ስንክሳር ዘወርኀ ሰኔ 20 - አትሮንስ ሚዲያ - Atrons Media

አትሮንስ ሚዲያ - Atrons Media

ስብኩ ወንጌለ ለኩሉ ፍጥረት ማቴ 16፤15


በቅርብ የተጻፉ

Post Top Ad

Tuesday, June 27, 2023

ስንክሳር ዘወርኀ ሰኔ 20

 አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም



ሰኔ ሃያ በዚች ቀን በኬልቄዶን አውራጃ በቂሣርያ አገር የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ቤተ ክርስቲያን በተወደደ ልጅዋ እጅ የታነፀችበት ነው፣ ከገልገላ አውራጃ አለሙት ከምትባል ቦታ የሆነው የሳፋጥ ልጅ ታላቁ ነቢይ ኤልሳዕ አረፈ።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም (ህንጸተ ቤተክርስቲያን)
ሰኔ ሃያ በዚች ቀን በኬልቄዶን አውራጃ በቂሣርያ አገር የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ቤተ ክርስቲያን ያለ ዕንጨት ያለ ጭቃና ውኃ በሦስት ደንጊያዎች በተወደደ ልጅዋ እጅ የታነፀችበት ነው።
ይኽም በዓል ከእመቤታችን 33ቱ በዓላት አንዱ ነው። ‹‹ህንጸተ ቤተ ክርስቲያን›› ይባላል። የመጀመሪያዋ ቤተ ክርስቲያን የታነጸችው በሰኔ 20 ቀን ነው። አናጺውም እራሱ ባለቤቱ መድኃኔዓለም ክርስቶስ ነው፤ ቦታው ፊልጰስዩስ ነው፤ ቤተክርስቲያኗ የተሰየመችው ደግሞ በእመቤታችን ስም ነው። እመቤታችን ካረገች በ4ኛ ዓመት ጳውሎስና ባርናባስ በፊሊጲስዮስ ገብተው አስተምረው ሕዝቡን አሳምነው ካጠመቁ በኋላ ‹‹እንግዲህ ወደ ቤተ ጣዖት አትሂዱ›› አሏቸው። አሕዛብ የነበሩትና አምነው የተጠመቁትም ‹‹የለመድነውን ከከለከላችሁን መካነ ጸሎት ስጡን›› አሏቸው። የከበሩ ሐዋርያትም ወደ ጴጥሮስና ዮሐንስም መልእክት ላኩባቸው። ጴጥሮስና ዮሐንስም ‹‹ያለ ጌታችን ፈቃድ አንዳች ልታደርጉ አይገባምና ጸልዩ እኛም እንጸልያለን›› ብለው መለሱላቸው። ሁሉም ሱባኤ ይዘው በጸሎት ተጉ። ጸሎትና ሱባኤያቸውን ከጨረሱ በኋላ ጌታችን በሞት ያረፉትን አስነሥቶ በሕይወት ያሉትንም ደቀመዛሙርቱን በደመና ጠቅሶ ፊልጵስዩስ ሰበሰባቸው። ጌታችን በኪሩቤል ጀርባ ላይ ሆኖ እልፍ አእላፍ መልአክትን አስከትሎ ይወርዳል እመቤታችን በቀኙ ነበረች። ቅዱስ ዮሐንስም ‹‹ጌታዬ ለምን ሰበሰብከን?›› ብሎ ጠየቀ። ጌታችንም ‹‹በእናቴ ስም ከጽንፍ እስከ ጽንፍ አብያተ ክርስቲያናት እንዲታነጹ ፈቃዴ ነውና ሕንጻ ቤተ ክርስቲያን ላሳያችሁ ሥርዓት ላስተምራችሁ ነው›› አለው። ይህንን ብሎ ወደ ምሥራቅ ወሰዳቸው። በዚያም ተራርቀው የነበሩ 3 ደንጊያዎች ነበሩ። ጌታችንም ሦስቱን ድንጋዮችን በተአምራት አቀራርቦ አንሥቶ ጎተታቸው። ድንጋዮቹም እንደ ሰም ተለጠጡ፣ እንደ ግድግዳም ሆኑ። ቁመቱን ወርዱን መጥኖ ለሐዋርያቱ ሠጣቸው። እነርሱም እሳት እንዳየው ሰም ከእጃቸው እየለመለሙ (እየተሳቡ) ቁመቱን 24 ወርዱን 12 ክንድ አድርገው ሠርተውታል።
ዳግመኛም የብርሃን ምሰሶ ወረደ በሰማያዊቷ ኢየሩሳሌም አምሳያ አድርጎ አነጻት ሁለንተናዋም ተጠናቀቀ። ከዚህም በኋላ ጌታችን ለሐዋርያቱ ‹‹እንግዲህ እናንተም እንዲህ አድርጋችሁ ሥሩ›› ብሏቸው ዐረገ። ሦስቱ ድንጋዮች የሥላሴን ሦስትነት ወደ አንድ ሆነው አንድ ሕንፃ መታጹ የሥላሴን አንድነት ያስረዳል። በአጠቃላይ የቤተ ክርስቲያን መታነጽ ለኛ ለክርስቲያኖች እጅግ ታላቅ በዓልና ደስታ ነው። ስለዚች ቤተ ክርስቲያን አባቶች ደማቸውን አፍሰውላታል፣ አንገታቸውን ለሰይፍ ሰጥተውላታል፣ አጥንታቸውን ከስክሰውላታል፣ ቆዳቸው ተገፏል፣ በድንጋይ ተወግረዋል፣ በእሳት ተቃጥለዋል፣ በአውሬ ተበልተዋል። ቤተ ክርስቲያን ግድግዳዋ ውኃ መሠረቷ ደም ነው። የማትታደስ ነገር ግን ከኃጢአት ከበደል የሚታደሱባት ርትዕት ናት። ይህች ቤተ ክርስቲያን ‹‹የክርስቶስ አካሉና ሙላቱ ናት።›› ኤፌ 1፡13፣ ቆላይ 1፡18፣14። እናም የዚህችን ቤተ ክርስቲያን ሥርዓት መጣስና ትምህርቷን መቆነጻጸል የክርስቶስን አካል ማድማት ነው።
ዳግመኛም በማግሥቱ ሰኔ 21 ቀን ጌታችን ድንግል እናቱን እመቤታችንንና ቅዱሳን መልአክትን አስከትሎ ወረደ። እመቤታችንን መንበር፣ ጴጥሮስን ተራዳኢ ካህን፣ እስጢፋኖስን ሠራዒ ዲያቆን አድርጎ ቀድሶ ለሐዋርያቱ አቁርቧቸዋልና ፍጹም ደስታም ሆነ።
ዳግመኛም ጴጥሮስን እጁን ጭኖ ፓትርያርክ አድርጎ ሾሞታል። በዚህም ጊዜ ሰማያውያን መላእክት ምድራውያን ሐዋርያት አንድ ሆነው አመስግነዋል። ከዚህ በኋላ ሐዋርያት ከጌታችን እንዳዩት በዓለም ዞረው ቤተ ክርስቲያን አንጸዋል። ከዚያ በፊት የነበረው የእነ ሰሎሞን ቤተ መቅደስ፣ የአይሁድ ምኩራብ፣ የአይሁድ ሥርዓተ አምልኮ መፈጸሚያ እንጂ የአዲስ ኪዳን የቁርባንም ሆነ የጥምቀት ሥርዓት መፈጸሚያ አልነበረም። እንኪያስ ‹‹ሐዋርያት የት ነበር ሕዝቡን የሚያጠምቁትና የሚያቆርቡት?›› ከተባለ እንደ ማርቆስ እናት ቤታቸውን ለሐዋርያት በሰጡ ‹‹በየአማኞቹ ቤት›› ይከናወን ነበር።
ሰኔ 20 ቀን ህንጸተ ቤተክርስቲያን (የቤተ ክርስቲያን መታነጽ) ታላቅ በዓል ነው። ቤተ ክርስቲያን እንደ እንግዳ ደራሽ እንደ ውኃ ፈሻሽ የመጣችና ሩቅ ብእሲ የመሠረታት ሳትሆን እራሱ ጌታችን አምላካችን በገዛ ደሙ የመሠረታት ናት። ሐዋ 20፡28። በዕለተ ዐርብ በዕፀ መስቀል ላይ ከጌታችን የፈሰሰው ቅዱስ ደም ቅዱሳን መላእክት በብርሃን ፅዋ ቀድተው በዓለም ሁሉ ረጭተውታል። ስለሆነም የጌታችን ወርቀ ደም በነጠበባቸው ቦታዎች ሁሉ ላይ ዛሬም ድረስ ቤተ ክርስቲያን ይሠራባቸዋል።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
ታላቁ ነቢይ ኤልሳዕ
በዚህችም ዕለት ከገልገላ አውራጃ አለሙት ከምትባል ቦታ የሆነው የሳፋጥ ልጅ ታላቁ ነቢይ ኤልሳዕ አረፈ። የዚህም ነቢይ መጠራቱ እንዲህ ኾነ ኤልያስ አልፎ ሲሔድ የሳፋጥ ልጅ ኤልሳዕን በፊቱ ዐሥራ ሁለት ጥምድ አስጠምዶ ሲያሳርስ አገኘው እርሱም በነዚያ የተሾመ ነበር ኤልያስም ሔዶ መጐናጸፊያውን በላዩ ጣለበት።
ኤልሳዕም ጥማዱን ትቶ ኤልያስን ተከተለው ኤልሳዕም አባቴ እወድሃለሁ አንተንም እከተላሉሁ አለው ኤልያስም ብላቴናዬ አድርጌሃለሁና ተመለስ አለው። እርሱም ኤልያስን ከመከተል ተመለሰ ዐሥራ ሁለቱንም ጥምድ በሬዎች ወስዶ አረደ በላመ ፈጅ ጋኖችም ቀቅሎ ለሕዝቡ አቀረበላቸው እነርሱም በሉ ኤልያስንም ተከትሎት ሔደ ብላቴናውም ሆነ።
ብዙ ዘመናትም ሲያገለግለው ኖረ። ኤልያስም በሚያርግበት ጊዜ ኤልሳዕን ከአንተ ተለይቼ ወደ ሰማይ ሳልወጣ አደርግልህ ዘንድ የምትሻውን ለምነኝ አለው ኤልሳዕም በአንተ ያደረ ሀብተ መንፈስ ቅዱስ እጥፍ ሆኖ ይደርብኝ አለው።
ኤልያስም ኤልሳዕን ድንቅ ነገርን ለመንከኝ ነገር ግን ከአንተ ተለይቼ ወደ ሰማይ ስወጣ ብታየኝ ይደርብህ ከአንተ ተለይቼ ወደ ሰማይ ስወጣ ባታየኝ ግን አይሆንልህም አለው።
ሁለቱም እየተነጋገሩ ሲሔዱ የእሳት ፈረስና የእሳት ሠረገላ መጣ ወደ መካከላቸውም ገብቶ አራራቃቸው ኤልያስም በመነዋወጥና በጥቅል ነፋስ እንደዚህ ወደ ሰማይ ዐረገ። ኤልሳዕም አይቶ የእስራኤል ኃይላቸውና ጽንዓታቸው አባ አባ ብሎ ጮኸ። ከዚህ በኋላም ዳግመኛ አላየውም ልብሶቹንም ከሁለት አድርጎ ከፈላቸው። ኤልያስም ለኤልሳዕ መጠምጠሚያውን ጣለለት በኤልሳዕ ራስ ላይም ወረደ ኤልሳዕም ተመልሶ በዮርዳኖስ ባሕር ዳር ቆመ። በራሱ ላይ የወረደች የኤልያስንም መጠምጠሚያ ይዞ ውኃውን መታባት ውኃውም አልተከፈለም የኤልያስ ፈጣሪ ወዴት ነው ይህስ እንዴት ነው አለ ከዚህ በኋላም ውኃውን መታው ውኃውም ተከፍሎ ወዲያና ወዲህ ቆመ ኤልሳዕም ተሻገረ።
በዚህም ኤልሳዕ የመንፈስ ቅዱስን ሀብት በዕጥፍ እንደተቀበለ ታወቀ። ኤልያስ የወንዙን ውኃ እንድ ጊዜ ከፈለ። ኤልሳዕ ግን ሁለት ጊዜ ከፈለ ኤልያስ አንድ ምውት አስነሣ ኤልሳዕ ግን ሁለት ምውት አስነሣ።
ከዚህም በኋላ ሒዶ ወደ ኢያሪኮ ገባ የዚያች አገር ሰዎችም ጌታችን እነሆ እንደምታያት የዚች አገር ኑሮዋ ያማረ ነው የአገሩ ውኃ ግን ክፉ ነው ሴቶች ሲጠጡት ይመክናሉ አሉት ኤልሳዕም ጨው ጨምራችሁ አዲስ ሸክላ አምጡልኝ አላቸው እነርሱም አመጡለት። ኤልሳዕም ወደ ውኃው ምንጭ ሒዶ ያንን ጨው በውኃው ምንጭ ጨመረው እንዲህም አላቸው እግዚአብሔር እንዲህ ይላል እርሱን ከመጠጣት የተነሣ የሚሞት እንዳይኖር የሚመክንም እንዳይኖር ይህን ውኃ አጣፈጥሁት። ከዚያች ቀን ጀምሮ እስከ ዛሬ ድረስ ኤልሳዕ እንደተናገረ ያ ውኃ ጣፋጭ ሆነ።
ከዚያም አገር ወደ ቤተል ወጣ ሲወጣም ከከተማው ሲወጡ ታናናሽ ልጆችን በጎዳና አገኘ እነርሱም አንተ ራሰ በራ ውጣ ውጣ እያሉ ይዘባበቱበት ጀመር። ወደ ኋላው ተመልሶ በአያቸውም ጊዜ የእግዚአብሔርን ስም ጠርቶ ረገማቸው የዚያን ጊዜ ሁለት ድቦች ከዱር ወጥተው ከእነርሱ አርባ ሁለት ልጆችን ገደሉ።
ከነቢያት ልጆች አንዲት ሴት ነበረች ወደ ኤልሳዕም ጮኸች ባሪያህ ባሌ ሞተ ባሌ እግዚአብሔርን የሚፈራ ሰው እንደ ነበረ አንተ ታውቃለህ ባለዕዳ ሁለቱን ልጆቼን ወስዶ ይገዛቸው ዘንድ መጣ አለችው። ኤልሳዕም አደርግልሽ ዘንድ ምን ትሻለሽ በቤትሽስ ምን አለሽ አላት ዘይት ካለበት ማሰሮ በቀር ለእኔ ለባሪያህ ምንም የለኝም አለችው።
ሔደሽ ከጎረቤትሽ ሁሉ የሸክላ ዕቃና ባዶ ዕቃዎችን ተዋሺ አታሳንሺ። ወደ ቤትሽም ገብተሽ በአንቺና በልጆችሽ ላይ ደጁን ዝጊ በዚያ በሸክላ ዕቃም ዘይቱን ገልብጪው የመላውንም አንሥተሽ አኑሪው አላት። እርሷም ወደ ቤቷ ገብታ በልጆቿና በእሷ ደጃፏን ዘጋች እነርሱ ያቀርቡላት ነበር እርሷም እየቀዳች ትገለብጥ ነበር። ከዚህ በኋላ ልጆቿን ዳግመኛ የሸክላ ዕቃ አቅርቡልኝ አለቻቸው የሸክላ ዕቃ ሁሉ አለቀ የለም አሏት ከዚህ በኋላ ያም ዘይት ተገታ።
እርሷም ሒዳ ለእግዚአብሔር ነቢይ ነገረችው አልሳዕም ሒጂ ይህን ዘይት ሸጠሽ ዕዳሽን ክፈዪ የቀረውን ዘይት ግን የልጆችሽን ሰውነትና ያንቺን ሰውነት አድኚበት አላት።
ከዚህም በኋላ ኤልሳዕ በአንዲቱ ቀን ወደ ሱማን ሔደ በዚያም አገር አንዲት ታላቅ ሴት ነበረች ወደዚያ ከመሔድ ውሎ አድሮ ነበርና እህል ይበላ ዘንድ አቆመችው። ያቺም ሴት ባሏን እነሆ ይህ የእግዚአብሔር ነቢይ ቅዱስ ነው ዘወትር በእኛ ዘንድ እያለፈ ይሔዳል። ትንሽ እልፍኝ እንሥራለት አልጋም እንዘርጋለት መብራት የሚበራበት መቅረዝንና ወንበርን ጠረጴዛንም እናዘጋጅለት ወደ እኛም በመጣ ጊዜ በዚያ ይደር አለችው።
ከዚህም በኋላ በአንዲቱ ቀን ወደዚያ ገብቶ በእልፍኙ አደረ። ደቀ መዝሙሩ ግያዝንም ያቺን የሱማን ሴት ጥራት አለውና ጠራት እርሷም መጥታ በኤልሳዕ ፊት ቆመች። እነሆ ይህን ሁሉ ክብር አከበርሽኝ ምን ላድርግልሽ ከንጉሥ ዘንድ ከአለቃም ዘንድ ቢሆን ጉዳይ እንዳለሽ ንገሪኝ በላት አለው እርሷም እኔስ በወገኖቼ መካከል እኖራለሁ አለችው። ምን ላድርግላት አለ ደቀ መዝሙሩ ግያዝም ልጅ የላትም ባሏም ሽማግሌ ነውና የሚታዘንላት ሴት ናት አለው። ደግሞ ጥራት አለው በጠራትም ጊዜ መጥታ በደጃፍ ቆመች። ኤልሳዕም የዛሬ ዓመት እንደዛሬ ልጅ ትወልጃለሽ አላት እኔን አገልጋይህን ጌታዬ አታሰቅቀኝ አለችው።
ከዚህም በኋላ ያቺ ሴት ፀንሳ ኤልሳዕ በነገራት ቀን በዓመቱ ወንድ ልጅን ወለደች። ያም ልጅ አድጎ ከአባቱ ጋራ ወደ አዝመራው መጣ። አባቱን ራሴን ራሴን አለው የሕፃኑም አባት ብላቴናውን ወደ እናቱ አስገባው አለው። ብላቴናውም ያንን ልጅ ወደ እናቱ አስገባው እናቱም እስከ ቀትር በጉልበቷ ላይ አስተኛችው።
ከዚህም በኋላ በሞተ ጊዜ አውጥታ በእግዚአብሔር ነቢይ ዐልጋ ላይ አስተኛችው ዘግታበትም ወጣች። ባሏንም ጠርታ ወደ እግዚአብሔር ነቢይ እሔዳለሁና አንድ አህያና ከብላቴኖች አንድ ብላቴና ስደድልኝ አለችው። ባሏም መባቻ ያይደለ ቅዳሜ ያይደለ ዛሬ ለምን ትሔጃለሽ አላት እጅ እነሣው ዘንድ እሔዳለሁ አለችው። አህያውንም ጫኑላት አገልጋይዋንም ተነሥ እንሒድ ባልኩህ ጊዜ መሔድን አትከልክለኝ ና ተከተለኝና ወደ እግዚአብሔር ነቢይ ወደ ቀርሜሎስ እንሒድ አለችውና ሔደች።
ኤልሳዕም ያቺን ሴት ስትመጣ በአያት ጊዜ ብላቴናው ግያዝን ያቺ ሴት ሱማናዊቷ ሴት ናት። አሁንም ሩጠህ ሒደህ ተቀበላት ደኅና ነሽን ባልሽስ ደኅና ነውን ልጅሽስ ደኅና ነውን በላት አለው እርሷም ደኅና አለችው። ወደ ኤልሳዕም ዘንድ ወደ ተራራው ደርሳ እግሩን ያዘችው ግያዝም ሊከለክላት መጣ ኤልሳዕም ሰውነቷ አዝናለችና ተዋት እግዚአብሔር ግን ነገሩን ሠውሮኛልና አልነገረኝም አለው። አታሰቅቀኝ ያልኩህ አይደለምን በውኑ እኔ ከአንተ ከጌታዬ ልጅን የለመንኩት መለመን አለን አለችው።
አልሳዕም ግያዝን ወገብህን ታጠቅ በትሬንም በእጅህ ይዘህ ሒድ ሰውም ብታገኝ እንዴትነህ አትበለው እንዴት ነህ ቢልህም አትመልስለት በትሬንም በሕፃኑ ግንባር ላይ አስቀምጣት አለው። የዚያም ሕፃን እናት እንዳልተውህ ሕያው እግዚአብሔርን በረከትህን አለችው ኤልሳዕም ተነሥቶ አብሮአት ሔደ። ግያዝም በፊታቸው ይሔድ ነበር ሩጦም ቀደማቸው በትሩንም በዚያ ልጅ ግንባር ላይ ጣላት ነገር ግን አልሰማውም አልተናገረውም ግያዝም ተመልሶ ኤልሳዕን ተቀብሎ ያ ልጅ አልተነሣም አለው።
ኤልሳዕም ወደ ቤት ገብቶ ሕፃኑን ሙቶ በዐልጋ ላይ ተኝቶ አገኘው በሁለታቸውም ላይ ደጃፉን ዘግቶ ወደ እግዚአብሔር ጸለየ። ወደ ዐልጋውም ላይ ወጥቶ በዚያ ሕፃን ላይ ተኛ አፉን በአፉ ላይ ዐይኖቹን በዐይኖቹ ላይ እጆቹንም በእጆቹ ላይ አድርጎ በላዩ ላይ ተኛ የዚያም ልጅ ሰውነት ሞቀ።
ከዚህ በኋላ ተነሥቶ በቤቱ ውስጥ ወዲያና ወዲህ ተመላለሰ ዳግመኛም ወጥቶ በዚያ ልጅ ላይ ተኛ እስከ ሰባት ጊዜ እንዲህ አደረገ ከዚያም በኋላ ያ ልጅ ዐይኑን ገለጠ ኤልሳዕም ግያዝን ጠርቶ ያቺን ሱማናዊት ሴት ጥራት አለው።
ጠርቷትም ወደርሱ ገባች ኤልሳዕም እነሆ ልጅሽን ውሰጂ አላት እርሷም ከእግሩ ላይ ወድቃ ሰገደችለት ልጅዋንም ይዛ ወጣች። የሶርያ ሰው ንእማንም ወደርሱ በመጣ ጊዜ በዮርዳኖስ ውኃ ከለምጹ አዳነው ንእማንም ብዙ እጅ መንሻ ወርቅና ብር ልብሶችንም አመጣለት ከእርሱም ምንም ምን አልወሰደም።
ደቀ መዝሙሩ ግያዝም ተደፋፍሮ ንእማንን ተከተለው ምክንያትም ፈጥሮ ንእማንን እንዲህ አለው ከኤፍሬም አገር ከነቢያት ልጆች ሁለት ሰዎች መጥተውብኛልና አንድ መክሊት ብርና ሁለት ልብሶች ስጣቸው ብሎሃል አለው ንእማንም ሁለት መክሊቶችንና ሁለት ልብሶችን ሰጠው።
ኤልሳዕም ግያዝ ያደረገውን አውቆ ረገመው የንእማንም ለምጽ ገንዘብ ወዳጅ በሆነው በግያዝ ላይ ተመለሰ። በሰማርያም ረኃብ ጸና ከሶርያ ሰዎች የተነሳ የአህያ መንጋጋ በአምሳ ወቄት ብር እስቲለወጥ ድረስ ኵስሐ ርግብም የድርጎ አራተኛ በአምስት ብር እስቲሸመት ድረስ በሀገራቸው የሶርያ ሰዎች ሰፍረው ተቀመጡ። በዚህ ነቢይ ጸሎትም በአንዲት ቀን ረኃቡ ተለወጠ ጥጋብም ሆነ። በዘመኑም ብዙ ድንቆችና ተአምራቶችን አደረገ በሞተም ጊዜ በመቃብር ውስጥ አኖሩት በዚያም ወራት የሞአብ ሰዎች አገራቸውን ከበቡ። ይቀብሩም ዘንድ ሌላ ሰውን አመጡ አደጋ ጣዮችንም በአዩ ጊዜ የዚያን ሰው ሬሳ በኤልሳዕ መቃብር ላይ ጣሉት የዚያም ሰው ሬሳ በኤልሳዕ ዐፅም ላይ ወረደ የኤልሳዕንም ዐፅም በነካው ጊዜ ያ በድን ድኖ በእግሮቹ ቆመ።
ይህም ነቢይ በአራት ነገሥታት ዘመን ትንቢት ተናገረ እሊህም ኢዮራም፣ አካዝያስ፣ ኢዩና፣ ዮአስ ናቸው የትንቢቱም ዘመን ከሀምሳ ዓመት በላይ ነው። ክብር ይግባውና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወደ ዓለም ከመምጣቱ አስቀድሞ ትንቢት ተናገረ ከዚህ በኋላም በሰለም አረፈ።
ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን፤ ልመናዋ በረከቷም ወንዶችና ሴቶች ባሮቿ ከሆን ከሁላችን የክርስቲያን ወገኖች ጋራ ይኑር፣ በቅዱሰኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን።
ስንክሳር ዘወርኀ ሰኔ

No comments:

Post a Comment

Post Bottom Ad

Pages