ከሰማይ ከወረደው በቀር - አትሮንስ ሚዲያ - Atrons Media

አትሮንስ ሚዲያ - Atrons Media

ስብኩ ወንጌለ ለኩሉ ፍጥረት ማቴ 16፤15


በቅርብ የተጻፉ

Post Top Ad

Wednesday, June 3, 2020

ከሰማይ ከወረደው በቀር


በዚህ ሳምንት ኦርቶዶክሳዊት ቤተክርስቲያናችን የጌታችንን ከሰማያት መውረድ ታስተምረናለች። ከሰማይ_ከወረደው_በቀር_ወደ_ሰማይ_የወጣ_ማንም_የለም_እርሱም_በሰማይ_የሚኖር_የሰው_ልጅ_ነው ዮሐ 3፥13 የሚለው ምንባብ ይነበባል። በዚህ ሳምንትም ይህ የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍል ስለሚተነተን ማብራርያውን መመልከት ተገቢ ነው። ስለ ጌታችንና አምላካችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ዕርገት ስንናገር በውሰጡ #ስለ_አምላክነቱ_ፈጣሪነቱ_እግዚአብሔርነቱ_ስለ_ምሥጢረ_ተዋሕዶም_ጭምር_ነው_የምንነጋገረው። እያንዳንዱን የመጽሐፍ ቅዱስ ቃል በሐዋርያትና በሊቃውንት መንፈስ ኾነው ለሚረዱ እውነተኛና ሐዋርያዊ ምእመናን የቅዱሳት መጻሕፍት ምሥጢር ተቀድቶ እንደ
ማያልቅ የውኃ ምንጭ ስለኾነ ነፍሳቸው በትርጓሜ ትረካለች። አንዲት ቅድስት
ቤተክርስቲያንን እውነተኛና ትክክለኛ ከሚያደርጓት ዐበይት ነገሮች ውስጥ
አንዱ በሐዋርትና በሊቃውንት ትርጓሜ ላይ መመሥረቷ ነው። የሐዋርያትን ትምህርት የማትቀበል ጉባዔ በምንም መልኩ ትክክል ልትኾን አትችልም፤
በዚህም መሠረታዊ ምክንያት በአንድ
የመጽሐፍ ቅዱስ ቃል ትርጓሜ ላይ ክርክር ሲነሣ ሐዋርትና ሊቃውንተ ቤተክርስቲያን ምን ብለው ተረጎሙት ብሎ መጠየቅ ቀዳማዊ ሊኾን
ይገባዋል። ነቢያትና ሐዋርያት የጻፉትን መጽሐፍ ቅዱስ ብለን የምንጠራውን እንቀበለዋለን። ይህ መጽሐፍ ልክ እንዳልታረደ በሬ ነውና የግድ ምግብ ኾኖ ለመበላት ሦስተኞቹን የቤተክርስቲያን አባቶችን ይፈልጋል፤እነርሱም ልክ እንደ አራጆችና ሠርተው እንደሚያበሉ ሰዎች ናቸው። እንግዲህ አንድ ሰው ነቢያትንና ሐዋርያትን እቀበላለሁ ብሎ በእነርሱ የተጻፉትን ቅዱሳት መጻሕፍት ባያጣጥምና ባይመገባቸው እቀበላለሁ ማለቱ ስለምንድነው? በእርግጥ በሬ ሳይታረድ ሊበላ የሚችለው ለጅቦች እንጂ ለሰዎች እንዳይደለ የታወቀ የተረዳም ነገር ነው። ማንም ሰው ቢኾን እኔ ክርስቲያን ነኝ ካለ በነቢያት ትንቢት በሐዋርያት ስብከትና በሊቃውንት ትርጓሜ ማመን ግድ ይለዋል። ካልኾነ በጉን ይዞ አርዶ መብላት ባለመቻሉ ብቻ ሳይጠቀምበት ያልፋልና። እስኪ አኹን ያነሳነውን የመጽሐፍ ቅዱስ ቃል በዚህ መንፈስ እንመርምረው፦
👉 ከሰማይ ከወረደ በቀር ወደ ሰማይ የወጣ ማንም የለም ሲል #አንደኛ_ከሰማይ_የወረደ_ሰማያዊ_የኾነ_ደግሞም_ወደ_ሰማይ_የወጣ_ማንም_የለም_ማለት_ነው። ሰማይ ያለው በወል ስም ነው እንጂ ከአንደኛው ሰማይ ሲል አይደልም፤ ከአርያም የወረደ ወደ አርያምም የወጣ ማንም የለም ሲል ነው እንጂ። ቅዱሳን ሲጀመር ከሰማይ የመጡ አይደሉም በመኾኑም ከሰማይ ከወረደ የሚለው እነርሱን የማይመለከት መኾኑን ከተረዳን የሄኖክ፣ የኤልያስ፣ የዕዝራእና የሌሎችም ቅዱሳን ዕርገት። ከዚኛው ጋር አንድ እንዳልኾነ ግልጽና የተረዳ ነው። እነርሱ ከምድር ዐርገው ወደ ብሔረ ብፁዐን የሔዱ እንጂ ጥንቱን ከሰማይ የወረዱ አይደሉምና ለእነርሱ በመጽሐፍ ቅዱስ ላይ ከተገለጸው ጋር ፈጽሞ አይጋጭም። እንዲያውም ታላቁ ሊቅ ቅዱስ ጎርጎርዮስ ኤልያስ በእሳት ሰረገላ ተወሰደ፤ ሄኖክን እግዚአብሔር ወሰደው። ለእነዚህ ለኹለቱ ረዳት አስፈልጓቸዋል፤ ጌታችን ግን በራሱ ሥልጣን ምንም ረዳት ሳይሻ ነው ያረገው ይልና እነዚህ ኹለቱ ቅዱሳን የክርስቶስን ዕርገት በምሳሌነት የሚያሳዩ ናቸው፤ ሄኖክ ከሕገ ኦሪት በፊት ላሉት፤ ኤልያስ ደግሞ በሕገ ኦሪት ላሉት የክርስቶስን ሥጋዌና የተዋሐደውን ሥጋ ይዞ ማረግ የሚያመለክቱ ናቸው በማለት ወደተለየና ድንቅ ወደ ኾነ ምሥጢር ይስበናል።
❖ ❖ ❖  ❖ ❖ ❖
👉 #ኹለተኛ ከሰማይ ከወረደ በቀር ወደ ሰማይ የወጣ ማንም የለም ሲል ወረደ የሚለው ሥጋዌውን የሚያስረዳ ነው፤ ለእግዚአብሔር መውጣት መውረድ የለበትምና። ኢየሱስ ክርስቶስ
እግዚአብሔር መኾኑ በብዙ የመጽሐፍ ቅዱስ ጥቅስ ውስጥ የሚገኝ እውነታ ነው። ዮሐ 1፥1 የሐዋ 20፥ 28፤ ፊል 2፥7። ወጣ የሚለው ደግሞ የተዋሐውን ሥጋ አሣረገ ማለት ነው። ቅዱስ ጳውሎስ ባለጸጋው እኛ በእርሱ ድህነት ባለጸጋ እንኾን ዘንድ ደሀ ኾነ በማለት እንደተናገረ፤ ዝቅ ብሎ እኛን ከፍ አደረገን ማለት ነው። በመጽሐፍ የእግዚአብሔር ቀኝ ከፍ ከፍ አደረገችኝ እንደተባለ የእኛን መዋረድ ዐይቶ ሰው ኾኖ ሥጋ ማርያምን ተዋሕዶ ተዋርደን የነበርነውን ከፍ አደረገን ማለት ነው። በትሕትናው ልዕልናን ሰጠን ሲል ነው።
❖ ❖ ❖  ❖ ❖ ❖
#ሦስተኛ አይሁዳዊያን ሊቀ ነቢያት ቅዱስ ሙሴ ወደሰማይ ዐርጎ ዓሥርቱን ትዕዛዛት ይዞ መጣ ብለው ያምኑ ስለነበር #ከሰማይ_የወረድኩት_እኔ_ነኝ_እንጂ_ሌላ_ማንም_አይደለም_ብሎ_የአይሁድን_የተሳሳተ_እምነት_በመምህራቸው_በኒቆዲሞስ_በኩል_ለመግለጥ_ስለፈለገ ከሰማይ ከወረደ በቀር ወደሰማይ የወጣ ማንም የለም አለ። ከእንግዲህ ወዲህ ሙሴ ወደ ሰማይ ዐርጎ ነው ትዕዛዛትን ይዞ የመጣው አትበሉ ከሰማይ የመጣሁት እኔ ነኝ ሙሴ ወደ ሰማይ ሔዶ አልመጣም ሲል ነው።
❖ ❖ ❖  ❖ ❖ ❖
#አራተኛ_ምሥጢረ_ተዋሕዶን_ሲያስረዳ_ነው። ከማይ ከወረደው በቀር ወደሰማይ የወጣ ማንም የለም ርሱም በሰማይ የሚኖር የሰው ልጅ ነው ይላል። ይህንን ንግግር ሲናገር ጌታችን በሥጋው
በምድር ነው የነበረው ኾኖም ግን በሰማይ የሚኖር የሰው ልጅ አለ በማለት ገለጸ፤ #ለምን_ቢባል_እግዚአብሔር_በኹሉም_ቦታ_ስላለ_ያን_በኹሉ_ቦታ_መኖርን_በተዋሐድኩት_ሥጋ_ገንዘብ_አድርጌዋለሁኝ። ሥጋ ከመለኮት ጋር ሲዋሐድ አንዱ የአንዱን ገንዘብ ገንዘብ ስለሚያደርግ፤ ምንም እንኳ ሥጋ ውስን ቢኾንም በምሥጢረ ተዋሕዶ ምሉእ በኩለሄ የኾነውን የእግዚአብሔርን የባሕርይ መገለጫ ገንዘብ አድርጌዋለሁ ሲል ነው። ለዚህ ነው ቅዱስ ጳውሎስ "ይህ የወረደው ኹሉን ይሞላ ዘንድ ከሰማያት ኹሉ በላይ የወጣው ደግሞ ያው ነው "ኤፌ 4፥10 ያለው። የወረደውና የወጣው በተዋሕዶ አንድ ኾነዋል ሲልነው። ወዴት እንደወጣም ሲናገር ከሰማያት ኹሉ በላይ ነው የሚለው ይህም የሚያስረዳው አምለክነቱን ነው
ከሰማያት ኹሉ በላይ ያለው አምላክ ነውና። ለዚህ ነው ቅዱስ ቄርሎስ ጌታችንን መድኃኒታችንን የሚከፍለው ኹለት አካል ኹለት ባሕርይ የሚለው
ከአብ የተወለደው ወልድ ወደ ሰማይ ካረገው ልዩ እንደኾነ ወደ ሰማይ ያረገው ሰው ከአብ ከተወለደው ልዩ እንደኾነ የሚናገር አንድ አካል አንድ ባሕርይ እንደኾነ የማያምን የተወገዘ የተለየ ይኹን" ያለው ድር.ቄር ገጽ 265።

መ/ር ቀለመ ወርቅ ደሳለኝ 

No comments:

Post a Comment

Post Bottom Ad

Pages