ስንክሳር ዘወርኀ ነሐሴ 14 - አትሮንስ ሚዲያ - Atrons Media

አትሮንስ ሚዲያ - Atrons Media

ስብኩ ወንጌለ ለኩሉ ፍጥረት ማቴ 16፤15


በቅርብ የተጻፉ

Post Top Ad

Thursday, February 22, 2024

ስንክሳር ዘወርኀ ነሐሴ 14

 በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን።



ቅዱስ ዕፀ መስቀል
የዕፀዋት ሁሉ ንጉሣቸው የሚሆን ቅዱስ ዕፀ መስቀል ለእኛም ኃይላችን: ቤዛችን: መዳኛችን: የድል ምልክታችን ነው:: መስቀል በደመ ክርስቶስ ተቀድሷልና አንክሮ: ስግደት ክብርና ምስጋና በጸጋ ይገባዋል::
ቅዱስ መስቀለ ክርስቶስ ላለፉት ሁለት ሺ ዓመታት ብዙ ተአምራትን ሠርቷል:: ከእነዚህ መካከልም አንዱን በዚህ ዕለት እናዘክራለን::
ታሪኩ: ምሥጢሩስ እንደ ምን ነው ቢሉ:-
በ400 ዓ/ም አካባቢ በግብፅ አባ ቴዎፍሎስ ፓትርያርክ ሳለ: ቅዱስ ቄርሎስም በሊቀ ዲቁና ሲያገለግል ሳለ በእስክንድርያ ከተማ ሁለት ደሃ ክርስቲያኖች ይኖሩ ነበር:: የቀን ሠራተኞች በመሆናቸው ከዕለት ምግብ አይተርፋቸውም ነበር::
ከሁለቱ አንዱ ፍጹም አማኝ ሲሆን ሌላኛው ግን ተጠራጣሪ ነበር:: ስለ ምን ነው ቢሉ:- በከተማዋ ብዙ ሃብታም አይሁድ ነበሩና እነሱን እየተመለከተ ነው:: ለእርሱ ክርስትና ማለት ገንዘብ መስሎታልና ዘወትር "ለምን ክርስቶስን እያመለክን ድሃ እንሆናለን?" እያለ ያማርር ነበር::
"ያዛቆነ ሰይጣን . . . " እንደሚባለው አንድ ቀን ባልጀራውን "ለምን ክርስቶስን አንክደውም? (ሎቱ ስብሐት!) እርሱን ከማምለክ የተረፈን ድህነት ብቻ ነው" አለው:: ባልንጀራው ሊመክረው ሞከረ:: "እግዚአብሔር አምላከ-ነዳያን ነው:: ቅዱሳን ነቢያት: ሐዋርያት: ጻድቃን: ሰማዕታትም በሥጋዊ ሃብት ነዳያን ነበሩ::" ብሎ ቢለውም ሰይጣን ሠልጥኖበታልና አልሰማውም::
ያ ስሑት ደሃ ወዲያው ወጥቶ ወደ ማኅበረ አይሁድ ሔደ:: እነርሱ በቁጥር ብዙ ሁነው በአንድነት ይኖሩ ነበር:: "ሥራ ቅጠሩኝ" አላቸው:: "በእምነት አትመስለንምና አይሆንም" አሉት:: ያን ጊዜ ለአለቃቸው (ፈለስኪኖስ) "አንተ ሥራ ቅጠረኝ እንጂ እኔ ክርስቶስን እክዳለሁ::" (ሎቱ ስብሐት!) አለው::
ወዲያው የከተማው ሕዝብ ተጠርቶ: በጉባኤ መካከል ሊያስክዱት ተዘጋጁ:: በፍጥነትም መስቀል: ጦር: ሐሞት አዘጋጁ:: ሥዕለ ስቅለቱንም አመጡ:: ያን ደሃ ከሃዲም "በል-ክርስቶስ ሆይ! ካድኩህ ብለህ ምራቅህን ትፋበት: ሐሞቱን አፍስበት: በጦርም ውጋው::" (ሎቱ ስብሐት!) አሉት::
ያ ልቡ የደነቆረ መስቀለ ክርስቶስ ላይ ተፋ:: ሐሞትም አፈሰሰበት:: በመጨረሻ በጦር ሲወጋው ግን ድንቅ ተአምር ተገለጠ:: በጦር ከተወጋው ከመስቀሉ ጐን ብዙ ደም ፈሰሰ:: ለረዥም ሰዓትም አላቋረጠም:: በዚህች ሰዓት በአካባቢው የነበሩ ሁሉም አይሁድ በግንባራቸው ተደፍተው ለክርስቶስና ቅዱስ መስቀሉ ሰገዱ::
ሁሉም በአንድነት "ክርስቶስ የአብርሃም አምላክ ነው:: መድኃኒትም ነው::" ሲሉ እየጮሁ ተናገሩ:: ባለማወቅ ስላደረጉት እነርሱ ምሕረትን ሲያገኙ ያ አዕምሮ የጐደለውን ደሃ ግን ዘወር ብለው ሲያዩት ወደ ድንጋይነት ተቀይሮ ነበር:: ነፍሱንም: ሥጋውንም በፈቃዱ አጠፋ::
የአይሁድ አለቃም ዓይነ ሥውር ዘመድ ነበረውና ወዲያው አምጥቶ ከደሙ ቢቀባው ዐይኑ በራ:: ታላቅ ደስታም በዚያ ሥፍራ ተደረገ:: ነገሩን የሰሙት ቅዱሳን ቴዎፍሎስ እና ቄርሎስ ሲመጡ ደሙ ከመፍሰስ አላቆመም ነበር::
በተአምሩ ደስ ተሰኝተው: ከደመ ክርስቶስ ለበረከት ተቀቡ:: የፈሰሰውን ቅዱስ ደም ከነአፈሩ አንስተው: መስቀሉን በትከሻ ተሸክመው: በፍፁም እልልታና ዝማሬ ወስደው በቤተ መቅደስ አኑረውታል:: የከተማዋ ሁሉም አይሁድም በክርስቶስ አምነው ተጠምቀዋል::
ቅዱሳን ስምዖንና ዮሐንስ
በቤተ ክርስቲያን ታሪክ አስደናቂ ታሪክ ካላቸው ጻድቃን እነዚህ ሁለቱ ቅድሚያውን ይይዛሉ::
እርሱስ እንደ ምን ነው ቢሉ:-
ቅዱሳኑ በ5ኛው መቶ ክ/ዘመን ሶርያ አካባቢ ተወልደው ያደጉ ክርስቲያኖች ናቸው::
ዘመዳሞች ከመሆናቸው ባሻገር አብረው ስላደጉ እጅጉን ይፋቀሩ ነበር:: የዋሃንም ነበሩ:: ወጣት በሆኑ ጊዜ ትልቁ ዮሐንስ ሚስት አገባ:: ታዲያ አንድ ቀን ከጌታችን መቃብር ኢየሩሳሌም ደርሰው ሲመለሱ ገዳመ ዮርዳኖስ አካባቢ ደረሱ:: እርስ በእርሳቸውም "ይህ ገዳምኮ የመላእክት ማደሪያ ነው::" ተባባሉ::
በዚያውም መንነው ለመቅረት አሰቡ:: ፈረስና ንብረታቸውን ለዘመዶቻቸው ልከው ጸሎት አደረሱ:: ፈቃደ እግዚአብሔርን ሊረዱም ዕጣ ተጣጣሉ:: ዕጣውም "ወደ ገዳም ሒዱ" የሚል ስለሆነ ተቃቅፈው ደስ አላቸው::
ወደ ገዳሙ ሲደርሱም አበ ምኔቱ አባ ኒቅዮስ ፈጣሪ አዞት የገዳሙን በር ከፍቶ ጠበቃቸው:: ተቀብሎ ሲያስገባቸውም አንድ ደግ መነኮስ ሲያልፍ: ቆቡ ቦግ ቦግ እያለ እንደ ፋና ሲያበራ እና መላእክት ከበውት አዩ:: ወዲያውም አበ ምኔቱን "እባክህ አመንኩሰን" አሉት::
እርሱም የአምላክ ፈቃድ ነውና በማግስቱ አመነኮሳቸው:: ፍቅረ ክርስቶስ ገዝቷቸዋልና በጥቂት ዓመታት ተጋድሎ ከብቃት (ከጸጋ) ደረሱ:: ሁለቱም ቆመው በፍቅር ሲጸልዩ የብርሃን አክሊል በራሳቸው ላይ ይወርድ ነበር:: አካላቸውም በሌሊት ያበራ ነበር::
እንዲህ ባለ ቅድስና ለዓመታት ቆይተው ከገዳሙ ወደ ጽኑ በርሃ ሊሔዱ ስለ ፈለጉ የገዳሙ በር በራሱ ተከፈተ:: አበ ምኔቱ አባ ኒቆን (ኒቅዮስ) እያነባ በጸሎት ሸኛቸው:: በበርሃም በጠባቡ መንገድ: በቅድስና ተጠምደው ለሃያ ዘጠኝ ዓመታት ተጋደሉ:: በዚህ ሰዓት ግን ሁለቱን የሚለያይ ምክንያት ተፈጠረ::
እግዚአብሔር ቅዱስ ስምዖን ወደ ከተማ እንዲገባ: ቅዱስ ዮሐንስ ግን በዚያው እንዲቆይ አዘዘ:: ሁለቱ ለረዥም ሰዓት ተቃቅፈው ተላቅሰው ተለያዩ:: ከሃምሳ ዓመታት በላይ ተለያይተው አያውቁም ነበርና::
ቅዱስ ስምዖን ወደ ከተማ ሲገባ ክብሩን ይደብቅ ዘንድ እንደ እብድ ሆነ:: በዚህ ምክንያትም የወቅቱ ከተሜዎች ይንቁት: በጥፊም ይመቱት ነበር:: (እባካችሁ ብዙ በየመንገዱ የወደቁ አባቶች አሉና እንጠንቀቅ!) ቅዱሱ ግን ስለ እነርሱ ይጸልይ ነበር::
በከተማዋ የነበሩ እብዶችን ሁሉንም በተአምራት ፈወሳቸው:: አንድ ቀን ግን ክርስቲያን ነን የሚሉ ሰዎች ደብድበውት ደከመ:: የእግዚእብሔር መልአክ ወርዶ "ና ልውሰድህ" ብሎ ዮሐንስን ከበርሃ: ስምዖንን ከከተማ በዚህች ቀን ወሰዳቸው:: እነሆ ብርሃናቸው ዛሬም ድረስ ለሚያምንበት ሁሉ ያበራል::
ቅዱስ ባስሊቆስ ሰማዕት
በመጀመሪያው ምዕተ ዓመት ከነበሩ ስመ ጥር ሰማዕታት አንዱ ቅዱስ ባስሊቆስ ነው:: ብዙ ጊዜ "ኃያሉ ሰማዕት" በመባልም ይጠራል:: ስለ ፍቅረ ክርስቶስ በመከራ በቆየባቸው ዘመናት ሁሉ ከማመስገን በቀር ምግብ አይቀምስም ነበር::
"ለምን አትበላም?" ሲሉት "እኔ የአምላኬ ስሙና ፍቅሩ አጥግቦኛል::" ይላቸውም ነበር:: አሥረው በግድ ለጣዖት ሊያሰግዱት ወደ ቤተ ጣዖት ቢያስገቡት በጸሎቱ እሳት ከሰማይ ወርዳ አማልክቶቻቸውን በልታለች:: ተበሳጭተው ለቀናት የደረቀ ባላ ላይ አንጠልጥለው ቢገርፉት ደሙ ፈሰሰ::
የታሠረባት ደረቅ እንጨት ግን ለምልማ: አብባ: አፍርታ በርካቶች ተደንቀዋል:: ከበረከቱም ተሳትፈዋል:: ኃያል ሰማዕት ቅዱስ ባስሊቆስ በዚህች ቀን ተከልሎ ጌታችንና መላእክቱ ወርደው ሲያሳርጉት ብዙ ሰው አይቶ አምኗል::
አምላከ ቅዱሳን ከፍቅረ መስቀሉ አድሎ: በኃይለ መስቀሉ ይጠብቀን:: የወዳጆቹን ጸጋ ክብርም ያድለን::

ነሐሴ 14 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት
1.ቅዱስ መስቀለ ክርስቶስ
2.ጻድቃን ቅዱሳን (አባ ስምዖንና አባ ዮሐንስ)
3.ቅዱስ ባስሊቆስ (ኃያል ሰማዕት)
4.ቅዱስ ድምጥያና ደቀ መዛሙርቱ (ሰማዕታት)
ወርኀዊ በዓላት
1.አቡነ አረጋዊ (ዘሚካኤል)
2.ቅዱስ ገብረ ክርስቶስ መርዓዊ
3.ቅዱስ ፊልጶስ ሐዋርያ
4.ቅዱስ ሙሴ (የእግዚአብሔር ሰው)
5.አባ ዮሐንስ ጻድቅ
6.እናታችን ቅድስት ነሣሒት
"የመስቀሉ ቃል ለሚጠፉት ሞኝነት ለእኛ ለምንድን ግን የእግዚአብሔር ኃይል ነውና . . . መቼም አይሁድ ምልክትን ይለምናሉ:: የግሪክ ሰዎችም ጥበብን ይሻሉ:: እኛ ግን የተሰቀለውን ክርስቶስን እንሰብካለን::"
(፩ቆሮ. ፩፥፲፰-፳፫)
ወስብሐት ለእግዚአብሔር
ስንክሳር ዘወርኀ ነሐሴ

No comments:

Post a Comment

Post Bottom Ad

Pages