ስንክሳር ዘወርኀ ነሐሴ 5 - አትሮንስ ሚዲያ - Atrons Media

አትሮንስ ሚዲያ - Atrons Media

ስብኩ ወንጌለ ለኩሉ ፍጥረት ማቴ 16፤15


በቅርብ የተጻፉ

Post Top Ad

Friday, February 16, 2024

ስንክሳር ዘወርኀ ነሐሴ 5

 አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም



ነሐሴ አምስት በዚህች ቀን የደብረ ቢዘን አባ ፊልጶስ አረፈ፣ ቅዱስ አባ አብርሃም ገዳማዊ አረፈ፣ የከበረ ተጋዳይ ወታደር ቅዱስ ዮሐንስ ጻድቅ አረፈ።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
አባ ፊልጶስ ዘደብረ ቢዘን
ነሐሴ አምስት በዚህች ቀን የደብረ ቢዘን አባ ፊልጶስ አረፈ። አቡነ ፊልጶስ ዘደብረ ቢዘን እንደ ነቢዩ ኤርምያስ በእናታቸው ማኅፀን ሳሉ የተመረጡና እንደተወለዱ ነው ሰማንያ አንዱን የብሉይ መጻሕፍትን አጠናቀው ያወቁት ናቸው፡፡ በ12 ዓመታቸውም ለመመንኮስና ገዳም ለመግባት ወስነው ወላጅ እናታቸውን አሰናብቺኝ በማለት ጠይቀዋል፡፡ ቅድስት እናታቸውም መርቀው ሸኟቸውና ትግራይ ውስጥ ወደሚገኘውና ደብረ ጸራቢ ወደሚባለው ገዳም ገቡ፡፡ የገዳሙ አስተዳዳሪ አቡነ በኪሞስም የምንኩስና ቀንበሩና ሸክሙ እጅግ ከባድ መሆኑን በመንገር ወደ እናታቸው እንዲመለሱ ቢመክሯቸውም አቡነ ፊልጶስ ግን ለምንኩስና የታጩ ሙሽራ መሆናቸውን ነገሯቸው፡፡ ከብዙ ፈተናም በኋላ አመነኮሷቸው፡፡
በገዳሙም እንጨት እየለቀሙና እየፈለጡ፣ ውኃ እየቀዱ፣ የክርስቶስን ሕማሙን ሞቱን እያሰቡ በጾምና ጸሎት ሲጋደሉ ከኖሩ በኋላ ጌታችን ተገልጦላቸው ወደ ሽሬ እንዲሄዱ ነገራቸውና ሽሬ አደያቦ ወደሚባለው ስፍራ ሄዱ፡፡ ብዙ አስደናቂ ተአምራት እያደረጉ ወንጌልን በሀገሩ ዞረው ሰበኩ፡፡ እንደ ሐዋርያው ቅዱስ ጴጥሮስ በጥላቸው ድውያንን ይፈውሱ ነበር፡፡ ከዚህ በኋላ ወደ ደብረ ቢዘን እንዲሄዱ ተነግሯቸው የእርሳቸውን በረከት ለመቀበል ከመጡ 16 ደጋግ መነኮሳት ጋር ወደ ደብረ ቢዘን ሄዱ፡፡ ይኸውም በኤርትራ ክፍለ ሀገር በሐማሴን አውራጃ ከአሥመራ ከተማ በስተምሥራቅ 25 ኪ.ሜ ርቀት ላይ የሚገኘው አስደናቂው ገዳም ነው፡፡
ጻድቁ የሐይቅ እስጢፋኖስን ባሕር በተአምራት ያቃጠሉት አባት ናቸው፡፡ በንጉሡ በዐፄ ዳዊት ዘመን ሰንበትን አንድ ብቻ ናት እያሉ በአንደኛዋ ሰንበት ሥራ ሲሠሩ ጻድቁ አቡነ ፊልጶስ ይህን ሰምተው አንዲት ሰንበት የሚሉትን ሁሉ ተቃወሟቸው፡፡ ከግብፅ የመጡት ጳጳስም ቀደም ብሎ ከአቡነ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ አሁንም ከአቡነ ፊልጶስ ጋር ንጉሡ ዐፄ ዳዊት አከራክረዋቸው ጳጳሱም በክርክሩ ተረቱ፡፡ ክፉዎችም በአቡነ ፊሊጶስ ላይ በክፋት ተነሱባቸው፡፡ በአቁማዳ ጠቅልለው ሐይቅ ባሕር ውስጥ ጣሏቸው፡፡ በዚህም ጊዜ እሳቸው የተጣሉበት ባሕር በእሳት ተቃጥሎ ጽድቃቸውን መስክሮላቸዋል፡፡ ዛሬም ድረስ በሐይቅ እስጢፋኖስ ባሕር ዳርቻ ላይ የተቃጠለው ድንጋይ ምልክቱ በግልጽ ይታያል፡፡ በወቅቱ የንጉሡ ሚስት በዋናተኛ አስፈልጋ ከሐይቁ ውስጥ አስወጣቻቸው፡፡ እግራቸውንም አጥባቸው ስትጨርስ የእግራቸውን እጣቢ ጠጣችው፡፡ ወዲያውም ‹‹ከማኅፀንሽ ፍሬ ታላቅ ጻድቅ ልጅ ይወጣል›› ብለው ትንቢት ነገሯት፡፡ በትንቢታቸውም መሠረት ታላቁ ጻድቅ ንጉሥ ዐፄ ዘርዐ ያዕቆብ ተወልዱ፡፡ በወቅቱ በተፈጠረው አለመግባባትና ክፉዎችም በባሕር ውስጥ ስለጣሏቸው ንጉሡ ዐፄ ዳዊትም አቡነ ፊልጶስን ከልብ ይቅርታ ጠይቀው ወዲያው ታርቀዋል፡፡ በዘመናቸውም ርኃብ ስለነተሳ ጻድቁን ከገዳማቸው አስጠርተው ‹‹ምን ባደርግ ይሻለኛል?›› ብለው አማክረዋቸዋል፡፡ አቡነ ፊልጶስም ‹‹የጌታችንን መስቀል ያስመጡ›› ብለው መከሯቸው፡፡
ንጉሡ ዐፄ ዳዊትም በአቡን ፊልጶስ ምክር መሰረት ከኢየሩሳሌም፣ ከቍስጥንጥንያና ከእስክንድርያ መንግሥታት ጋር ተጻጽፈው ዓሥሩን ታላላቅ ቅዱሳን ይዘው ሄደው መስቀሉን መስከረም 10 ቀን አምጥተውታል፡፡ ቅዱስ መስቀሉን ያመጡት ዓሥሩ ቅዱሳንም የደብረ ቢዘኑ አቡነ ፊልጶስ ፣ የጣና ደሴቱ አቡነ ኂሩተ አምላክ፣ የጣና ደሴቱ አቡነ እንድርያስ፣ አቡነ በትረ ማርያም፣ አቡነ ዮሐንስ፣ አቡነ ታዴዎስ፣ አቡነ ያፍቅረነ እግዚእ፣ አቡነ ዘካርያስ፣ አቡነ ያሳይና አቡነ ቶማስ ናቸው፡፡ አቡነ ፊሊጶስ ዘደብረ ቢዘን በታላቅ ተጋድሎ ኖረው ከጌታችን ዘንድ ታላቅ ቃልኪዳን ከተቀበሉ በኋላ ነሐሴ 5 ቀን በታላቅ ክብር ዐርፈዋል፡፡
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
ቅዱስ አባ አብርሃም ገዳማዊ
በዚህች ቀን ሌላው አብርሃም አረፈ። የዚህም ቅዱስ ወላጆቹ ባለጸጎች ናቸው በተግሣጽና ፈሪሃ እግዚአብሔርን በማስተማር አሳደጉት ። በአደገ ጊዜም ያለ ፈቃዱ አጋቡት እግዚአብሔርም ወደሚፈቅደው ይመራው ዘንድ ሲለምን ኖረ።
በሰባተኛውም ቀን በዐልጋው ላይ ሳለ የእግዚአብሔር ቸርነት አነሳሥቶት ከጫጉላ ቤቱ ወጣ ብርሃን እየመራው ሒዶ ባዶ ቤት አግኝቶ በውስጡ ገብቶ ኖረ ምግቡን ከሚቀበልባት ከጥቂት መስኮት በቀር መዝጊያ ሠርቶ ደጁን ዘጋ።
ዓለምን ከተወ በዓሥረኛው ዓመት አባትና እናቱ ብዙ ጥሪት ትተውለት ሞቱ እርሱ ግን ለድኆችና ለችግረኞች በትኖ በጾምና በጸሎት ተወስኖ እየተጋደለ ኖረ ከአንድ ዐጽፍና ሰሌን በቀር ምንም ምን ጥሪት አላኖረም እንዲህም ሆኖ ዐሥር ዓመት ተጋደለ።
እግዚአብሔርም ትዕግሥቱን አየ በአንዲት አገርም አረማውያን ነበሩ ከታናሾቻቸው እስከ ታላላቆቻቸው ወደ ሃይማኖት ሊመልሳቸው የሚችል የሌለ። በአንዲት ቀንም አባ አብርሃምን ጳጳሱ አሰበው ብርታቱንና ብልህነቱንም አይቶ ቄስ እንዲሆንና እነዚያን አረማውያን እንዲመልሳቸው አስገደደው በግድ አስጨንቆም ቅስና ሾመው ። ወደዚያም ቦታ ደርሶ ቤተ ክርስቲያን ሠራ እነዚያን አረማውያን እርሱን ፈጣሪያቸውን ወደ ማወቅ ይመልሳቸው ዘንድ በውስጧ ወደ እግዚአብሔር ጸለየ።
በአነዲት ቀንም ወደ ጣዖቶቻቸው ቤት ገባ ያን ጊዜ ጣዖታቱን ከመቀመጫቸው ጣላቸው የአገር ሰዎችም በአዩ ጊዜ ቁጣን ተመልተው አብዝተው ደበደቡትና ከአገር አበረሩት በጥዋትም በቤተ ክርስቲያን ውስጥ ሲጸልይ አገኙት።
ሁለተኛም በገመድ አሥረው ወደ ከተማው ውጭ ጐትተው በላዩም አፈር ቆልለው እንዳይሞት ጥቂት መተንፈሻ ትተው አልፈው ከዚያ ሔዱ። በእግዚአብሔርም ኃያል ተነሥቶ ሔደ ስለ መመለሳቸውም ሲጸልይ አገኙት በእንዲህ ያለ ሥራም እየተጋደለ ዐሥር ዓመት ኖረ።
የክብር ባለቤት እግዚአብሔርም ትዕግሥቱን አይቶ ወደ ቀናች ሃይማኖት ልባቸውን መለሰ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም ከታናናሾች እስከ ታላላቆች ድረስ ሁሉንም አጠመቃቸው
የክብር ባለቤት በሆነ በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሃይማኖትም ጸኑ።
ከዚህም በኋላ በሃይማኖታቸው መጽናታቸውን ባየ ጊዜ ከንቱ ውዳሴ እንዳያመጣበት ፈርቶ ወደ እግዚአብሔር ጸለየ አገሪቱንም በመስቀል ምልክት አማተበባትና ማንም ሳያውቅ ወጥቶ ወደ ሌላ አገር ሔደ ።
ሰይጣንም በሚያስፈራው በብዙ ሥራ ይፈታተነው ነበር ቅዱሱም የክብር ባለቤት በሆነ በጌታችን ኃይል አሸነፈው ። ጽኑ በሆነ ተጋድሎም ኖረ ያለ ዕንባም ሰዓት አላለፈችውም በጥርሶቹም አልሳቀም በከንፈሮቹም ፈገግ አላለም ስጋውን ቅባት አልነካውም ስጋውንና ደሙን ከሚቀበልበት ጊዜ በቀር ፊቱንና እግሩን አልታጠበም ።
እናትና አባቱ በስድስት ዓመቷ ትተዋት የሞቱ እኅት ነበረችው ስሟም ማርያ ይባላል ዘመዶቿም ወደ አብርሃም አምጥተዋት ፈሪሀ እግዚአብሔር ሃያ ዓመት ሆናት ድረስ ትሕትናንም እያስተማራት በእርሱ ዘንድ አደገች።
ከዚህም በኋላ ሰይጣን ቀንቶባት ከአንድ መነኩሴ ጋር አፋቀራት ድንግልናዋንም አጠፉች ልብሷንና አስኬማዋን ለውጣ ወደ ሌላ አገር ሔደች።
አባ አብርሃምም በዚያች ሌሊት ታላቅ ከይሲ ርግቢቱን ሲውጣትና ጥቂት ቆይቶ ከእግሩ በታች ሲተፋት ራእይን አየ። በማግሥቱም ማርያ ከቦታዋ ታጣች አባ አብረሃምም ደነገጠ ወደ እግዚአብሔርም ከብዙ ዕንባ ጋር ጸለየ እርሷን ያገናኘው ዘንድ።
ከጥቂት ወራትም በኋላ እኅቱ ያለችበትን አባ አብርሃም ሰማ ሰዎችም እንዳያውቁት የምንኩስናውን ልብስ ለውጦ ፊቱንም ተከናንቦ የወታደር ልብስ ለብሶ በፈረስ ተቀምጦ ወዳአለችበት አገር ሔደ ከዚያም ደርሶ ማርያ ወዳለችበት ገባ የመሸተኛንም ልብስ ለብሳ በአያት ጊዜ እጅግ አዘነ ነገር ግን እንዳትሸሸው እንድታውቀው አልሆነም።
ከዚህም በኋላ ለሚያገለግላት አሽከር ከማርያ ጋር የሚደሰትበት መብልና መጠጥ እንዲያዘጋጅ የወርቅ ዲናር ሰጠው ለርካሽ ሥራ እንደሚፈልጓት ሰዎች ይመስላት ዘንድ።
ከራት በኋላም ወደ ውስጠኛው ቤት አስገባት በሩንም ዘጋ እጇንም ይዞ ራሱን ገለጠላት በአወቀችውም ጊዜ ደንግጣ እንደ በድን ሆነች ልጄ ሆይ አይዞሽ ከእግዚአብሔር በቀር ከኃጢአት ንጹሕ የሆነ የለም ነገር ግን ወደ ንስሐ ተመለሺ ወደቦታሽም ገብተሽ የቀድሞ ሥርዓትሽን ያዢ አላት እርሷም እሺ አለች።
በነጋም ጊዜም ወስዶ በፈረሱ አስቀመጣትና ደስ እያለው ተመለሰ እኅቱን ከሰይጣን እጅ ማርኳልና ወደቦታውም በደረሰ ጊዜ የቤቷን ደጅ ዘግቶላት ማቅ በመልበስ እየተጸጸተች የተጋድሎንም ሥራ እየተማረች በብርታቷና በተጋድሎዋ ያዩ ሁሉ እስቲአደንቁ ጸንታ ኖረች ።
እግዚአብሔርም በዚህ ቅዱስ ሰው እጆች ድንቆች ተአምራቶችን አደረገ አጋንንትን በማስወጣት በሽተኞችን በማዳን ከአንዲት ዓመትም በኋላ የማርያን ንስሓዋን አይቶ በሰባ ዘመኑ የተመሰገነ እግዚአብሔርን እያመሰገነ አረፈ።
ማርያ እኅቱም ከለቅሶ ጋር ትርኅምትን በማብዛት ቀንና ሌሊት እየተጋደለች ሌሎች አምስት ዓመታትን ኖረች ከዚያም በኋላ አረፈች ያዩዋትም በፊቷ ውስጥ ሰለአለው ብርሃን እግዚአብሔርን አመሰገኑ።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
ቅዱስ ዮሐንስ ጻድቅ
በዚህችም ቀን የከበረ ተጋዳይ ወታደር ዮሐንስ አረፈ። የዚህም ቅዱስ ወላጆቹ ክርስቲያኖች ናቸው እርሱም በከሀዲ በዑልያኖስ ሠራዊት ውስጥ ወታደር ሆነ። ንጉሡም ከባልንጀሮቹ ወታደሮች ጋራ ላከው የክርስቲያን ወገኖችንም በሚኖሩበት ቦታ ሁሉ እንዲአሠቃዩአቸው አዘዛቸው።
እርሱም ለባልንጀሮች ጭፍሮች ክርስቲያኖችን እጅግ እንደሚጠላቸውና እንደሚጣላቸው ይገልጽላቸዋል በጭልታም ገብቶ በጎ ነገርን የሚሹትን ሁሉ ይሰጣቸዋል ያጽናናቸዋልም። ሁል ጊዜም ይጸልያል ይጾማል ይመጸውታልም የቅዱሳንንም አኗኗር ኖረ ምስጉን እግዚአብሔርንም አገልግሎ በሰላም አረፈ።
ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን።
ነሐሴ 5 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት=
1.ቅዱስ አባ አብርሃም ገዳማዊ
2.ቅድስት ማርያ እህቱ
3.ቅዱስ ዮሐንስ ጻድቅ
4.አባ ፊልዾስ ዘደብረ ቢዘን
ወርሐዊ በዓላት
1.ቅዱስ ዼጥሮስ ሊቀ ሐዋርያት
2.ቅዱስ ዻውሎስ ብርሃነ ዓለም
3.አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ
4.ቅዱስ ዮሐኒ ኢትዮዽያዊ
5.ቅዱስ አሞኒ ዘናሒሶ
6.ቅድስት አውጋንያ (ሰማዕትና ጻድቅ)
ስንክሳር ዘወርኀ ነሐሴ

No comments:

Post a Comment

Post Bottom Ad

Pages