ስንክሳር ዘወርኀ ግንቦት 20 - አትሮንስ ሚዲያ - Atrons Media

አትሮንስ ሚዲያ - Atrons Media

ስብኩ ወንጌለ ለኩሉ ፍጥረት ማቴ 16፤15


በቅርብ የተጻፉ

Post Top Ad

Tuesday, June 6, 2023

ስንክሳር ዘወርኀ ግንቦት 20

 አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም

ግንቦት ሃያ በዚህች ቀን የከበረ ጻድቅ የኢትዮጵያ ንጉስ ካሌብ አረፈ፣የሀገረ ቶና የከበረ አባ አሞንዮስ አረፈ፣ ከአባቶች መምህራን ዐሥራ ስድስተኛ የሆነ በደብረ ሊባኖስ አበ ምኔት ሆኖ የተሾመ የከበረ አባት አባ በትረ ወንጌል አረፈ።


ቅዱስ አጼ ካሌብ (መናኙ ንጉሠ ኢትዮጵያ)
ግንቦት ሃያ በዚህች ቀን የከበረ ጻድቅ የኢትዮጵያ ንጉሥ ካሌብ አረፈ። ይህ ቅዱስ እግዚአብሔርን የሚፈራውና በፍጹም ልቡ የሚወደው ሃይማኖቱም የቀና ነው።
በናግራን አገር ያሉ ክርስቲያኖችን አይሁድ እንደሚገድሏቸው በሰማ ጊዜ እጅግ አዘነ መንፈሳዊ ቅናትንም ቀና። ከዚህም በኋላ ተነሣ ወደ ቤተ ክርስቲያንም ገብቶ በመሠዊያው ፊት ቆመ ዐይኖቹንም ወደ ሰማይ አቅንቶ እንዲህ ብሎ ጸለየ ፈጣሪዬ እግዚአብሔር ሆይ የፍጥረት ሁሉ ጌታ የሚታየውንና የማይታየውን የፈጠርህ መላእክት ሁሉ አእላፈ አእላፋት አንተን የሚያመሰግኑህ ለአንተም የሚገዙ ዐይኖቻቸው ብዙ የሆነ ኪሩቤል ክንፎቻቸው ስድስት የሆነ ሱራፌልም ጽኑዕ ክቡር ልዩ ፍጹም አሸናፊ እግዚአብሔር በቅዱሳን የሚመሰገን እያሉ ያለማቋረጥ የሚያመሰግኑህ ፣ ብርሃንን እንደ ልብስ የሚጐናጸፍ የክብር ባለቤት ለሆነ የጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አባቱ እግዚአብሔር ሆይ የአማልክት አምላክ የጌቶች ጌታ የጠፉ በጎችን ይመልሳቸው ዘንድ ልጅህን ይኸውም ቃልህ ነው በፈቃድህ የላክኸው አንተ ነህ።
ተናጋሪ በግ ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ ከአብ ከመንፈስ ቅዱስ ሳትለይ ከሰማይ የወረድክና ስለ እኛ ከእመቤታችን ከቅድስት ድንግል ማርያም ሰው የሆንክ ከጨለማም ከድንቁርናም አውጥተህ ወደ ብርሃን ወደ ሕይወት ወደ ዕውቀት የመራኸን።
አሁንም ከሀዲ ወንጀለኛ ፊንሐስ የቤተ ክርስቲያንን ልጆች እንደ በጎች በማረድ እንደ ገደላቸው በእሳትም አቃጥሎ የወገኖችህንና የርስትህን ልጆች እንዳጠፋቸው እይ። እነሆ አብ ሆይ እኔ አመንሁብህ በአንድ ልጅህም በሕያው ቅዱስ መንፈስህም በመሠዊያህ ክብርም ተማፅኛለሁ በሃይማኖትህም ጸንቼአለሁ እነሆ ስለ አምልኮትህና ስለ ምእመናን ወንድሞቼ ስለ ቀናሁ በአንድ ልጅህ መስቀል ጠላቶችህን ልዋጋቸው እወጣለሁና ከአለኝታዬ እንዳታሳፍረኝ የማያውቁህም አምላካቸው ወዴት ነው እንዳይሉ።
ስለ በደሌና ስለ ኃጢአቴም ጸሎቴን የማትሰማ ልመናዬንም ንቀህ የምትተው ከሆነ በዚሁ ቦታ ብትገድለኝ ይሻለኛል። አቤቱ መሐሪ ይቅር ባይ ርኅሩህ ርስትህ የሆኑ ምእመናንን በከሀድያን ጠላቶችህ እጅ አሳልፈህ አትስጥ። እኛ ወገኖችህና የርስትህ መንጋዎች ስለሆን ለአንተም ምስጋና እናቀርባለን ምስጋና ገንዘብህ ነውና ለዘላለሙ።
ከዚህም በኋላ ንጉሥ ካሌብ ከሀገረ መንግሥቱ ወጥቶ ሔደ የናግራንን ሀገር ያጠፉአት አይሁድን ገደላቸው ብዙ ተአምራትም አድርጎ ስለ አደረገለት ሁሉ እግዚአብሔርን እያመሰገነ ወደ ሀገረ መንግሥቱ በታላቅ ክብር በታላቅም ደስታ ተመለሰ።
ለእግዚአብሔር ምን ዋጋ እከፍለዋለሁ ለጌትነቱና ፍጹም ለሆነ ገናናነቱ መባ አድርጌ ነፍሴንና ሥጋዬን ከማቀርብለት በቀር አለ። ከዚህም በኋላ ይህን ዓለም ንቆ መንግሥቱንም ትቶ ወጣ ደጋጎች መነኰሳት ወደሚኖሩበት ወደ አባ ጰንጠሌዎን በተራራ ላይ ወደ አለ ገዳም እስከ ደረሰ በእግሩ ሔደ። ወደ ዋሻ ውስጥም ገብቶ ሰውም እንዳያየው የዋሻውን በር ዘግቶ በዚያ ውስጥ ኖረ ከዚያችም ወጥቶ ዳግመኛ ዓለምን እንዳያይ ማለ።
ከእርሱ ጋራም ያገባው ዕቃ የለም ከምንጣፍ ከሸክላ ጽዋ ከለበሳት የምንኲስና ልብስ በቀር ምግቡም አምባሻና ጨው የሚጠጣውም ውኃ ነው። የክብር ባለቤት ከሆነ ከእግዚአብሔር ቃል መቃብር መስኮት ላይ ይሰቅልለት ዘንድ የኢየሩሳሌሙን ኤጲስቆጶስ አባ ዮሐንስን እየለመነው ዋጋው ብዙ የሆነ የነገሠበትን ዘውድ ላከ።
ወደ ዋሻውም ከገባ በኋላ ከማንም ጋራ አልተነጋገረም እግዚአብሔርንም ደስ አሰኝቶ በፍቅር አንድነት አረፈ።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
አባ አሞንዮስ
በዚህች ዕለት የሀገረ ቶና የከበረ አባ አሞንዮስ አረፈ። ይህም ቅዱስ ጎልማሳ ሁኖ ሳለ አባ እንጦንዮስ ወደ ምንኩስና ሲጠራው ራእይን አየ። በነቃም ጊዜ ተነሥቶ ወዲያውኑ ወደ አባ ኤስድሮስ ሔደ ከእርሱም አስኬማን ለብሶ እያገለገለውም በእርሱ ዘንድ ኖረ።
ከዚህ በኋላም ወደ ደብረ ቶና ተመልሶ ለራሱ በዓትን ሠራ በታላቅ ገድልም ተጠምዶ በቀንም በሌሊትም ተጋደለ። ሰይጣንም በእርሱ ላይ ቀንቶ በሴት መነኲሲት አምሳል ወደርሱ መጣ የበዓቱን ደጃፍ በአንኳኳ ጊዜ ከፈተለትና ገባ ቅዱሱም ተነሥተን እንጸልይ አለው ያን ጊዜ ተንኰሉን ገለጠ መልኩም እንደ እሳት ላቦት ሆነ ቅዱሱንም እኔ ታላቅ ጦርነት አመጣብሃለሁ አለው።
ከዚህም በኋላ መልኳ ውብ ወደ ሆነ ወደ አንዲት ወጣት ሴት ሰይጣን ሒዶ አነሣሣት። ቅዱስ አሞንዮስን ከእርሷ ጋራ በኃጢአት ልትጥለው ቀጭን ልብሶችን ለብሳ ወደ ርሱ በምሽት ጊዜ ደረሰች።
እንዲህም እያለች ደጃፉን አንኳኳች እኔ መጻተኛ ሴት ነኝ መንገድንም ስቼ በምሽት ጊዜ ከዚህ ደረስኩ አራዊትም እንዳይበሉኝ በውጭ አትተውኝ እግዚአብሔርም ስለ እኔ ደም እንዳይመራመርህ።
በከፈተላትም ጊዜ የሰይጣን ማጥመጃው እንደ ሆነች የላካትም እርሱ እንደሆነ አወቀ በአምላካውያት መጻሕፍት ቃልም ገሠጻት ለኃጥአን ስለ ተዘጋጀ የሲኦል እሳትም አስገነዘባት ሁለተኛም ለጻድቃን ስለ ተዘጋጀ ፍጹም ተድላ ደስታ ነገራት።
ያን ጊዜም የሚላትን ታስተውለው ዘንድ እግዚአብሔር ልቧን ከፈተላት። መልካሙንም ልብስ ከላይዋ አውጥታ ጣለች ከእግሮቹ በታችም ሰገደች ነፍሷንም ያድን ዘንድ በማልቀስ ለመነችው። የጠጉር ልብስም አለበሳት ራስዋንም ተላጭታ በገድል ሁሉ በብዙ ትሩፋትም ተጠመደች በቀንም በሌሊትም ዐሥራ ሁለት ጊዜ የምትጸልይ ሁናለችና በየሁለትና በየሦስት ቀንም ትጾማለች።
ሰይጣንም በአፈረ ጊዜ በመነኲሴ ተመስሎ በየአንዳንዱ ገዳም ሁሉ በመግባት እያለቀሰና እያዘነ እንዲህ አላቸው በአባ አሞንዮስ ቤት ሴት አለችና እርሱ ከታላቅ ገድል በኋላ የአንዲትን ሴት ፍቅር ወዶአልና እርሷም በእርሱ ዘንድ በበዓቱ ውስጥ ትኖራለች እነሆ መነኰሳትን አሳፈራቸው አስኪማውንም አጐሳቈለ።
የመላእክት አምሳል የሆነ ጻድቁ አባ ዕብሎ ያን ጊዜ ተነሣ አባ ዮሴፍንና አባ ቦሂንም ከእሱ ጋራ ወሰዳቸው። ወደ ቅዱስ አሞንዮስ ገዳም ደብረ ቶና ደረሱ ደጃፉንም በአንኳኩ ጊዜ ያቺ ሴት ወደ እሳቸው ወጣች እርስ በእርሳቸውም ያ መነኲሴ የነገረን ዕውነት ነው ተባባሉ።
የከበረ አሞንዮስም ሳድዥ ብሎ ስም አውጥቶላታል ይህም የዋሂት ማለት ነው። ገብተውም ጸሎት አድርገው የእግዚአብሔርንም ገናናነት እየተነጋገሩ እስከ ምሽት ተቀመጡ።
አባ አሞንዮስም አምባሻ እየጋገረችልን ነውና ተነሡ ሳድዥን እንያት አላቸው። በገቡም ጊዜ በሚነድ የእሳት ምድጃ ውስጥ ቆማ እጆቿም ወደ ሰማይ ተዘርግተው ስትጸልይ አገኙዋት። አይተውም ስለዚህ ድንቅ ሥራ እጅግ አደነቁ የተመሰገነ እግዚአብሔርንም አመሰገኑት። ከዚህ በኋላም አቅርባላቸው በሉ።
በዚያቺም ሌሊት መልአክ ስለ አባ አሞንዮስና ስለ ሳድዥ ገድላቸውን ለአባ ዕብሎ ነገረው ወደዚህም ዛሬ ያደረሳችሁ እግዚአብሔር ነው የሳድዥን ዕረፍት እንድታዩ አላቸው።
ሦስት ሰዓትም በሆነ ጊዜ የሚያስጨንቅ የሆድ ዝማ ታመመች በእግዚአብሔርም ፊት አንዲት ስግደትን ሰገደችና በዚያው ነፍሷን ሰጠች መልካም አገናነዝም ገንዘው ቀበሩዋት።
አባ አሞንዮስም ትሩፋቷን ሊነግራቸው ጀመረ እርሷ በእርሱ ዘንድ ዐሥራ ስምንት ዓመት ስትኖር ከቶ ፊቷን ቀና እንዳላደረገች እርሱም ደግሞ ፊቷን እንዳላያት ምግባቸውም አምባሻና ጨው እንደሆነ። ከጥቂት ቀን በኋላም አባ አሞንዮስ በሰላም አረፈ።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
አባ በትረ ወንጌል
በዚችም ቀን ከአባቶች መምህራን ዐሥራ ስድስተኛ የሆነ በደብረ ሊባኖስ አበ ምኔት ሆኖ የተሾመ የከበረ አባት አባ በትረ ወንጌል አረፈ። ይህም ቅዱስ ከታናሽነቱ ጀምሮ እንደ መላእክት ንጽሕናን የለበሰ ትሕትናን ቅንነትን የሚወድ ነበረ።
የምንኵስናንም ልብስ ከለበሰ በኋላ መልካም ገድልን ተጋደለ በክርስቶስ መንጋ ላይም ጠባቂ ሆኖ ተሾመ ከዚያም በኋላ በበጎ እርጅና አረፈ።
ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን።
ምንጭ፡ ስንክሳር ዘወርኀ ግንቦት

No comments:

Post a Comment

Post Bottom Ad

Pages