅድስት አርሴማ ሌሊት ታላቅ ምሥጢርን አየች፡፡ እልፍ አእላፋት የብዙ ብዙ የሚሆኑ ቅዱሳን መላእክት የሥላሴን ዙፋን ከበው "የጌትነትህ ምስጋና ሰማይንና ምድርን መላ ፍጹም አሸናፊ እግዚአብሔር ቅዱስ ቅዱስ ቅዱስ" እያሉ ሲጮኹ ተመለከተች፡፡ ይህንንም የመላእጅትን ዜማ እንደሰማችና እንዳየች ለሰማዕታቱ ነገረቻቸው፡፡ "ከእነዚህም መላእክት ውስጥ አንዱ ወደ እኔ ተልኮ መጣና በቀኜ ቆሞ በጥላው ሸሽጎ የሕይወትን እንጀራ መግቦኝ የድኅነትን ጽዋ አጠጣኝ፡፡ ያንጊዜም ሥጋዬ ወደ ምድር ወረደ፣ በላዬም ነፍሴ ተመለሰቸ፡፡ ከእንቅልፍ እንደሚነቃና የወይን ጠጅ ጠጥቶ ስካሩ እንደተወው ሰው ነቃሁ" አለቻው፡፡
በነጋም ጊዜ ንጉሡ በፍርዱ ዙፋን ተቀምጦ ሰማዕታቱን ከእሥር ቤቱ አውጥተው ወደ ፍርድ አደባባይ ያመጧቸው ዘንድ አዘዘ፡፡ በፊቱም አቁሞ ለጣዖታት አማልክቶቹ እንዲሰግዱና እንዲሠው አዘዛቸው፡፡ እነርሱም "እኛስ የምናመልከው እውነተኛ አምላክ አለን ለረከሱ ጣዖታት አንገዛም" ባሉት ጊዜ "ትእዛዜን ካልፈጸማችሁ ሰውነታችሁን በትንሽ በትንሹ እየቆራረጥኩ እጥለዋለሁ" አላቸው፡፡ ሰማዕታቱም "በሚያስፈራ ቃልህና በቅጣትህ የምንፈራና አምላካችንን ክርስቶስን የምክደው አይደለንም፡፡ ስለ አምላካችን ስለ ኢየሱስ ክርስቶስ ስም ነፍሳችንን እንሰጥ ዘንድ ወደ አንተ መጥተናል" አሉት፡፡ ያን ጊዜም ንጉሡ ድርጣድስ እጅግ ተቆጥቶ "ይህችን ሴት በማስቀደም ጽኑ ቅጣት ቅጧቸው የምታስተምራቸው እርሷ ናትና" ብሎ አዘዘ፡፡ ጭፍሮቹም "የሴት ልቧ ደካማ ነውና ቅድሚያ ወንዶችን አሠቃይተን ብንገድል ሴቶቹ ለጣዖቶችህ ይገዛሉ" በማለት ወንዶቹን ለብቻ ወስደው ለተራቡ አንበሶችና ሌሎች አውሬዎች ሰጧቸው፡፡ ቅድስት አርሴማም አጽናናቻቸውና ተሰነባብተው ወደ ሰማዕትነት ገቡ፡፡ ነገር ግን የተራቡት አንበሶችና ሌሎችም አውሬዎች ወደ ሰማዕታቱ መቅረብ አልተቻላቸውም ይልቁንም በሰማዕታቱ ፊት ሰገዱላቸው፡፡ በጅራታቸውም እየዳሰሷቸው አጫወቷቸው፡፡ የቅድስት አርሴማንም የእግሯን ትቢያ ላሱ፡፡ እርሷም በእጆቿ ዳሰሰቻቸው፡፡ አውሬዎቹም ብረቱን እየበጠሱ ንጉሡ ከመንግሥቱ ዙፋን እስኪወድቅ ድረስ አባረሩት፡፡ ወታደሮቹንም ሲያባርሯቸው ከእነርሱ ውስጥ 300 ጭፍሮች ሞቱ፡፡ የተረፉትም ይህንን ተአምር ሲያዩ እጅግ እያደነቁ ሰማዕታቱ ምትሃተኞች መሆናቸውን ተናገሩ፡፡ ይልቁንም ቅድስት አርሴማን "እርሷ መመኪያቸውና መሪያቸው ናትና አስቀድመን እንግደላት" አሉ፡፡
ከዚህም በኋላ ጥልቅ ጉድጓድ ቆፍረው በውስጡ እሳትን አንድደው ሰማዕታቱን ከዚያ ይጨምሯቸው ዘንድ ሲመክሩ ንጉሡ በዚህ ምክራቸው ደስ ተሰኘ፡፡ እንደምክራቸውም ጥልቅ ጉድጓድ ቆፍረው በውስጡ እሳት አንድደው የተለያዩ ሰውነትን ቆራርጠው የሚጥሉ እንደ ዲን፣ ሙጫ፣ ቅንጭብ ጨምረው የእሳቱ ነጎድጓድ እስኪሰማ ድረስ አንድደው ሰማዕታቱን ከዚያ እንዲጨምሯቸው ንጉሡ አዘዘ፡፡ ቅድስት አርሴማንም "አሁን ከዚህ ማን እንሚያድንሽ አያለሁ" አላት፡፡ እርሷም "እኛንስ አምላካችን እንደሚያድነን አሁን ታያለህ አንተ ግን ከዚህ ክፋትህ ካልተመልስክና ጣዖት ማምለክህን ትተው እውነተኛውን አምላክ ካላመለክህ በኋላ ከዘላለማዊው እሳት ወዴት ትሸሻለህ? በማስ ትማጸናለህ? በዕንጨት ነውን ወይስ በድንጋይ?..." በማለት ስለ ዕለተ ምጽዓት ሌላም ብዙ ነገር አስተማረችው፡፡ በዚህም ጊዜ ከወታደሮቹ አንዱ ተነሥቶ በኃይል ሲመታት ከአፍንጫዎቿ ደም እንደ ውኃ ፈሰሰ፡፡ ንጉሡም "በዚህ የምተውሽ አይደለሽም ሥጋሽን በእሳት አቃጥለዋሁ" በማለት ተናገራት፡፡ ያንጊዜም ምድር አፏን ከፍታ ያንን የመታትን ወታደር ዋጠችው፡፡ ይህንንም ያዩ ሁሉ በማድነቅ እጅግ ፈሩ፡፡ ንጉሡም ፈርቶ ከዙፋኑ ላይ ፈጥኖ ተነሣ፡፡ ቅድስት አርሴማም ፈገግ ብላ በእርሱ ይመጣ ዘንድ ያለውን ነገር ትንቢት ነገረችው፡፡ "እግዚአብሔር ስለ እኛ ይበቀልሃል፣ የአጋንንትም ማደሪያ ያደርግሃል፣ እንደ ጅብ በራስህ ሥጋህን እስከምትበላ ድረስ ያሳብድሃል፡፡ መልክህና ምሳሌህ ይለወጣል፣ እንደ በረሃ እሪያም ትሆናለህ፣ የምትናገረውን አታውቅም፣ የእርኩሳን አጋንንት የእግራቸው መረገጫ ትሆናለህ፡፡ ያንጊዜም የሙታንን ትንሣኤ ተስፋ ትታመን ዘንድ አለህ ይህ እንደሚሆንብህ በእውነት እነግርሃለሁ" አለችው፡፡ ንጉሡም ይህን ጊዜ "እናተን በክፉ ቅጣት አሠቃይቼ ከገደልኩ በኋላ ይህን አሁን ያልሽውን ብሆን አይሳዝነኝም" አላት፡፡ ይህንንም ሲነጋገሩ ወታደሮቹ መጥተው የእሳቱ ነበልባል ከሩቅ እስኪታይ ድረስ እንደነደደ ነገሩት፡፡ እርሱም ሰማዕታቱን ከእሥር ቤት አውጥተው በማምጣት ከቅድስት አርሴማ ጋር በእቶኑ እሳት ውስጥ ይጥሏቸው ዘንደ አዘዘ፡፡ ቅድስት አርሴማም ሰማዕታቱን ካጽናናቻቸውና ከመከረቻቸው በኋላ በመስቀል ምልክት አማትባ ማንም ገፍቶ ሳይጨምራት ራሷን ወደ እሳቱ ውስጥ ወረወረች፡፡ ቀጥሎም ዲያቆን ጤሜልዮስ ወደ እሳቱ ተወርውሮ ገባ፡፡ ታላቃቸው ጌርሎስም እንዲሁ ራሱን ወርውሮ ወደ እሳቱ ውስጥ ገባ፡፡ ሁሉም እንዲሁ በየተራ ራሳቸውን እየወረወሩ ገቡ፡፡ በጎች ወደ ወንዝ ውኃ እየሮጡ እንደሚገቡ ሁሉም ሰማዕታት ራሳቸውን እየወረወሩ ወደ እቶኑ እሳት ገቡ፡፡ ይህንንም ሲያደርጉ ያዩአቸው ወታደሮች ሁሉ በሀዘኔታ አለቀሱላቸው፡፡ ነገር ግን ወዲያው ሰማዕታቱ ከእሳቱ ውስጥ ሆነው እግዚአብሔርን በሰላም ሲያመሰግኑ አዩአቸውና እጅግ ተደነቁ፡፡ ቅድስት አርሴማም በዚያ ላሉት ሁሉ ወደፊት በንጉሡ ላይ የሚሆነውን ነገር በትንቢት ነገረቻቸው፡፡
ከዚህም በኋላ ንጉሥ ድርጣድስ ቅድስት አርሴማን እንደበቀሉለትና እንዲያጠፉለት ወደ አማላከቶቹ ቤት ይወስዷት ዘንድ የሠራዊቱን አለቆች አዘዛቸው፡፡ ወደ አማልክቶቹም ቤት በወሰዷት ጊዜ በዚያ ሆና ስትጸልይ በወንዶች አምሳል የተሠሩ 77 እና በሴቶች አምሳል የተሠሩ 33 ጣዖታት ሁሉ ተሰባበሩ፡፡ ከአንገታቸው የተሰበሩ አሉ፣ እግሮቻቸውና እጆቻቸው የተሰበሩ አሉ፣ ወገባቸው የደቀቁ አሉ፣ እንደትቢያም የተነተኑ አሉ፡፡ በምድርም ታላቅ ንውጽውጽታ ሆነ፡፡ የመላእክት አለቃ ቅዱስ ሚካኤልም እንደመብረቅ ባለ ድምጽ መጥቶ ምድሪቱን መላትና በዚያ ያሉ ጣዖታት በሙሉ እንደትቢያ ጠፉ፡፡ ቅድስት አርሴማም ይህንን ባየች ጊዜ ደስ ተሰኝታ የሆነውን መጥቶ ያይ ዘንድ ወደ ንጉሡ ላከችበት፡፡ ንጉሡም በመጣ ጊዜ "አምላኬ መልአኩን ልኮ አዳነኝ፣ ጣዖታቶችህንም እንዳልነበሩ አደረጋቸው እህግዲህስ እፈር" አለችው፡፡ ንጉሡም "በምትሃትሽ ይህንን እንዳደረግሽ ዐውቀለሁ" አላትና ወደ እስር ቤት ወስዶ ከሰማዕታቱ ጋር ጨመራት፡፡
ሰማዕታቱም በእስር ቤት ሆነው እህልና ውኃ ከቀመሱ ሰባት ቀን ሆኗቸዋልና ርሀቡና ጥሙ እጅግ ጠናባቸው፡፡ ያንጊዜም ቅድስት አርሴማ ተነሡ እንጸልይ አለቻቸውና ቢጸልዩ ብርናኤልና አቅናኤል በሚባሉ ሁለት ቅዱሳን መላእክት እጅ ሰማያዊ ኅብሥትባ የገነት ውኃ መጣላቸው፡፡ ከመካከላቸውም ካህኑ ኢያሴኖስ ባርኮ ለሌሎቹ ሰማዕታት ሰጣቸውና ተመግበው ፈጣሪያቸውን አመሰገኑ፡፡ የተረፋቸውም ኅብሥት በመላአክቱ እጅ ወደ ሰማይ ወጣ፡፡
በማግሥቱም ንጉሡ ወደ ፍርድ አደባባይ ባወጣቸው ጊዜ ሰማዕታቱ ፊታቸው እንደፀሐይ ያበራ ነበር፡፡ የእሥር ቤት ጠባቂውንም ጠርቶ "እህል ያበላሃቸውና የነገሥታትን ልብስ ያለበስካቸው ለምንድነው?" ብሎ ተቆጣው፡፡ ጠባቂውም "ጌታዬ ሆይ እነርሱስ ሳይበሉ ሳይጠጡ ይረካሉ እንጂ የሰጠኃቸው ምንም ነገር የለም"*አለው፡፡ ቃሉንም በመሐላ ካጸናለት በኋላ "ነገር ግን ንጉሥ ሆይ በሌሊት እሥር ቤት በብርሃን ተጥለቅልቆ አይቼዋለሁ፡፡ ዳግመኛም ሃያ ሰባት የብርሃን አክሎችም ሲወርዱ አየሁ" አለው፡፡ ቀጥሎም ይህ ጠባቂ "ንጉሥ ሆይ እኔም በእነዚህ ሰማዕታት አምኛለሁ" አለው፡፡ ወደ ቅድስት አርሴማም ዞሮ "እመቤቴ ሆይ በጸሎትሽ አስቢኝ" በማለት ሌሎቹንም ሰማዕታት ተመጸናቸው፡፡ ንገሡም በዚህ እጅግ ተቆጥቶ ራሱን በሰይፍ አስቆረጠው፡፡ እርሱም በጣዖት የሚያመልክ አረማዊ ቢሆንም አምኖ በደሙ ተጠምቋልና የሰማዕትነትን የክብር አክሊል ተቀዳጀ፡፡ ቅዱሳን የሆኑ ሰማዕታቱም ይህን አደነቁ ሰማዕትነትን በመፈጸም ቀድሟቸዋልና፡፡ በድኑንም በምድረ በዳ ጣሉት ነገር ግን አውሬዎችና አሞራዎች አልበሉትም ቅዱሳን መላእክት ይጠብቁታልና፡፡
ንጉሡም ሰማዕታን በጽኑ ዱላዎች ካስደበደባቸውና ለእያንዳንዳቸው ሌላ ሦስት ሦስት መቶ ግርፋት ካስገረቸው በኋላ ወደ እሥር ቤት መለሳቸው፡፡ በመግስቱም ቅድስት አርሴማን አስመጥቶ ከእርሱ ጋር ትሴስን ዘንድ አባበላት፡፡ "ንግሥት አድርጌሽ በወርቅ ዙፋኔ ላይ ትቀመጫለሽ፣ በአርማንያ ካሉ ሴቶች ሁሉ በላይ አደርግሻለሁ…" እያለ አባበላት፡፡ ቅድስት አርሴማ ግን "ልብህ የደነደነ ሰነፍ ሆይ ኃጢአትህን ሁሉ ይቅር ይልህ ዘንድ ወደ አምላክህ እግዚአብሔር ትመለስ ዘንድ በተሻለህ ነበር …" እያለች አስተማረችው፡፡ ስለ ጌታችንም መንገሥት ካስተማረችው በኋላ "እኛ ሰማዕታቱ ስለ አንተ እንጸልይልሃለን" አለችው፡፡ ንጉሡ በዚህ ጊዜ ማመኔን ብትወጂ ግን ከእኔ ጋር ተስማምተሽ እንጋባለን ለአምላክሽም እገዛለሁ" ሲላት ወዲያው እርኩስ መንፈስ ፊቱን መታውና "ከእናትህ መኅፀን ጀምሮ ያሳደኩህና በሥራህ ሁሉ ልብ፣ አፍና ብርታት ሆኜ በኃይሌም ብርታት የክርስቲያን ልጆችን እንድታስጨንቃቸውና እንትገድላቸው ያደረኩህን እኔን ለምን ተውከኝ? ስለዚህች ሴት ብለህ እግዚአብሔር አምላክን ታመልክ ዘንድ ወደድክን! ..." እያለ በቁጣ ሆኖ አፉን አጣመመውና ምድር ላይ ጣለው፡፡ ከዚህም በኋላ ለጣዖታቱ ይሰግዱ ዘንድ ሰማዕታቱን በቁጣ አዘዛቸው፡፡ ነገር ግን የጣዖታቱ ካህናት መጥተው ጣዖታቱን ቅድስት አርሴማ እንዳጠፋቻቸው ነገሩት፡፡ ዳግመኛም "እርሷን ካልገደልካት አገራችን ትጠፋለች፣ መንግሥትህ ተሻራላች" አሉት፡፡
ከዚህም በኃላ ከቅድስት አርሴማ ጋር ያሉትን 27ቱን ሰማዕታት ስሙ ጋብጋቦ ወደሚባል ወንዝ ወስደዋቸው አንገታቸውን በሰይፍ ቆረጧቸውና የሰማዕትነት ፍጻሜአቸው ሆነ፡፡ ከእነርሱም አንደኛውን በቅድሚያ አንገቱን ሲቆርጡት ሥጋው ወደ ምድር ወደቀ፡፡ ራሱ ግን ለብቻ ለአንድ ሰዓት ያህል ቆመች፡፡ ቡርክት ቅድስት አርሴማም ሮጣ ሄዳ የሰማዕቱን በርቲኖስን ራስ ያዘቻትና ወደ አንገቱ መለሰቻት፡፡ እርሱም "ሰማዕት ለመሆን እኔን ስላስቀደመ አምላኬ እግዚአብሔርን አመሰግነዋለሁ" እያለ ሦሰት ጊዜ ተነፈሰ፡፡ ለቅድስት አርሴማም "እመቤቴ ሆይ መምጣትን እንዲያፋጥኑ ከፀሐይ ይልቅ የምታበራ አገርን እንዲያዩ ለወንድሞቻችን ለእኅቶቻችን ነገሪያቸው" አላት፡፡ እርሷም ወደ ሰማዕታቱ ዞራ "ወንድማችን በገነት ያየውን ይነግረንና ያሳየን ዘንድ በሕይወት ኖሯል እንጂ አልሞተም" አለቻቸው፡፡
ከዚህም በኃላ ሰማዕታቱ እግዚአብሔርን አመስግነው "እኔ አስቀድሙ እኔ አስቀድሙ..." እያሉ ወታደሮቹን ለመኗቸው፡፡ እየተሻሙ በየተራ እየተሰየፉ ሰማዕትነታቸውን ፈጽመው የክብር አክሊልን ተቀዳጁ፡፡ የእነዚህም የ27ቱ ክቡራን ሰማዕታት ስማቸው ይህ ነው፡- ካህኑ ኢያሚኖስ፣ አፍጢኖስ፣ በርቲኖስ፣ ጢሞና፣ ጢሞዓና፣ ዘኬዎስ፣ እስጢፋኑ፣ አርሞና፣ ኪርያኮስ፣ አንጥያኮስ፣ ያዕቆብ፣ ቡራኬሌስ፣ አስቂርያቆስ፣ አስኪርያኖስ፣ ሚርያኖስ፣ ትትግርጦስ፣ ያስቲኖስ፣ ጥልያኖስ፣ ዑልያኖስ፣ ጴርቅላስ፣ ኬብያኖስ፣ ጴጥሮስ፣ ጳክንዮስ፣ ሐናንያ፣ ሐሊባኖስ፣ ኤስያኖስ እና ኤልያብ ናቸው፡፡
ቅድስት አርሴማም የሰማዕታቱን ራሶቻቸውን ትሰበስብ ነበር፡፡ ወደ ሥጋቸውም ታጋጥመው ነበር በዚያም ጊዜ እንደመጀመሪያው ይሆናል፡፡ እንዳልተቆረጠም ይሆናል፡፡ ልብሶቻቸውንም ታለብሳቸዋለች፡፡ ይህንንም ታላቅ ተአምር ያዩ 92 የንጉሡ ወታደሮች ወደ ንጉሡ ሄደው "እኛም በአምላካቸው አምነን ክርስቲያን ሆነናል" በማለት መሰከሩ፡፡ ንጉሡም በፈረስ ገመድ ላይ አስሮ ሥጋቸው ተቆራርሶ እስኪወድቅ ድረስ ካሠቃያቸው በኃላ አንገታቸውን ሰየፋቸውና የክብር አክሊልን ተቀዳጁ፡፡ ዳግመኛም በእነርሱ ምክንያት ሌሎችም አመኑ፡፡ ከዚህም በኃላ ንጉሡ ቅድስት አርሴማን ውበቷን እያሰበ ልቡናውን ሳተ፡፡ ድንግልናዋንም ሊያረክስ ሽቶ እናቷን አጋታን እንድታባብልለት አዘዛት፡፡ እናቷም ሄዳ "ልጄ ሆይ ስሚ ይህ አረማዊ እንዳያረክስሽ ተጠንቀቂ" አለቻት፡፡ ንጉሡም ቅድስት አርሴማን "መንግሥቴንና ግዛቴን ሁሉ አወርስሻለሁ" እያለ በመሀላ ቢለምናትም እሺ እንደማትለው ሲያውቅ ይዞ በግድ ወደ እልፍኙ ሊያስገበት ሲል ቅድስት አርሴማ ይዛ መሬት ላይ ጣለችው፡፡ በእርሷ ላይ ያደረ የመንፈስ ቅዱስ ኃይል ሞገስ ሆኗታልና፡፡
እርሱ ግን በጦርነት እጅግ የበረታ ኃይለኛ ስለነበረ አሁን በታናሽ ሴት ብላቴና ስለተሸነፈ አፈረ፡፡ በዚህም እጅግ ተናዶ ለሥጋዊ ፈቃዱም እንደተመኛት ሊያገኛት ስላልቻለ ተስፋ ቆርጦ በንዴት አንገቷን ይቆርጧት ዘንድ አዘዘ፡፡ የቅድስት አርሴማንም ራሷን ቆረጧትና የሰማትነት ፍጻሜዋ ሆነ፡፡ ከአንገቷም ደም፣ ውኃ፣ ወተትና ማር ወደ አራቱም አቅጣጫ ፈሰሰ፡፡ እርሷና ሌሎቹም 72 ሰማዕታት ከተሰየፉ በኃላ ሥጋቸው ቀምድር ላይ ተጥሎ ቀረ፡፡ ንጉሡም ጋኔን ተጭኖበት መልኩ ተለውጦ እንደ እሪያ ሆነ፡፡ ከዚያ በፊት የአርማንያውን ሊቀ ጳጳሳት አቡነ ጎርጎርዮስን ንጉሡ ድርጣድስ ዕጣን ሊያሳርግ ወደ ጣዖት ቤቱ ሲገባ አቡነ ጎርጎርዮስን ጠርቶ ለአማልክት ዕጣን አሳርጉ ቢላቸው እሳቸውም ትእዛዙን አልፈጽምም ባሉት ጊዜ እጅግ ጽኑ በሆኑ በተለያዩ ሥቃዮች ካሠቃያቸው በኃላ ጥልቅ ጉድጓድ አስቆፍሮ በዚያ ውስጥ ጣላቸው፡፡ አባታችንም በዚያ ጥልቅ ጉድጓድ እንደተጣሉ ለ15 ዓመታት ኖሩ፡፡ ስለምግባቸውም እግዚአብሔር አንዲት እናትን አዘዘላቸው፡፡ በንጉሡ አዳራሽ አቅራቢያም የምትኖረው ይህች ሴት በእግዚአብሔር ታዝዛ እንጀራን እየጋገረች ወደ ጉድጓዱ ትጥልላቸው ነበር፡፡ ከእርሷም በቀር አባታችን በሕይወት መኖራቸውን የሚያውቅ ሰው የለም፡፡ እንዲህም እያደረገች 15 ዓመት ኖራለች፡፡
ንጉሡ ድርጣድስም ቅድስት አርሴማን ማግባት ፈልጎ ሳለ ፈጽሞ እምቢ ብትለው በእርሷ ምክንያት ብዙ ደናግል ሴቶችን ገደለ፡፡ ሰይጣን በልቡ ያደረበት ይህ ንጉሥ ድርጣድስም ደናግሎቹን እና ቅድስት አርሴማን በብዙ ሥቃይ ከገደላቸው በኋላ ሥጋቸውን በተራራ ላይ ጥሎት ነበር፡፡ ነገር ግን ምንም ሳይሆን በጌታችን ጥበቃ ኖረ፡፡ የቅድስት አርሴማንም ውበቷን እያሰበ ስላስገደላት የሚጸጸት ሆነ፡፡ ወገኖቹም ‹‹ከሀዘንህ ታርፍ ዘንድ ወደ ጫካ ሄደን አውሬ አድን›› አሉት፡፡ ንጉሡም በፈረሱ ተቀምጦ ወደ ጫካ ወጣ፡፡ ነገር ግን ሰይጣን ተዋሃደውና በእነ ቅድስት አርሴማና በአቡነ ጎርጎርዮስ ላይ በሠራው ግፍ እግዚአብሔር የተፈጥሮ መልኩን ቀይሮት እንደ እሪያ አደረገው፡፡ ንጉሥ ናቡከደነጾር ከእግዚአብሔር ቁጣ የተነሣ አእምሮው ስቶ ልቡ ተሰውሮ ወደ እንስሳነት እንደተለወጠ ሁሉ (ዳን 4፡28-37) ንጉሥ ድርጣድስም እንዲሁ ከእግዚአብሔር ቁጣ የተነሣ ወደ እሪያነት ተለወጠ፡፡
ንጉሡ ድርጣድስ ወደ እሪያነት ከተለወጠ በኋላ ያገኘውን ሁሉ የሚናከስ ሆነ፡፡ በቤተ መንግሥቱም ባሉ ሰዎች ላይ ሰይጣን አደረባቸውና ታላቅ ጭንቅ ሆነ፡፡ የንጉሡም እኅት በሌሊት "ጎርጎርዮስን ከጉድጓድ ካላወጣችሁት በቀር አትድኑም" የሚል ራእይ አየችና ለወገኖቿ ነግረቻቸው፡፡ የሞተ መስሏቸው ስለነበር ይህን ሲሰሙ እጅግ ደነገጡና ሄደው ቅዱስ ጎርጎርዮስን 15 ዓመት ተጥሎ ከኖረበት ጉድጓድ ውስጥ በገመድ ጎትተው አወጡትና አክብረው ወሰዱት፡፡
እርሱም የእነ ቅድስት አርሴማን ሥጋ ወዴት እንዳደረሱት ሲጠይቅ በተራራው ላይ እንዳለ ነግረውት ሄዶ ሲያየው ምንም ሳይነካው በደህና አገኘው፡፡ አንሥቶም ባማሩ ቦታዎች አኖራቸው፡፡ ሰይጣን ያደረባቸውን የቤተ መንግሥቱንም ሰዎች ፈወሳቸው፡፡ ስለ ንጉሡም ወደ አውሬነት መለወጥ ነግረውት እንዲፈውሰው ለመኑት፡፡ አቡነ ጎርጎርዮስም ወደ ንጉሡ ሄደው በእሪያነቱ ሳለ "ብፈውስህና ባድንህ ከክፉ ሥራህ ትመለሳለህ? በእውነተኛው አምላክ በኢየሱስ ክርስቶስ ታምናለህ?" አሉት፡፡ እሪያ የነበረው ንጉሥም "አዎ" ቢላቸው ጸሎት አድርገው ፈውሱት፡፡ አእምሮውና የቀድሞው መልኩም ተመለሰለት፡፡ ነገር ግን አቡነ ጎርጎርዮስ ንጉሡ ዳግመኛ እንዳይታበይ በማለት ከእግሩ ላይ የእሪያ ጥፍር አስቀሩለት፡፡
የቤተ መንግሥንም ሰዎች ሁሉ ከፈወሳቸው በኋላ 8 ቀን እንዲጾሙ አዘዛቸው፡፡ ሃይማኖትንም አስተምሮ ሥርዓት ሠራላቸው፡፡ እርሱም ክህነት አልነበረውምና ወደ ሮሜው ንጉሥ ወደ አኖሬዎስና ወደ ሊቀ ጳጳሳቱ መልአክት ላኩና ጳጳስ ይላኩላችሁ አላቸው፡፡ የሮሙ ሊቀ ጳጳሳትም ጎርጎርዮስን ሾሞ ላከላቸው፡፡ ንጉሡ አኖሬዎስም በዚህ ተደሰተ፡፡ ጎርጎርዮስም ተሹሞ ከመጣ በኋላ ሁሉንም አጠመቃቸው፡፡ አርማንያም በቅዱስ ጎርጎርዮስ ትምህርት በክርስትና የምትታወቅ አገር ሆነች፡፡ እርሱም በእመቤታችን ስም ቤተ ክርስቲያን ሠራላቸው፡፡ ምእመናንያንም የሰማዕታቱን ሥጋ ሰብስበው በመልካም ቦታ ካስቀመጡት በኃላ የመከራው ዘመን ሲያልፍ የተዋበች ቤተ ክርስቲያን ሠርተው የቅዱሳኑን በዚያ አኖሩ፡፡ ከሥጋቸውም ብዙ ድንቅ ድንቅ ተአምራት ተፈጽመው ታዩ፡፡
የቅድስት አርሴማ ዕረፍቷ መስከረም 29 ነው፡፡ የቤተክርስቲያኗም ቅዳሴ በአርማንያ አገር፣ በኪልቂያ፣ በሶርያ፣ በአንጾኪያና በግብፅ አውራጃዎች ሁሉ በታኅሣሥ ወር በ6ኛው ቀን ሆነ፡፡ ጌታችን ከገባላት ብዙ ቃልኪዳን ውስጥ አንደኛው "ልጁን በአንቺ ስም የጠራውን በመንግሥተ ሰማያት የበለጠና የከበረ ስምን እኔ እሰጠዋለሁ" የሚል ነው፡፡

በዚህችም ቀን ቅዱስ አባት የእስክንድርያ አገር ሊቀ ጳጳሳት የአባ አብርሃም ሶርያዊ የዕረፍቱ መታሰቢያ ነው እርሱም ለአባቶች ሊቃነ ጳጳሳት ስልሳ ሁለተኛ ነው። ይህም አባት ከምሥራቅ አገር የክርስቲያን ወገን ነው እርሱም ብዙ ገንዘብ ያለው ነጋዴ ነበር እየነገደም ብዙ ጊዜ ወደ ምስር አገር ደረሰ ከዚህም በኋላ በውስጧ የሚኖር ሆነ ከእርሱም ለድኆችና ለችግረኞች ርኅራኄ ማድረግና ብዙ ትሩፋቶች ተገለጡ።
የደግነቱና የትሩፋቱ የአዋቂነቱም ዜና በተሰማ ጊዜ አባቶች ኤጲስቆጶሳት የሀገር ታላላቆችና ምሁራኖች በእስክንድርያ አገር ሊቀ ጵጵስና ይሾሙት ዘንድ ተስማሙ።
በዚያንም ጊዜ በእግዚአብሔር ፈቃድ ሊቀ ጵጵስና ተሾመ ከዚህም በኋላ ገንዘቡን ሁሉ ለድኆችና ለችግረኞች ሰጥቶ የሊቀ ጵጵስናውን ሥራ መሥራት ጀመረ። በሹመቱም ወራት ክፉ ልማድን ሁሉ አስወገደ ኤጲስቆጶሳቱንም ስለ ክህነት ሹመት መማለጃ እንዳይቀበሉ አወገዛቸው ዕቁባቶች ያሉአቸውንም ሰዎች ዕቁባቶቻቸውን እንዲተው አወገዛችው ውግዘቱንም በሰሙ ጊዜ ሁሉም ፈርተው ክፉ ልማዳቸውን ተዉ ወደርሱም መጥተው ከእግሮቹ በታች ወድቀው በደላቸውን ያስተሰርይላቸው ዘንድ ለመኑት።
የንጉሥ ጸሐፊ ከሆነ ከአንድ ሰው በቀር ቃሉን ያስተሐቅር ዘንድ የደፈረ ማንም የለም። ይህም ልዑል እግዚአብሔርን ስለ ማይፈራ የዚህን የቅዱስ አባት ግዝትን አልፈራም ይህ አባት ግን ስለ ራሱ ድኅነት ብዙ ጊዜ ለመነው ከክፋቱ ተመልሶ ከመቅሠፍት ይድንም ዘንድ ገሠጸው መከረውም ሰውዬው ግን አልሰማውም።
ይህም አባት ማስተማሩንና መገሠጹን ሰልችቶ አልተወውም ለሌሎች ዕንቅፋት እንዳይሆን ስለዚህ ወደዚያ ሰው ቤት ሔደ የሊቀ ጳጳሳቱንም መምጣት በሰማ ጊዜ ደጁን ዘጋ ይህ አባትም ደጁን እያንኳኳ ሁለት ሰዓት ያህል ቆመ ከዚህም በኋላ የዚህ ሰው ደሙ በራሱ ላይ ነው እኔ ከደሙ ንጹሕ ነኝ ብሎ የእግሩን ትቢያ አራግፎ ተመለሰ። ወዲያዉኑ በዚህ ሰው ላይ ምልክትን ጌታችን ገለጸ ከደንጊያ የተሠራ የቤቱ መድረክ ከሁለት ተከፈለ ይህ ፈጽሞ ድንቅ ነውና ከዚህ አባት ግዝት የተነሣ ጠንካራው ዐለት ተሠነጠቀ ለምለም የነበረ የሰውየው ልብ ግን ከዐለት ጠነከረ።
ዳግመኛም ድንቅ ምልክትን እግዚአብሔር በዚህ ሰው ላይ አደረገ ከድኆች ሁሉ እጅግ የባሰ ድኃ ሆኖአልና ከሹመቱም በጎስቁልናው ሻሩት ከገንዘቡም አንዲት መሐልቅ እንኳ አልቀረለትም ደግሞም ሥጋውን ጭንቅ በሆነ ደዌ ቀሠፈው እጆቹና እግሮቹም ተቆራርጠው በክፉ አሟሟት ሞተ ለሁሉም መቀጣጫ ሆነ ብዙዎች ከኃጢአተኞች ውስጥ ንሰሐ ገቡ።
በዚህም አባት ዘመን ለምስር ንጉሥ የጭፍራ አለቃ የሆነ አንድ ሰው ነበር እርሱም ወደ እስልምና ሕግ የገባ አይሁዳዊ ነው። ለዚህም የጭፍራ አለቃ አይሁዳዊ የሆነ ወዳጅ ነበረው ወደ ንጉሥም አብሮት እየገባ ከንጉሥ ጋር ይነጋገራል ከጭፍራ አለቃው ጋር ወዳጅ ስለሆነ በንጉሥ ዘንድ ባለሟልነትን ባገኘ ጊዜ ንጉሡን እንዲህ አለው ጌታዬ ንጉሥ ሆይ ሊቀ ጳጳሳትን እንድታስመጣውና በፊትህ እንድከራከረው ተመኝቻለሁ። ንጉሡም ልኮ ይህን አባት ሊቀ ጳጳሳት አባ አብርሃምን አስመጣው ከእርሱም ጋር የመቅፉዕ ልጅ የእስሙናይን ኤጲስቆጶስ አባ ሳዊሮስ ነበረ። ይህ አይሁዳዊም ከእሳቸው ጋር በተከራከረ ጊዜ ረትተው አሳፈሩት ንጉሡም ሊቀ ጳጳሳቱንና ከእርሱ ጋር ያሉትን ታላቅ ክብርን አከበራቸው በፍቅር በሰላምም ወደ ቤታቸው አሰናበታቸው።
የጭፍራ አለቃውና ወዳጁ አይሁዳዊም አፈሩ ሊቀ ጳጳሳቱን የክርስቲያን ወገኖችንም የሚወድቁበትን የሚፈልጉ ሆኑ። በአንዲትም ቀን የጭፍራ አለቃው ወደ ንጉሡ ገብቶ ጌታዬ ንጉሥ የማስረዳህ ነገር አለ እሊህ ክርስቲያኖች ሃይማኖት የላቸውም እኮን ወንጌላቸው የስናፍጭ ቅንጣት ታህል ሃይማኖት ካላችሁ ይህን ተራራ ከዚህ ተነቅለህ ወደዚያ ሒድ ብትሉት ይሔዳል የሚሳናችሁ የለም ይላልና አለው።
ንጉሡም ይህን በሰማ ጊዜ ሊቀ ጳጳሳት አባ አብርሃምን ልኮ አስመጣውና ወንጌላችሁ የሰናፍጭ ቅንጣት ታህል ሃይማኖት ካላችሁ ይህን ተራራ ከዚህ ተነቅለህ ወደዚያ ሒድ ብትሉት ይሔዳል ይላል ስለዚህ ነገር ምን ትላላችሁ አለው።
ሊቀ ጳጳሳቱም እውነት ነው የከበረ ወንጌል ይላል አለው ንጉሡም መልሶ እንዲህ አለው እነሆ ይህ ሃይማኖት ያላችሁ እናንተ የብዙ ብዙ ናችሁ ። ከእናንተ ውስጥ ይህን ምልክት የሚገልጥ አንድ ሰው ልታመጣልኝ እሻለሁ አለዚያም ለክርስቲያን ወገኖች ሁሉ አንተ አለቃቸው ነህና ይህን ምልክት ትገልጥ ዘንድ ይገባሃል አለው። ሊቀ ጳጳሳቱም ሰምቶ ደነገጠ እጅግም ፈራ ንጉሡንም እስከ ሦስት ቀን ታገሠኝ አለው ንጉሡም ይሁንልህ አለው ።
ሊቀ ጳጳሳቱም ከንጉሡ ፊት ወጥቶ በአቅራቢያው የሚገኙትን ኤጲስቆጶሳቱን ካህናቱንና መነኰሳቱን ሁሉ ሰበሰባቸው በምስር አገር በመዓልቃ በእመቤታችን በቅድስት ድንግል ማርያም ቤተ ክርስቲያን ውስጥ በእሊህ በሦስቱ ቀኖች እየጾሙና እየጸለዩ በእመቤታችን ሥዕል ፊት ቁመው ወደ እግዚአብሔር ሲማልዱ ቆዩ።
በሦስተኛውም ቀን በሌሊት እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ለሊቀ ጳጳሳቱ በብሩህ ገጽ ተገልጻ እንዲህ አለችው በፊቴ ያፈሰስከውን ዕንባህን ተቀብዬ ስለአንተ ልጄን ለምኜዋለሁና አትፍራ አሁንም የብረት አፈር በአለበት ሜዳ ወደ ገበያ በሚወስደው ጎዳና ተነሥተህ ሒድ አንድ ዓይና የሆነ የውኃ እንስራ የተሸከመ ሰው ታገኛለህ ይህን ምልክት እርሱ ያደርግልሃልና እርሱን ያዘው የዚህም ሰው ስሙ ጫማ ሰፊ ስምዖን ይባላል እርሱም ስለምወደው ልጄ ኢየሱስ ክርስቶስ ትእዛዝ ዓይኑን አውልቆ ጥሏልና።
በዚያንም ጊዜ ሊቀ ጳጰሳቱ ተነሥቶ ፈጥኖ ሔደ ያንንም ሰው አግኝቶ ያዘው የክርስቲያን ወገኖችን እዘንላቸው ራራላቸው አለው አምላክን የወለደች እምቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም እንደተገለጸችለትና እርሱንም እንዳመለከተችው ነገረው። እርሱም ለሊቀ ጳጳሳቱ ሰግዶ አባቴ ሆይ እኔ ኃጥእ በደለኛ ነኝና ይቅርታ አድርግልኝ ይህን የምትለኝን ላደርገው የማልችል ነኝ ነገር ግን የእግዚአብሔር ፈቃድ ይሁን አምላክን በወለደች በእመቤታችን በቅድስት ድንግል ማርያም ፀሎት በአንተም በከበረች ጸሎትህ የክርስቲያንን ወገኖች እንድትረዳቸው ይሁን።
እኔንም ለማንም እንዳትገልጠኝ እለምንሃለሁ እኔ የዚህን ዓለም ክብር መሸከም አልችልምና ነገር ግን የምልህን አድርግ አንተም ንጉሡ ይነሣልኝ በሚልህ ተራራ ትይዩ ከካህናቶችህና ከሕዝብህ ጋር ገብተህ ቁም ወንጌሎችን መስቀሎችን ማዕጠንቶችን የሰም መብራቶችን ያዙ ንጉሡም ከነሠራዊቱ በአንዲት ዳርቻ ይቁም እኔም ማንም እንዳያውቀኝ ከሕዝቡ ተደባልቄ በፊትህ እቆማለሁ አርባ አንድ ጊዜ ኪራላይሶን እያላችሁ በመጮህ ወደ እግዚአብሔር ማልዱ ይኸውም አቤቱ ክርስቶስ ማረን ራራልን ይቅር በለን ማለት ነው።
ከዚህም በኋላ ዝም እንዲሉ ሕዝቡን እዘዛቸው እኔም ያን ጊዜ ስሰግድ አንተ ስገድ እንዲህም ሦስት ጊዜ አድርግ በዚያ ተራራ አንጻር ማሕየዊ በሆነ በመስቀል ምልክት በየስግደትህ አማትብ አለው።
ሊቀ ጳጳሳቱም ይህን ሰምቶ ለወገኖቹ በማሰማት አስገነዘባቸው በዚያም ተራራ በሌላ ገጽ ከሠራዊቱ ጋር ወጥቶ እንዲቆም ለንጉሡ ነገረው ሊቀ ጳጳሳቱም እንደነገራቸው ሁሉም ወጥተው ቆሙ ከዚህም በኋላ ሊጸልዩ ጀመሩ አርባ አንድ ጊዜም አቤቱ ክርስቶስ ማረን አሉ ከዚህም በኋላ ሊቀ ጳጳሳቱ ሦስት ጊዜ ሰገደ ሲነሣም ወደዚያ ተራራ አማተበ በዚያንም ጊዜ ተራራው ከቦታው ተነቅሎ በአየር ላይ ተንሳፈፈ ሊቀ ጳጳሳቱና ሕዝቡም ሲሰግዱ ያ ተራራ ወደ ቦታው ይወርዳል ከሰገዱበትም ሲነሡ ከቦታው ተነቅሎ ወደ አየር ወጥቶ ይንሳፈፋል እንዲህም ሦስት ጊዜ አደረገ።
ሕዝቡም ሁሉ ይህን ድንቅ ሥራ አይተው እጅግ አደነቁ ምስጉን እግዚአብሔርንም አመሰገኑት ሊቀ ጳጳሳት አባ አብርሃምንም ፈሩት ንጉሡም ወደርሱ አስቀርቦ ታላቅ ክብርን አከበረው እንዲህም አለው የምትሻውን ለምነኝ ከእኔም ተመኝ ምንም ምን አልከለክልህም ንጉሡም ሊቀ ጳጳሳቱን ግድ ለምነኝ ባለው ጊዜ አብያተ ክርስቲያናት ልሠራ እሻለሁ ይልቁንም የሰማዕት ቅዱስ መርቆሬዎስን ቤተ ክርስቲያን በምስር ሀገር ልሠራ እሻለሁ አለው እንደወደደም ይሠራ ዘንድ አዘዘለት ከቤተ ምንግሥቱም ብዙ ገንዘቡን አቀረበለት ሊቀ ጳጳሳት አባ አብርሃምም በምድር ላይ እግዚአብሔር ዕድሜህን ያርዝም መንግሥትህንም ያጽና እኔ ገንዘብ አልሻም አለው።
ይህንንም በአለው ጊዜ ንጉሥ አደነቀ የዚህንም ዓለም ገንዘብ በመናቁ እጅግ ወደደው። ከዚህም በኋላ የቅዱስ መርቆሬዎስ ቤተ ክርስቲያን ሥራዋ እስቲፈጸም ሌሎችም በግብፅ አገር የተሠሩ ብዙዎች አብያተ ክርስቲያናት እስቲሠሩ ንጉሡ በፈረስ ተቀምጦ ከሠራዊቱ ጋር በመሔድ ከሊቀ ጳጳሳቱ ጋር አብሮ ለሥራ ይሰለፍ ነበር የሚቃወሙ ክፉዎች ሰዎች የተሠራውንም ያፈርሱ ዘንድ የሚሹ ስለነበሩ ስለዚህ ንጉሥ አጽንቶ አስጠበቀ።
ተጋድሎውንም በፈጸመ ጊዜ እግዚአብሔርንም አገልግሎ በወንጌላዊ ማርቆስ ወንበር ስድስት ዓመት ከስድስት ወር ከኖረ በኋላ በሰላም አረፈ። በዚህም አባት በገድሉ መጽሐፍ ያ ስለ ዕቁባቶቹ ያወገዘው ጸሐፊ በመርዝ ገደለው የሚል አለ።
ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሳን ሰማዕታት አና ጻድቃን ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።

No comments:

Post a Comment

Post Bottom Ad

Pages