ስንክሳር ዘወርኀ ነሐሴ 26 - አትሮንስ ሚዲያ - Atrons Media

አትሮንስ ሚዲያ - Atrons Media

ስብኩ ወንጌለ ለኩሉ ፍጥረት ማቴ 16፤15


በቅርብ የተጻፉ

Post Top Ad

Friday, February 23, 2024

ስንክሳር ዘወርኀ ነሐሴ 26

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን።

ነሐሴ ሃያ ስድስት በዚህች ቀን ለአብርሃም ሚስት ለተመሰገነች ቅድስት ሣራ መታሰቢያዋ ነው፣ የከበረ አባ ሞይስስና እህቱ ሣራ በሰማዕትነት ሞቱ፣ የከበሩ መነኰሳት ቅዱሳን አጋቦስና ቴክላ በሰማዕትነት ሞቱ፣ የከበሩ አባቶቻችን አቡነ ኢየሱስ ሞዐ እና አቡነ ሃብተ ማርያም የተፀነሱበት ዕለት ነው፡፡

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
ቅድስት ሣራ
ነሐሴ ሃያ ስድስት በዚህች ቀን ለአብርሃም ሚስት ለተመሰገነች ሣራ መታሰቢያዋን እናደርግ ዘንድ የቤተ ክርስቲያን መምህራን አባቶች አዘዙ።
ይቺንም ክብርተ ማሕፀን የሆነች ጡቶቿም የተባረኩ ክብርት ሣራን የጌራራ ንጉሥ አቤሜሌክ ባል እንዳላት ሳያውቅ በወሰዳት ጊዜ እንዳይቀርባት እግዚአብሔር ገሠጸው በደዌም ቀሠፈው ባሏ አብርሃምም በጸለየለት ጊዜ ከደዌው ተፈወሰ ከዚህም በኋላ ከብዙ ገንዘብ ጋራ ወደ ባሏ መለሳት።
ከዚህም በኋላ እግዚአብሔር በሦስትነቱ ተገልጦ ወደ ቤቷ እንግድነት በመጣ ጊዜ ለአብርሃምም የይስሐቅን መወለድ በነገረው ጊዜ ሣራም በድንኳኑ ውስጥ ሳቀች እንዲህ ስትል እስከ ዛሬ ገና ነኝን ጌታዬም አርጅቷል።
እግዚአብሔርም አብርሃምን እንዲህ አለው ሣራን ለብቻዋ ምን አሳቃት እስከ ዛሬ ገና ነኝን ጌታዬም አርጅቷል እኔም አሁን አርጅቻለሁ ብላ በውኑ ለእግዚአብሔር የሚሳነው ነገር አለን። ከዚህም በኋላ ሣራ ፀንሳ እግዚአብሔር ባለው ወራት በርጅናዋ ለአብርሃም ወንድ ልጅን ወለደች።
ይስሐቅም በአደገ ጊዜ ልጅዋ ይስሐቅን ከእስማኤል ጋራ ሲጫወት አየችው። አብርሃምንም ሣራ እንዲህ አለችው ይቺን ባሪያ ከነልጅዋ አባራት የባሪያ ልጅ ከልጄ ከይስሐቅ ጋራ አይወርስምና። ይህም ነገር ለአብርሃም ስለ ልጁ እስማኤል እጅግ ጭንቅ ሆነበት።
እግዚአብሔርም አብርሃምን እንዲህ አለው የዚህ ልጅ የዚችም ባሪያ ነገር በፊትህ ጭንቅ አይሁንብህ የምትልህን ሁሉ ሣራን ስማት ከይስሐቅ ዘር ይተካልሃልና።
ይህም ነገር ታላቅ ምሥጢር አለው የተመሰገነ ጳውሎስ ቅድስት ሣራን የቤተ ክርስቲያን ምሳሌ አድርጓታልና። ከዚህም በኋላ በበጎ እርጅና በአረፈች ጊዜ ከኬጢያዊ ኤሞር ልጆች በገዛው ቦታ ቀበራት።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
ቅዱሳን ሞይሥና እህቱ ሣራ
በዚህች ቀን የከበረ አባ ሞይስስና እኅቱ ሣራ በሰማዕትነት ሞቱ።
የእሊህም ቅዱሳን ወላጆቻቸው ደጎች እጅግም ባለጸጎች ናቸው። የከበረ ሞይስስ ወላጆቹ ከአረፉ በኋላ እኅቱ ሣራን ሊአጋባትና ወላጆቹ የተዉትን ገንዘብም ሊሰጣት እርሱም ወደ ገዳም ሒዶ ሊመነኵስ አሰበ።
ይህን አሳቡንም በነገራት ጊዜ እንዲህ ብላ መለሰችለት እኔን ልታጋባኝ ከወደድክ አስቀድሞ አንተ አግባ አርሱም እንዲህ አላት እኔ ብዙ ኃጢአት ሠርቻለሁ ስለዚህ ኃጢአቴን ለመደምሰስ እመነኵስ ዘንድ እሻለሁ ማግባት አይቻለኝም የነፍሴን መዳኛ አስባለሁ እንጂ ።
ሁለተኛም እንዲህ ብላ መለሰችለት አንተ ነፍስህን ስታድን እኔን በዓለም ወጥመድ ውስጥ እንዴት ትጥለኛለህ። እርሱም እንዲህ አላት ምንኵስና ከፈለግሽ ስለ ራስሽ የምታውቂ አንቺ ነሽ እኔም የወደድሺውን አደርግልሻለሁ።
እንዲህም አለችው ለነፍስህ የምታደርገውን ለኔም እንዲሁ አድርግ እኛ ሁለታችን ከአንድ ባሕርይ ከአንድ አባት ከአንዲት እናት የተገኘን ነንና የልቧንም ቆራጥነት አይቶ ወዲያውኑ ከእርሷ ጋራ ተነሣ ገንዘባቸውንም ሁሉ ለድኆችና ለምስኪኖች በተኑ።
ከዚህም በኋላ እኅቱ ሣራን ወሰዳት ከእስክንድርያ ከተማ ውጭ ወዳለ የደናግል ገዳም ውስጥ አስገባት እርሱም ከወንዶች ገዳም ገብቶ በዚያ ተጋድሎን ተጋደለ። እንዲሁ እኅቱም ጽኑዕ በሆነ ገድል ተጠምዳ እየተጋደለች ሁለቱም ሳይገናኙ ዐሥር ዓመት ኖሩ።
በሊቀ ጳጳሳት አባ ድሜጥሮስ የሹመት ዘመን ሳዊርያኖስ የሚባል ከሀዲ ተነሥቶ የክርስቲያንን ወገኖች ማሠቃየት ጀመረ። ከመነኰሳት ገዳማትም ብዙዎች በሰማዕትነት ሞቱ። አባ ሞይስስም ተነሣ ሊሰናበታትም ወደ እኅቱ ሣራ ላከ በሰማዕትነት መሞት እንደሚሻም ነገራት።
ሣራ እኅቱም በሰማች ጊዜ ወዲያውኑ ተነሣች ሒዳ በሰማዕትነት ትሞት ዘንድ እንድታሰናብታት እመ ምኔቷን ለመነቻት እመ ምኔቷም ጸለየለችላት ሰላምታም ሰጥታ አሰናበተቻት እርሷም ደናግሉን ሁሉ ተሰናበተቻቸው።
ከዚህም በኋላ ወደ ወንድሟ ሔደች በጐዳናም አገኘችውና እርስ በርሳቸው ሰላም ተባባሉ ወደ እስክንድርያ ከተማም ገብተው በመኰንኑ ፊት ቁመው በክብር ባለቤት በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ታመኑ መኰንኑም ጽኑዕ ሥቃይን አሠቃያቸው ከዚህም በኋላ ራሳቸውን በሰይፍ አስቆረጠ። በመንግሥተ ሰማያትም የሰማዕትነት አክሊልን ተቀበሉ።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
መነኮሳት አጋቦስና እህቱ ቅድስት ቴክላ
በዚህችም ቀን የከበሩ መነኰሳት አጋቦስና ቴክላ በሰማዕትነት ሞቱ። እሊህም ቅዱሳን በከሀዲው ሉልያኖስ ዘመን መከራ በመቀበል ተጋደሉ ። ከመኳንንቶቹም አንዱ ጽኑዕ ሥቃይን አሠቃያቸው ። ሥቃያቸውም በአሰለቸው ጊዜ ለአንበሶች ጣላቸውና ገድላቸውን ፈጽመው የሰማዕትነት አክሊልን ተቀበሉ።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
አቡነ ኢየሱስ ሞዐ
በዚህች ቀን አባታቻን አቡነ ኢየሱስ ሞዐ የተፀነሱበት ዕለት ነው፡፡ ቅዱሱ አባት ሀገራቸው ጎንደር ክፍለ ሀገር ስማዳ ወረዳ ሲና ዳኅና በሚባል ቦታ ነሐሴ 26 ቀን ተፀንሰው ግንቦት 26 ቀን 1210 ዓ.ም ከአባታቸው ዘክርስቶስና ከእናታቸው እግዚእ ክብራ ተወለዱ። የተወለዱትም በቅዱስ ነአኲቶ ለአብ ዘመነ መንግስት ነው፡፡ አቡነ ኢየሱስ ሞዐ የአቡነ ተክለ ሃይማኖት የቆብ አባት ሲሆኑ ታላቁን ሐይቅ ቅዱስ እስጢፋኖስን ገዳም የቆረቆሩ ደገኛ አባት ናቸው፡፡
ዕድሜያቸው 30 ዓመት እስከሚደርስ ድረስ ከቤተሰቦቻቸው ትምህርተ ሃይማኖትንና ግብረ ገብን ሲማሩ ከቆዩ በኋላ በ1240 ዓ.ም ይህንን ዓለም በመተው ወደ ደብረ ዳሞ ገዳም ገቡ፡፡ በደብረ ዳሞ ገዳም መነኰሳቱን እየረዱ፣ የቤተ ክርስቲያንን ትምህርት እያጠኑ፣ ቅዱሳት መጻሕፍትን እየገለበጡ ለሰባት ዓመታት ከቆዩ በኋላ የደብረ ዳሞ 3ኛ አበ ምኔት ከሆኑት ከአባ ዮሐኒ እጅ ምንኩስናን በ1247 ዓ.ም ተቀበሉ፡፡
አንድ ቀን ሌሊት መልአኩ ቅዱስ ገብርኤል ወደርሳቸው መጥቶ ‹‹የስምህ መክበርያ ወደሆነው ሐይቅ ወደ ተባለው ሥፍራ ሂድ›› አላቸው፡፡ አባታችንም ‹‹ቦታውን እንዴት ዐውቀዋለሁ?›› በማለት መልአኩን ቢጠይቁት ‹‹ተነሥ! ጉዞህን ጀምር ቦታውን እኔ አሳይሃለሁ›› አላቸው፡፡ አባ ኢየሱስ ሞዓ በመልአኩ እንደታዘዙት ከበዓታቸው ተነሥተው ተከተሉት፡፡ የብዙ ወራት መንገድ የሆነውን ጐዳናም በስድስት ሰዓት አደረሳቸው፡፡ በዚያን ወቅት ከሐይቅ ገዳም በስተ ሰሜን ወደነበረው ጴጥሮስ ወጳውሎስ ቤተ ክርስቲያን ደረሱ፡፡ ወደ ሐይቅ እስጢፋኖስ ከመግባታቸው በፊት ለ6 ወራት ያህል በጴጥሮስ ወጳውሎስ ቤተ ክርስቲያን አገልግለዋል፡፡ ያገለግሉበት በነበረው ቤተ ክርስቲያን ቀን ቀን ሕዝቡን ሲያስተምሩ በመዋል ሲመሽ ወደ ሐይቁ በመግባት ሲጸልዩ ያድሩ ነበር፡፡ በሐይቅ እስጢፋኖስና በዙርያው ለነበሩ አበውም ማታ ማታ አንድ ብርሃን ወደ ሐይቁ ሲገባ ጠዋት ጠዋትም ሲወጣ ይታያቸው ነበር፡፡ ከዚህም በኋላ አባታችን በገዳሙ አባቶች ልመናና በልዑል እግዚአብሔር ትዕዛዝ ወደ ሐይቅ ገዳም ገብተው አበምኔት ሆኑ፡፡
ሐይቅ እስጢፋኖስ ገዳም ከደሴ 30 ኪሎ ሜትር ርቆ የሚገኝ ሲሆን የመሠረቱት ካልዕ ሰላማ የተባሉ ግብፃዊ ጻድቅ ናቸው፡፡ ሐይቅን አባ ሰላማ ካልዕና ዐጼ ድል ነአድ በ862 ዓ.ም ነው የቆረቆሩት። ገዳሙን ካቀኑት በኋላ ‹‹የማንን ታቦት እናስገባ?›› ብለው ሲያስቡ ቶራ የምትባል እንስሳ ጭነት ተጭና ከመካከላቸው ተገኘች፤ ጭነቱን አውርደው ቢያዩት በሐር ጨርቅ የተጠቀለለ የቅዱስ እስጢፋኖስንና የቅዱስ ጊዮርጊስን ሁለት ታቦት አገኙ፡፡ በላዩም ላይ ‹‹ይህንን ታቦት በኢየሩሳሌም የሚኖሩ የተሰወሩ ቅዱሳን ከእግዚአብሔር ታዘው የላኩት ነው›› የሚል ጽሑፍ አገኙ፡፡
ይህ ከሆነ ከ400 ዘመን በኋላ ነው አቡነ ኢየሱስ ሞዐ ወደዚህ ቦታ የመጡት፡፡ አቡነ ኢየሱስ ሞዐ ለ52 ዓመት ቀን ቀን መንፈሳዊ ሥራቸውን እየሠሩ ሌሊት ሌሊት ሐይቁ ውስጥ ቆመው ሲጸልዩ ያድራሉ፡፡ አባ ኢየሱስ ሞዐ በሐይቅ እስጢፋኖስ በአበ ምኔትነት በቆዩባቸው 45 ዓመታት ከየገዳማቱ ቅዱሳን መጻሕፍትን በመገልበጥና በማሰባሰብ የመጀመርያው ዘመናዊ የቤተ ክርስቲያን ቤተ መጻሕፍት በሐይቅ እስጢፋኖስ ገዳም እንዲቋቋም አድርገዋል፡፡ በዚሁ ገዳም ውስጥ የመጀመርያውን የቤተ ክርስቲያን ቋሚ ትምህርት ቤት በማቋቋም 800 መነኮሳትን በትምህርተ ሃይማኖት አሠልጥነው በንቡረ ዕድነት ማዕረግ ሾመው በመላ ሀገራችን እንዲሠማሩ አድርገዋቸዋል፡፡
ከእነዚህም ተማሪዎቻቸው መካከል አቡነ ተክለ ሃይማኖት (ደብረ ሊባኖስ)፣ አቡነ ኂሩተ አምላክ (ጣና ሐይቅ ዳጋ እስጢፋኖስ)፣ አቡነ ጊዮርጊስ ዘጋሥጫ (ቦረና)፣ አባ በጸሎተ ሚካኤል (ቦረና)፣ አቡነ ገብረ እንድርያስ (ቦረና)፣ አቡነ ሕዝቅያስ (ቦረና)፣ አቡነ እስትንፋሰ ክርስቶስ (ዳውንት)፣ አቡነ አሮን (መቄት- ጣራው ክፍት የሆነው)፣ አቡነ ተክለ ኢየሱስ ሞዐ (ሐይቅ)፣ አቡነ አላኒቆስ (ትግራይ)፣ አቡነ በግዑ (ሐይቅ)፣ አቡነ ሠረቀ ብርሃን (ሐይቅ)፣ አቡነ ብስጣውሮስ (ሐይቅ)፣ አቡነ ዮሴፍ (ላስታ) ዋና ዋናዎቹና በጣም ጥቂቶቹ ናቸው፡፡ ጻደቁን ንጉሥ ዐፄ ይኩኖ አምላክንም በትምህርተ ሃይማኖት አንጸውና ኮትኩተው ያሳደጉት ጻድቁ አባታችን ናቸው፡፡ እነዚህም ልጆቻቸው እያንዳንዳቸው እጅግ አስገራሚ ገድል ያላቸው የከበሩ ቅዱሳን ናቸው፡፡
አቡነ ተክለ ሃይማኖት ወደ አቡነ ኢየሱስ ሞዐ መጥተው በሐይቁ ዳር ቆመው ሳለ ቅዱስ ሚካኤል መጥቶ በእግሩ በውኃው ላይ እየሄደ እያሳያቸው ተከትለውት እንዲሄዱ ነገራቸው። አባታችን አቡነ ተክለ ሃይማኖትም ሐይቁን በእግራቸው ተራምደው ተሻግረው አቡነ ኢየሱስ ሞዐን አገኟቸው፡፡ እርሳቸውም አቡነ ተክለ ሃይማኖት ወደ እርሳቸው እየመጡ እንደሆነ በመንፈስ ዐውቀው ነበርና ሲያገኟቸው በጣም ተደስተው ከተቀበሏቸው በኋላ አመነኩሰዋቸዋል፡፡ አቡነ ኢየሱስ ሞዐ እጅግ በጣም ብዙ መነኮሳትን አፍርተዋል፡፡ የመጀመሪያው መነኩሴ አባ እንጦንስ ነው፡፡ እንጦንስ መቃርስን፣ መቃርስ ጳጉሚስን፣ ጳጉሚስ ቴዎድሮስን፣ አቡነ አረጋዊንና 8ቱን ቅዱሳን አመነኮሱ፡፡ አቡነ አረጋዊም ወደ ኢትዮጵያ በ460 ዓ.ም መጥተው ክርስቶስ ቤዛን፣ አባ ክርስቶስ ቤዛም መስቀለ ሞዐን፣ መስቀለ ሞዐም አባ ዮሐኒን፣ አባ ዮሐኒም አባ ኢየሱስ ሞዐን፣ አባ ኢየሱም ሞዐም አቡነ ተክለ ሃይማኖትን አመነኮሱ፡፡ አቡነ ኢየሱስ ሞዐ ምን ያህል ቀደምትና ባለ ታሪክ አባት እንደሆኑ ከዚህ መረዳት ይቻላል፡፡
በዮዲት ጉዲት እጅጉን ተጐድታ የነበረችው ሀገራችን ዳግም የወንጌሉ ብርሃን እንዲበራባት ሊቃውንት፣ እንዳይታጡባት፣ ቅዱሳት መጻሕፍት እንዳይቆነጻጸሉ፣ መነኮሳት አባቶች ወደ ደቡብ ኢትዮጵያ ወርደው ገዳማትን እንዲያስፋፉ ያደረጉት አቡነ ኢየሱስ ሞዐ ለቤተ ክርስቲያናችንና ለሀገራችን ትልቅ ባለውለታ ናቸው፡፡ በተለይም በሐይቅ እስጢፋኖስ ያፈሯቸውን 800 ሊቃውንት በመላዋ ኢትዮጵያ በመሰማራታቸው ዛሬ የምናያቸውን አብዛኛዎቹን ገዳማትና ቅዱሳት መጻሕፍት አቆይተውልናል፡፡ አባታችን ለ45 ዓመታት ሐይቅ እስጢፋኖስ ገዳምን በአበ ምኔትነት እያስተዳደሩ ከቆዩ በኋላ ኅዳር 26 ቀን 1292 ዓ.ም በዕለተ እሑድ ዐርፈዋል፡፡ ባረፉበት ዕለትም በወቅቱ በቦታው የታየው ብርሃን ሀገሪቱን መልቶ ታይቷል፡፡
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
አቡነ ሃብተ ማርያም
ዳግመኛም በዚህች ቀን ቅዱስ አባታችን አቡነ ሀብተ ማርያም ፅንሰታቸው ነው። አባታቸው ፍሬ ቡሩክ እናታቸው ዮስቴና የሚባሉ በሕገ እግዚአብሔር፣ በሃይማኖት፣ በትሩፋትና በምግባር ጸንተው የሚኖሩ ደጋግ ክርስቲያኖች ናቸው፡፡ ቅዱስ አባታችን ፅንሰታቸው ነሐሴ 26፣ ልደታቸው ግንቦት 26፣ ዕረፍታቸው ኅዳር 26 ነው፡፡ አቡነ ሀብተ ማርያምን አቡነ ተክለ ሃይማኖት ‹‹አምስት መቅሰፍታት እንዲጠፉ በደጄ በደብረ ሊባኖስ ተቀበርልኝ›› ብለው የለመኗቸው ታላቅ አባት ናቸው፡፡
የአቡነ ሀብተ ማርያም እናት ቅድስት ዮስቴና ጻድቁ አቡነ ሀብተ ማርያምን ከመውለዷ በፊት ‹‹ሰው ዓለሙን ሁሉ ቢገዛ ነፍሱን ካጣ ምን ይጠቅመዋል?›› የሚለውን የወንጌል ቃል አስባ መንና ወደ በረሃ የገባች ቢሆንም በበረሃ ውስጥ ከሰው ተለይቶ የሚኖር የበቃ ባሕታዊ በዋሻ ውስጥ አገኘችና ለምነና ወደ በረሃው እንደመጣች ነገረችው፡፡ ባሕታዊውም በጸሎት ወደ እግዚአብሔር ካመለከተ በኋላ ‹‹ምንኩስና ለአንቺ አልተፈቀደልሽም፣ ወደ ቤትሽ ግቢ፣ ከሕጋዊ ባልሽ ወንድ ልጅ ትወልጃለሽ እርሱም ለዓለም ሁሉ የሚጠቅም፣ ሰው ሁሉ የሚማፀነው፣ ገድሉ ትሩፋቱ በዓለም የሚነገርለት፣ በነፍስም በሥጋም የሚያማልድ፣ እንደ መልአክትም ክንፈ ጸጋ የሚሰጠው በምድር ሆኖ መንበረ ጸባኦትን የሚያይ ወንድ ልጅ ትወልጃለሽ›› በማለት ትንቢት ከነገራት በኋላ ቅድስት ዮስቴና ወደ ቤቷ ተመለሰች፡፡ እርሷም ሀብተ ትንቢት እስከመሰጠት ድረስ የደረሰች በሃይማኖት በምግባር በትሩፋት ያጌጠች ሆነች፡፡
ቅድስት ዮስቴናም ወደ ቤቷ ከተመለሰች በኋላ አቡነ ሀብተ ማርያም ተወለዱና ወላጆቻቸው ፈሪሃ እግዚአብሔርን እያስተማሩ አሳደጓቸው፡፡ ከዕለታት በአንድ ቀን ካህናቱ በቤተ ክርስቲያን ምህላ ሲያደርሱ ‹‹እግዚኦ መሐረነ ክርስቶስ›› እያሉ ሲጸልዩ ሰምተው በልቡናቸው ‹‹ይህች ጸሎት በጣም ጥሩ መልካም ጸሎት ናት፤ እኔ ይህችን ጸሎት መርጫታለሁ፤ በዚህ ጸሎት ዓለም ከአሳችነት ኅሊና በሚመጣውም ዓለም ከገሃነም እሳት እንድንድንባት አውቃለሁ›› አሉ፡፡ ይህችንም ጸሎት ማዘውተር ጀመሩ፡፡ እናትና አባታቸውም በተኙ ጊዜ ሌሊት ለጸሎት ተነሥተው በዚህ ጸሎት ፈጣሪአቸውን ያመሰግኑ ነበር፤ ስግደትን ይሰግዳሉ ነገር ግን እናትና አባታቸው ከእንቅልፋቸው በነቁ በጊዜ ሮጠው ወደ መኝታቸው ሄደው ይተኛሉ፡፡ የጽድቅ ሥራቸውንም ከአምላካቸው በቀር ማንም አያውቅባቸውም ነበር፡፡ ከጥቂት ጊዜ በኋላ አባታቸው ፍሬ ብሩክ የበግ ጠባቂ አደረጋቸው፡፡ እግዚአብሔር ግን በኋላ ለብዙዎች ስውራን ቅዱሳንና በዓለም ለሚኖሩ ምዕመናን በጎች ጠባቂ ያደርገው ዘንድ ወዶ መርጦታልና ያ ቀን እስኪደርስ ድረስ ፈጣሪያችን አቡነ ሀብተ ማርያምን ይጠብቃቸው ነበር፡፡
ከዕለታትም በአንደኛው ዕለት አባታቸን በጎችን ሲጠብቁ ሌሎች እረኞች በአመጻ ከሰው ሰርቀው ቆርጠው ያመጡትን እሸት ‹‹ና እንብላ›› አሏቸው፡፡ አባታችን ግን ‹‹ከየት እንዳመጣቸሁት ምንም ስለማላውቅ አልበላም›› አሏቸው፡፡ እረኞቹም ሀብተ ማርምን በቁጣ ዐይን እያዩአቸው ተቀምጠው ሲበሉ አባታችን ‹‹የማንችለው ዝናብ መጥቷልና ተነሡ በፍጥነት ወደቤታችን እንሂድ›› አሏቸው፡፡ እረኞቹም ‹‹ሰማዩ ብራ ነው ምንም ደመና የለውም፤ ነፋስም አይነፍስም፡፡ እኛ የማናየው አንተ ብቻ የምታየው ምን ነገር አለ?›› እያሉ በአባታችን ላይ ተዘባበቱባቸው፡፡ አባታችን ግን በጎቻቸውን እያስሮጡ በፍጥነት ወደ ቤታቸው ሄዱ፡፡ ወዲያውም በጣም ኃይለኛ ዝናብ ዘነበ፡፡ የጥፋት ውኃው በላያቸው እስኪፈጸምባቸው ድረስ እነዚያን እረኞች ከቦታቸው አልተነቃነቁም ነበርና በጥፋቱ ውኃ አለቁ፡፡ በዚያችም ሌሊት አቡነ ሀብተ ማርያን ከሰማይ ሦስት ጊዜ ‹‹ሀብተ ማርያም ሀብተ ማርያም›› የሚል ድምፅ ጠራቸው፡፡ አባታችንም እንደ ሳሙኤል ‹‹ጌታዬ ባሪያህ ይሰማሃል ተናገር›› ሲሉ ጌታችን አናገራቸው፡፡ ‹‹ከዚህ በኋላ ለሚሰሙህ ለመረጥኳቸው ቃሌን ትነግራቸው ዘንድ ከእኔም ጋር በምሥጢር በባለሟልነት ትነጋገር ዘንድ መርጨሃለሁ›› አላቸው፡፡
ከጥቂት ቀንም በኋላ አባታችን በጎችን እየጠበቁ ሳሉ አንድ አመጸኛ መጣና በትራቸውን በኃይል ነጥቆ ወሰደባቸው፡፡ አቡነ ሐብተ ማርያምም ‹‹በሕያው እግዚአብሔር አምልሃለሁ እቋቋምህ ዘንድ ኃይል የለኝምና በትሬን መልስልኝ›› ቢሉት የትዕቢትን ቃል ተናገራቸው፡፡ አባታችንም ‹‹እምቢ ካልክስ እሺ የእግዚአብሔርን ኃይል ታያለህ›› አሉት፡፡ ወዲያም ያ አመጸኛ ላዩ ታች፣ ታቹ ላይ፣ ግራው ቀኝ፣ ቀኙ ግራ ሆኖ በአየር ላይ ተሰቅሎ ዋለና እየጮኸ አባታችንን ለመናቸው፡፡ አባታችንም ‹‹የቀጣህ እግዚአብሔር ይቅር ይበልህ›› ባሉት ጊዜ ከተሰቀለበት ወርዶ በእግሩ ቆመ፡፡ በዚያ የነበሩና ይህንን ተአምር ያዩ እረኞችም እጅግ ፈርተው ሄደው ለወላጆቻቸው ያዩትን ተናገሩ፡፡ የሀገሩ ሰዎችም ‹‹ቀድሞ እግዚኦ መሐረነ ክርስቶስ እያለ ሲጸልይ ሲሰግድ አይተነዋል አሁንም ጠላቱን በነፋስ የሚቀጣ ይህ ልጅ ወደፊት ምን ይሆን!›› እያሉ አደቁ፡፡ ወላጆቻቸውም ይህን በሰሙ ጊዜ በግ ጠባቂነቱን አስተዋቸውና ወስደው ለመምህር ሰጧቸው፡፡ አቡነ ሀብተ ማርያምም የቤተ ክርስቲያንን ትምህርት ሁሉ በሚገባ ተማሩ፡፡
ከዚህም በኋላ አባታቸው ከሀገሪቱ ታላላቅ ሰዎች አንዷን እጮኛ አጨላቸው፡፡ ነገር ግን አቡነ ሀብተ ማርያም ‹‹አባቴ ሆይ እኔ ራሴን ለክርስቶስ በድንግልና ለመኖር አጭቻለሁ፣ ተራክቦዬም ቃለ ወንጌልን መስማት እንጂ ሌላ አይደለምና ለምን እንዲህ ትለኛለህ?›› አሉት፡፡ አባታቸውም ይህን ሲሰማ ተቆጥቶ ያለ አቡነ ሀብተ ማርያም ፈቃድ ሙሽራይቱን ለማምጣት ሄደ፡፡ አባታችን ግን ሀገር ጥለው ለመሰደድ ከቤት ተደብቀው ወጡ፡፡ መንፈስ ቅዱስም በመብረቅ አምሳል አባታቸውን ገስጻቸውና በዚህ ድንጋጤ ምክንያት ከዚህ ኃላፊ ዓለም ዐረፈ፡፡
አባታችንም የአባታቸውን ዕረፍት ሳያዩ አፋር ወደምትባል ሀገር ሄደው አባ ሳሙኤል ከሚባል ደግ መነኩሴ ቦታ ገብተው መነኩሴውን እያገለገሉት ኖሩ፡፡ አንድ ቀን አባታችን እንስራ ተሸክመው ውኃ ይቀዱ ዘንድ ወደ ወንዝ ወረዱና ውኃውን ቀድተው ሲመለሱ ድንጋይ አደናቀፋቸውና እንስራው ከላያቸው ላይ ወደቀ፡፡ ነገር ግን መሬት ከመድረሱ በፊት አባታችን ፈጥነው የጌታችን ስም በጠሩ ጊዜ እንስራው ወድቆ ሳይሰበር ተመልሶ በትከሻቸው ላይ ተቀመጠ፡፡ አባ ሳሙኤልም ይከተሏቸው ነበርና ይህን ጽኑ ተዓምር አይተው እጅግ አደነቁ፡፡
እንዲሁ ከዕለታት በአንድ ቀን በሌሊት መብራት ለአባ ሳሙኤል እያበሩ ሳለ መብራቱ ከእጃቸው ላይ ወድቆ ጠፋ፡፡ መምህሩም አባ ሳሙኤል ቁጡ ነበረና ስለ መምህራቸው ቁጣ በጣም ደንግጠው ወድቆ የጠፋውነ መብራት ፈጥነው ባነሱት ጊዜ መብራቱ በእግዚአብሔር ተዓምር ራሱ በርቶ ታየ፡፡ አባ ሳሙኤልም ይህን ተዓምራት አይቶ እጹብ እጹብ በማለት ‹‹የዚህ ቅዱስ ልጅ መጨረሻ ምን ይሆን?›› ብሎ ካደነቀ በኋላ ‹‹የዓለም ሁሉ የጥበብ መብራት ይሆናል›› ሲል ትንቢት ተናገረላቸው፡፡ እመቤታችን ለአባ ሳሙኤል ተገልጣላቸው የአቡነ ሀብተ ማርያምን ክብር ነግራዋለች፡፡ አባታችንም አባ ሳሙኤልን 12 ዓመት ከትሕትና ጋር እየታዘዙ ቤተ ክርስቲያንን እያገለገሉ ኖረው ከዚህ በኋላ በእግዚአብሔር ፈቃድ ወጥተው ሄደው እለ አድባር በተባለ ገዳም መኖር ጀመሩ፡፡ ከቦታውም ደርሰው ጥቂት ከቆዩ በኋላ እግዚአብሔር ከመረጣቸው ከአባ መልኬጼዴቅ እጅ የምንኩስናን ስርዓት ተቀበሉ፡፡ ይኸውም የሚዳው አቡነ መልኬጼዴቅ በደጃቸው የተቀበረውን ሰው አፈር የማያስበሉት ጻዲቅ ናቸው፡፡ ይህንንም የጻድቃኑን አባትና ልጅነታቸውን መሠረት በማድረግ የይሰበይ አቡነ ሀብተ ማርያም ገዳም ካህናት፣ መሪጌቶችና ዲያቆናት ግንቦት 4 ቀን ወደ ሚዳ መራቤቴ በመሄድ የአቡነ መልኬጼዴቅን በዓል እጅግ በደማቅ ሁኔታ ያከብራሉ፡፡
አቡነ ሀብተ ማርያምም ምንኩስናን ከተቀበሉ በኋላ ገድላቸውንና ትሩፋታቸውን በማብዛት በሳምንት አንድ ጊዜ ቅጠልን ብቻ የሚመገቡ ሆኑ፡፡ አርባ አርባ ቀን ሰማንያ ሰማንያ ቀንም የሚጾሙበት ጊዜ ነበር፡፡ በሌሊትም ወደ ጥልቅ ባሕር እየገቡ መዝሙረ ዳዊት፣ አራቱን ወንጌላትና ሌሎች የጸሎት መጽሐፍትን ይደግሙ ነበር፡፡ ፊታቸውም እንደ ንጋት ምሥራቅ ኮከብ ያበራ ጀመር፡፡
ከዚህም በኋላ ወደ ምሥራቅ ሄደው ጎሐርብ ወደምትባል ሀገር ደረሱ፡፡ በዚያም በዓት አጽንተው ሲጸልዩ ጌታችን ቅዱስ ገብርኤልንና ቅዱስ ሚካኤልን በቀኝና በግራ አስከትሎ ተገለጠላቸውና ‹‹ወዳጄ ሀብተ ማርያም ሆይ ሰላም ላንተ ይሁን›› አላቸው፡፡ ያን ጊዜ አባታችን ከፈጣሪአቸው ግርማ የተነሳ ደንግጠው ከመሬት ወድቀው እንደ በድን ሆኑ፡፡ ጌታችንም አንስቶ ክቡራን በሆኑ እጆቹ አጸናቸውና ‹‹የመጣሁት ለጸናህ ነው ሰውነትህንም እንደ ንስር ላድሳት ነው እንጂ ላጠፋህ አይደለም፡፡ ድካምህና ገድልህ ሁሉ ለዘለዓለም መታሰቢያ ሊሆን በኢየሩሳሌም ሰማያዊት ተጽፎልሃል ብዬ በእውነት እነግርሃለሁ፡፡ ለአንተ ለወደድኩህና ለመረጥኩህና ወዳጄ የማቴዎስንና የማርቆስን ወንጌል ባነበብክ ጊዜ ተጭነህ ወደምትሄድበት ቦታ የሚያደርስህ የብርሃን ሰረገላ ሰጥቼሃለሁ፡፡ እንደ አንተም ካሉ በዋሻ በመሬት ፍርኩታ ከሚኖሩ ከመረጥኳቸው ቅዱሳን ጋር ትገናኝ ዘንድ ወደ አራቱም አቅጣጫ ትበር ዘንድ የብርሃን ሠረገላ ሰጥቼሃልሁ፡፡ ዳግመኛም የሉቃስንና የዮሐንስን ወንጌል ባነበብክ ጊዜ ወደ ኢየሩሳሌም ትሄድ ዘንድ የእሳት ሠረገላ ሰጥቼሃለሁ›› አላቸው፡፡ ዳግመኛም ‹‹በጸሎትህ አምኖ በጎ ሥራ ለሚሠራ ሁሉ፣ ስምህን የጠራውን ዝክርህን ያዘከረውን ሁሉ የሀብተ ማርያም አምላክ ሆይ ከጠላት እጅ አድነኝ ያለኝን በኅሊና ያሰበውን በልቡናው የወሰነውን እፈጽምለታለሁ፡፡ አንተን ገድልህንና ቃል ኪዳንህን የናቀውን ያቃለለውን ሁሉ ፍጹም መበቀልን እበቀለዋለሁ፡፡ እንደ ወዳጄ እንደ ፊቅጦርም በእናቴ በማርያም ድንግል አተምኩህ›› ካላቸው በኋላ ቅዱስ ሚካኤል ከእርሳቸው እንዳይለይ የዘወትር ጠባቂ አድርጎ ሰጣቸውና በታላቅ ግርማ ወደ ሰማይ ዐረገ፡፡
አባታችንም ከጌታችን ይህን ቃል ኪዳን ከተቀበሉ በኋላ ነፍሳቸውን ‹‹ነፍሴ ሆይ ከፈጣሪሽ ከእግዚአብሔር ጋር ፊት ለፊት አፍ ለአፍ ትነጋገሪ ዘንድ ደፍረሻልና በጎም ሥራ ሳይኖርሽ ከፈጣሪሽ ቃልኪዳን ተቀብለሻልና ከዛሬ ጀምሮ እንደ መላእክት ዘወትር አትተኝ›› እያሉ ተጋድሏቸውን አብዝተው ቀጠሉ፡፡
መልአኩ ቅዱስ ሚካኤልም አባታችንን እንደ ጓደኛ ሆኖ ዘወትር ይጎበኛቸው ነበር፡፡ ቅዱሳን አባታቸንን ሊጎበኟቸው መጥተው ከደጅ ቆመው እንደሆነ ቅዱስ ሚካኤል አባታችንን ‹‹እከሌ ጉዳዩ እንዲህ ነው እንዲህ ብለህ ተናገረው…›› እያለ ያማክራቸው ነበር፡፡ እሳቸውም ቅዱስ ሚካኤል ካዘዛቸው በቀር ምንም አይሠሩም ነበር፡፡ ቅዱሳት መጻሕፍትንም ባነበቡ ጊዜ ኃይለ ቃሉን እየተረጎመ ምሥጢራትን ይነግራቸዋል፤ የተሰወረውንም ይገልጥላቸዋል፡፡ ከእንስሳት ጩኸት ጀምሮ ከዱር አራዊት ድምፅና እስከ አእዋፍ ቋንቋ ያለውን ያስረዳቸው ነበር፡፡
ይኸውም መልአክ አንድ ቀን አቡነ ሀብተ ማርያምን ወደ ቤተ ክርስቲያን አስገብቷቸው ሥጋ ወደሙን ለመቀበል ተዘጋጅተው ሳለ ወንጌል የሚነበብበት ሰዓት ሲደርስ ያልተማረ ቄስ የክርስቶስ ጌትነቱን የምትናገር ወንጌልን ሲያነብ ‹‹ወዮሴፍ ብእሲሃ ለማርያም ጻድቅ ውእቱ›› የሚል ከቄሱ አፍ ይህን ንባብ አባታችን ሲሰሙ እጅግ ደንግጠው ወንጌል ወደሚነበብበት ስፍራ ሄደው የሚያነበውን ቄስ ገሠጹት፡፡ ‹‹ወዮሴፍሰ ፈሃሪሃ ለማርያም ጻድቅ ውእቱ በል እንጂ ብእሲሃ አትበል›› ብለው መከሩት፡፡ ቄሱም አቡነ ሀብተ ማርያም እንዳዘዙት ከስህተቱ ወደ ቀና ንባቡ ተመለሰ፡፡ ይህን ጊዜ ጌታችን ለአባታችን ድጋሚ ተገልጦላቸው ‹‹ሀብተ ማርያም ሆይ ይህን ትምህርትህን ወድጄ አመሰገንኩህ፣ የእናቴን የድንግል ማርያምን የድንግልናዋን ንጽሕና ስለ አከበርክ እኔም በመንግስተ ሰማያት ፈጽሜ አከብርሃለሁ›› አላቸው፡፡ ዳግመኛም ጌታችን ‹‹አሁንም ዮሴፍ ብእሲሃ ለማርያም የሚሉትን ሁሉ ለያቸው እንጂ አትተዋቸው፤ እንዲህ የሚል ጽሑፍም ብታገኝ እንዳይኖር እርሱን ፍቀህ ፈሃሪሃ ለማርያም የሚለውን ጻፍ›› ብሎ አባታችንን ካዘዛቸው በኋላ ሰላምታ ሰጥቷቸው ወደ ሰማይ ዐረገ፡፡ አባታችንም በዚህ ጊዜ ፊታቸው ላይ ብርሃን ስለተሳለባቸውና እንደ ፀሐይ ስላበራ ሰዎችም አይተው ባደነቁ ጊዜ ወደ በዓታቸው ገቡና ጌታችንን ‹‹አቤቱ ጌታዬ ሆይ በሰው ፊት ክብሬን አትግለጥብኝ ሰውርልኝ፣ በቸርነትህም አድነኝ›› ብለው ጸለዩ፡፡ እንዲህም ብለው በጸለዩ ጊዜ ፊታቸው መልኩ ተለውጦ እንደ ቀድሞው ሆነ፡፡
ከዕለታትም በአንደኛው ቀን አባታችን ታመው ተኝተው ሳለ ቅዱስ ጴጥሮስና ቅዱስ ጳውሎስ መጥተው ሥጋ ወደሙን አቀብለዋቸዋል፡፡፡ አባታችን በጸሎት ላይ ሳሉ ቅዱስ ሚካኤል ነጥቆ ወደ ሰማይ ወስዶ ቅዱሳን የሚኖሩባቸውን ዓለማት፣ መንግስተ ሰማያትን እንዲሁም ኃጥአን የሚኖሩበትን ሲኦልን አሳያቸው፡፡ በገነት ያሉትንም ከአዳም ጀምሮ እሳቸው እስካሉበት ጊዜ እስከ አቡነ መርሐ ክርስቶስ ድረስ ያሉትን ቅዱሳን አሳያቸው፡፡ ከዚህም በኋላ በእግዚአብሔር ዙፋን ፊት ቆመው ሳለ ሰይጣንም መጥቶ በእግዚአብሔር ፊት ቆመና ‹‹አቤቱ ጌታዬ ሆይ በሀብተ ማርያም ላይ እንደ ኢዮብ ብዙ መከራ አጸናበት ዘንድ ፍቀድልኝ›› ብሎ እየጮኾ ሲናገር አባታችን እጅግ ፈርተው አለቀሱ፡፡ እግዚአብሔር ግን በሰይጣን ላይ ተቆጥቶ ‹‹በነፍሱም በሥጋውም መከራ ታጸናበት ዘንድ አልፈቅድም›› አለው፡፡ ‹‹እኔ ከእናቱ ማኅፀን ጀምሮ መርጨዋለሁና በንጽሕናና በቅድስና ኃጢአት እንዳይሠራ ዘወትር እጠብቀዋለሁ፤ በእርሱ ላይ ማሰልጠንስ ይቅርና በሀብተ ማርያም ጸሎት በተማጸነኝ ሁሉ ላይ እንኳን አላሠለጥንህም›› አለው፡፡ ሰይጣንም ይህን ቃል ሰምቶ አፍሮ እያዘነ ሄደ፡፡
አቡነ ተክለ ሃይማኖትም ከእርሳቸው በኋላ በመንበራቸው ከተሾሙት ከስምንቱ መምህራን ጋር ለሀብተማርያም ተገለጡላቸው፡፡ እነርሱም ኤልሳዕ፣ ፊሊጶስ፣ ሕዝቅያስ፣ ቴዎድሮስ፣ ዮሐንስ፣ ዮሐንስ ከማ፣ እንድርያስና መርሐ ክርስቶስ ናቸው፡፡ እነዚህም መልካቸው እንደ ፀሐይ ያበራ ልብሳቸው እንደ መብረቅ ያንጸባርቅ ነበር፡፡ አቡነ ተክለ ሃይማኖትም ልብሳቸው የእሳት ላንቃ የከበበው መልኩም ነጭ የሆነ የሚያስደንቅ ሆኖ ‹‹በቅድምና ለነበረ ለአብ በቅድምና ለነበረ ለወልድ በቅድምና ለነበረ ለመንፈስ ቅዱስ ምስጋና ይገባል›› እያለ ልብሳቸው በሰው አንደበት ያመሰግን ነበር፡፡ አቡነ ተክለ ሃይማኖትም አቡነ ሀብተ ማርያምን ‹‹ልጄ ሀብተ ማርያም ሆይ! ፈጣሪዬ እግዚአብሔር ስለወደደህ ብዙ ምርኮ እንዳገኘህ በአንተ ፈጽሞ ደስ ይለኛል፡፡ ነገር ግን የምለምንህ ነገር አለና እሺ በለኝ›› አሏቸው፡፡
አቡነ ሀብተ ማርያምም ‹‹ጌታዬ ነገሩ ምንድን ነው?›› ሲሏቸው አቡነ ተክለሃይማኖት ‹‹ከተቀበርኩበት ቦታ እንድትቀበር ቃል ኪዳን ግባልኝ›› አሏቸው፡፡ አቡነ ሀብተማርያምም ‹‹አባቴ ሆይ ይህንን አደርግ ዘንድ ስለምን ትወዳለህ?›› አሏቸው፡፡ አቡነ ተክለሃይማኖትም በሀገሬ ላይ የታዘዙ አምስት መቅሰፍቶች አሉና ስለዚህ ነው እነዚህም አንዱ መብረቅ ነው፤ ሁለተኛውም ቸነፈር ነው፤ ሦስተኛውም ረሃብ ነው፤ አራተኛውም ወረርሽኝ ነው፤ አምስተኛውም የእሳት ቃጠሎ ነው፡፡ የአንተ አጽም በውስጡ የተቀበረ እንደሆነ አጥንቴ የተቀበረባት ሀገሬ ከነዚህ መቅሰፍታት ትድናለች›› አሏቸው፡፡
አቡነ ሀብተ ማርያምም ‹‹ንዑድ ክቡድ የምትሆን አባቴ ሆይ ልዩ ክቡር በሚሆን በአንተ አጽም መቀበር ያልዳነች በእኔ አጽም መቀበር ድኅነት ታገኛለችን? ይህንስ ተወው›› ብለው በተከራከሯቸው ጊዜ አቡነ ተክለ ሃይማኖትም መልሰው ‹‹ልጄ ሀብተ ማርያም ሆይ አንተ የማታውቀው ከፈጣሪያችን ከእግዚአብሔር የተሰጠህ እኔ የማውቀው ክብር አለህና ስለዚህ ነው፡፡ ይልቁንስ እንዳልኩህ በተቀበርኩበት ቦታ እንድትቀበርልኝ ቃልኪዳን ግባልኝ›› ብለው ማለዷቸው፡፡ ይህንንም ሲባባሉ እንዲህ የሚል ቃል መጣላቸው፡- ‹‹ከወዳጄ ከሀብተ ማርያም አንደበት ይህ ቃልኪዳን አይወጣም፣ ዳግመኛም ወዳጄ ተክለ ሃይማኖት ሆይ! እርሱ በወደደው የሚቀበር አይደለምና እኔ ከተቀበርኩበት እንድትቀበር ብለህ የምታስገድደው ለምንድን ነው? እኔ በወደድሁት ቦታ ይቀበራል እንጂ›› የሚል ቃል ተነገረ፡፡ አቡነ ተክለሃይማኖትም እየለመኑናና እየሰገዱ ከሥላሴ ዙፋን ፊት ተንበረከኩ፡፡ ሦስተኛውም ‹‹ይሁን እንዳልከው ይቀበርልህ›› የሚል ቃል ተሰማ፡፡ ዳግመኛም ‹‹በአንተም አጽም በሀብተ ማርያምም አጽም ቦታህ ከመቅሰፍታት ትዳንልህ፤ ልጆችህ ግን በቸነፈር ደዌ ቢሞቱ ከሰማዕትነት ተቆጥሮላቸው ወደ መንግሥተ ሰማያት እንዲገቡ በራሴ ምዬ ቃልኪዳን ገብቼልሃለሁ›› አላቸው፡፡ በዚህም ጊዜ አቡነ ተክለሃይማኖት እጅግ ደስ ተሰኝተው ሦስት ጊዜ ሰገዱ፡፡
ከዚህም በኋላ መልአኩ ለአቡነ ሀብተ ማርያም ክብሯ እንደ ጽርሐ አርያም የሆነች አገርን አሳያቸው፡፡ ሥፍር ቁጥር የሌላቸውም ቅዱሳን መላእክት በውስጧ ተድላ ደስታ ያደርጉባት ነበር፡፡ አባታችንም መልአኩን ‹‹ይህች ክብሯ ፍጹም የሆነችን አገር ማን ትባላለች በውስጧ ለመኖር በእጅጉ ወድጃለሁና›› ብለው ሲጠይቁት መልአኩም ‹‹ይህችማ አገር የአባትህ የተክለ ሃይማኖት አጽም ያረፈባት ደብረ ሊባኖስ ናት፤ ከእርሱም ጋር በክብር እስክትነሣ ድረስ በውስጧ ትቀበርባት ዘንድ ለአንተም ተሰጥታሃለችና ደስ ይበልህ፡፡ አባትህም እንደ ኢየሩሳሌም እንደትሆንለት ቃልኪዳን ተቀብሎባታል›› አላቸው፡፡
በአንደኛውም ቀን አቡነ ሀብተ ማርያም ከሌሎች ቅዱሳን ጋር ሆነው ሲሄዱ ብዙ አጋንንት እየተደነባበሩ ወደ ታች ሲወርዱ ተመለከቱና አባታችን ሥራቸውን ለማየት ተከተሏቸው፡፡ አንዱንም ኃጥእ ይዘው ነፍሱን ከሥጋው ለዩዋትና ወደ ሲኦል አወረዷት፡፡ አባታችንም ከሌሎቹ ቅዱሳን ጋር ሆነው ያችን ነፍስ ይምርላቸው ዘንድ ጌታችንን በጸሎት ማለዱት፡፡ ነገር ግን ‹‹ለጣዖት ስትሰግድ ስለኖረች ይህችን ነፍስ አልምራትምና አትድከሙ›› የሚል ቃል ከልዑል እግዚአብሔር ዘንድ መጣላቸው፡፡ ቅዱሳኑም ‹‹ልመናችንን የማትቀበል ከሆነ በከንቱ ሰብስበኸናል›› ብለው ቢያዝኑ እግዚአብሔርም ‹‹ሕገ እግዚአብሔርን የዘነጉ ሰዎችን ቅጣት እንድታዩ ነው›› አላቸው፡፡ እነርሱም ሕገ እግዚአብሔርን የዘነጉ ሰዎችን ሲቀጣቸው ለደጋጎቹ ሰዎች ደግሞ መልካሙን ዋጋቸውን ሲሰጣቸው አይተው አንድ ሆነው አመስግነውታል፡፡
ከዚህም በኋላ መልአኩ ቅዱስ ራጉኤል አንዱን ሰው በመብረቅ ቀሰፈውና ቅዱስ ሚካኤል ሄዶ ቅዱስ ራጉኤልን ሲከራከረው አባታችን ተመለከቱ፡፡ ቅዱስ ሚካኤል ‹‹የእኔ አገልጋይ ነውና ለምን ገደልከው?›› ሲለው ቅዱስ ራጉኤልም ‹‹ሰንበት ሳይለይ ዝሙትን መሥራት የለመደ ሥራውም ዝሙት ስለሆነ በፈጣሪዬ ታዝዤ ነው የገደልኩት፡፡ ኃጥአንን ሊያጠፋ እንጂ ጻድቃንን ለመቅጣት መብረቅ እንዳይታዘዝ አንተስ ታውቅ የለም እንዴ?›› አለው፡፡ ይህንንም ተባብለው ከሥላሴ ፊት ሰግደው ቅዱስ ሚካኤል የተገባለትን ቃልኪዳን በማሳሰብ ምልጃውን አቀረበ፡፡ እግዚአብሔርም በጎና ክፉ ሥራዋን ባስመዘነ ጊዜ በጎ ሥራዋ ስለበለጠ ቅዱስ ሚካኤል ያችን ነፍስ ታቅፎ ወስዶ ለቅዱስ ገብርኤል ሰጠው፡፡ ሰባቱም ሊቃነ መላእክት እየተቀባበሉ ወስደው ከመስቀል ዘንድ አደረሷት፡፡ ለቅዱስ መስቀልም ካሰገዷት በኋላ አሳልመዋት በቅዱስ ሚኤካል አማላጅነት ወደ ገነት አስገቧት፡፡ አቡነ ሀብተ ማርያምም ይህን በተመለከቱ ጊዜ ቅዱስ ሚካኤልን ‹‹መስቀል ታሳልሟት ዘንድ ያችን ነፍስ ወደ መስቀል ለምን ወሰዳችኋት?›› ብለው ጠየቁት፡፡ መልአኩም ‹‹በትልቅም በትንሽም ነገር ክርስቲያናዊትን ነፍስ የሚቃወም ቢመጣባት ድል የምትነሳበትን በመስቀል ፍርድ ይታይላታልና ስለዚህ ነው፡፡ የሚከራከራት ቢኖር ግን እንዳየኸው ወደ መስቀል ባደረሷት ጊዜ የሚቃወማት ሰይጣን ፈጥኖ ይርቅላታል ዳግመኛም ሊከራከራት አይችልም›› አላቸው፡፡
ከአቡነ ሀብተማርያም በረከት ለመቀበል ብዙ ቅዱሳን ከሮም፣ ከግብፅ፣ ከአስቄጥስና ከሲሐት ገዳም ወደ አባታችን ዘንድ ይመጡ ነበር፤ ከየሀገራቸውም በአንበሳ ተቀምጠው የሚመጡ አሉ፤ ክንፍ ተሰጥቷቸው እንደ ንስር የሚበሩም አሉ፤ ብፁዕ አቡነ ሀብተ ማርያምም የቅዱሳኑን ብቃት አይተው ‹‹ሥራችሁ እንዲህ እንዲህ ሲሆን ለምን ወደኔ መጣችሁ?›› ብለው ሲጠይቋቸው ቅዱሳኑም ‹‹በማንኛውም ሥራ እግዚአብሔርን በለመነው ጊዜ በኢትዮጵያ የሚኖር እንደ ሙሴ ያለ ሀብተ ማርያም የሚባል ወዳጄ አለና ሁሉን ስለሚነግራችሁ ዘወትር እርሱን ጠይቁ ብሎ ስላዘዘን ወደ አንተ መጣን›› አሏቸው፡፡ አባታችንም ቅዱሳኑን ከባረኳቸውና ከእነርሱም ከተባረኩ በኋላ አባታችን ለቅዱሳኑ የሚመጣውን እንዳለፈ የሚደረገውንም እንደተደረገ አድርገው ይነግሯቸዋል፡፡ ቅዱሳኑም ከልጅነታቸው ጀምረው እስከዚያች ቀን ድረስ የሠሩትን ሥራ ሁሉ ይነግሯቸዋል፡፡ እነርሱም እጃቸውን እየሳሙ በረከታቸውን ይቀበሉ ነበር፡፡ እንደዚሁም አቡነ ሀብተ ማርያም ቅዱስ ሚካኤልና ቅዱስ ገብርኤል እየተራዱዋቸው ቀድሰው በሚያቆርቡ ጊዜ ተሰውረው የሚኖሩ 500 ስውራን ቅዱሳን መጥተው ሥጋ ወደሙን ከአባታችን እጅ ተቀበሉ፡፡ ቀድሰውም ወደበዓታቸው እንደገቡ እመቤታችን ተገልጣላቸው ‹‹በነገውም ዕለት ቅዳሴዬን ቀድስ፣ ይህም ቅዳሴ መዓዛ ቅዳሴ ነውና፡፡ የዓለም መሠረት ማርያም ወደኔ ነይ ብለህ በጠራኸኝ ጊዜ ነቢያትን ሐዋርያትን አስከትዬ መጥቼ እባርክሃለሁ›› አለቻቸው፡፡ አባታችንም ‹‹በነገው ዕለት ሌላ ተረኛ ቄስ ይቀድሳልና ይህ እንዴት ይሆንልኛል?›› አሏት፡፡ እመቤታችንም ‹‹ፈቃዴ ስለሆነ አንተ እንድትቀድስ አደርጋለሁ›› አለቻቸው፡፡ በነጋታው ተረኛው ቄስ ከእንቅልፉ በነቃ ጊዜ ቸኩሎ እየተፋጠነ ወደ ቤተ ክርስቲያን ሲገሰግስ ወድቆ ጥርሱ ደማና ስለ ሥጋ ወደሙ ቅዳሴ እጅግ ደንግጦ ወደ አባታችን መጥቶ ‹‹ቅዳሴው በእኔ ስም ከሚታጎል አንተ ቀድስልኝ›› አላቸው፡፡ አባታችንም አስቀድማ እመቤታችን የነገረቻቸውን ነገር አስበው እያደነቁ ሄደው ቀደሱ፡፡ እመቤታችንም ነቢያትን ሐዋርያትን አስከትላ መጥታ ባረከቻቸው፡፡
ነሐሴ 26 ቀን የሚከበሩ
👉
ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት
1.ብጽዕት ሣራ (የአብርሃም ሚስት)
2.ቅዱሳን አባ ሞይስስና እህቱ ሣራ (ሰማዕታት)
3.ቅዱሳን አጋቦስና ቴክላ (ሰማዕታት)
👉
ወርሐዊ በዓላት
1.ቅዱስ ቶማስ ሐዋርያ
2.አቡነ ሐብተ ማርያም ጻድቅ
3.አቡነ ኢየሱስ ሞዐ ዘሐይቅ
4.ቅዱሳን ሰማዕታተ ናግራን
5.ቅዱስ አቡነ ሰላማ ከሣቴ ብርሃን
ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በከበሩ ቅዱሳን ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን ።
ስንክሳር ዘወርኀ ነሐሴ

No comments:

Post a Comment

Post Bottom Ad

Pages