ስንክሳር_ዘወርኀ_የካቲት 8 - አትሮንስ ሚዲያ - Atrons Media

አትሮንስ ሚዲያ - Atrons Media

ስብኩ ወንጌለ ለኩሉ ፍጥረት ማቴ 16፤15


በቅርብ የተጻፉ

Post Top Ad

Friday, March 3, 2023

ስንክሳር_ዘወርኀ_የካቲት 8

 አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም

የካቲት ስምንት በዚህች ዕለት #ጌታችን_ኢየሱስ_ክርስቶስ ከከበረ ልደቱ ከአርባ ቀኖች በኋላ ወደቤተ መቅደስ የገባበት ሆነ፣ የከበረች እመቤት #አመተ_ክርስቶስ አረፈች፣ ከአሴር ወገን የሆነች የፋኑኤል ልጅ #ነቢዪት_ሐና አረፈች፣ በትሩፋቱ ፍጹም የሆነ ታላቅ አረጋዊ የገዳመ ሲሐቱ #ቅዱስ_ኤልያስ አረፈ።


የካቲት ስምንት በዚህች ዕለት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከከበረ ልደቱ ከአርባ ቀኖች በኋላ ወደቤተ መቅደስ የገባበት ሆነ።
ለዚህ ምሥጢር አገልጋይ የሆነ ጻድቁ ዮሴፍና የወለደችው እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም የክብር ባለቤት እርሱ በእስራኤል ሕዝብ ላይ የሠራውን ሕግ ይፈጽሙ ዘንድ መሥዋዕትም ሊአቀርቡ መጡ። ጻድቅ ሰው ስሞዖን ካህንም ሕፃኑን ተቀብሎ አቀፈው።
እንዲህም ሆነ አባታችን አዳም ከተፈጠረ በአምስት ሽህ ሁለት መቶ ዓመት አሸናፊ የተባለ በጥሊሞስ በነገሠ ጊዜ የአይሁድ ወገኖች ከሥልጣኑ በታች ነበሩ። ወደ ኢየሩሳሌምም ልኮ ከሊቃውንቶቻቸው፡ ከአዋቂዎች መምህራኖቻቸው ሰብዓ ሰዎችን መርጦ ወደርሱ ወሰዳቸው የኦሪትንም መጻሕፍት ከዕብራይስጥ ቋንቋ ወደ ጽርዕ ቋንቋ የተረጕሙ ዘንድ አዘዛቸው። ይህም የሆነ በእግዚአብሔር ፈቃድ ነው ከአይሁድ ሕጉና ሥርዓቱ እንደሚፈልስና በዓለም ሁሉ ላሉ ለክርስቲያን ወገን ይሆን ዘንድ አለውና።
ዳግመኛም ሁለት ሁለት እያደረጉ እንዲለዩአቸው አዘዘ እነርሱ ሰባ ሁለት ስለሆኑ ሠላሳ ስድስት ድንኳን አዘጋጅቶ በዚያ ሁለት ሁለቱን አኖራቸው ተገናኝተው በመስማማት የሚጽፉትን የሕጉን ቃል እንዳይለውጡ በላያቸው ጠባቂዎችን አኖረ። እነርሱ በተንኰል ሥራ የታወቁ ናቸውና።
ለዚህም ለስሞዖን ይተረጒም ዘንድ የነቢዩ ኢሳይያስ መጽሐፍ ደረሰውና እነሆ ድንግል ትፀንሳለች ወንድ ልጅንም ትወልዳለች ስሙንም ዐማኑኤል ትለዋለች ከሚለው ደረሰ። ይህንንም ቃል ይጽፍ ዘንድ ፈራ ይህ እንዴት ይሆናል ብሎ ንጉሥ እንደሚዘብትበት ቃሉንም እንደማይቀበለው አስቧልና እርሱ ራሱም እንዴት ሊሆን ይችላል ብሎ ተጠራጠረ። ይህንንም ሲያስብ እንቅልፍ መጣበትና አንቀላፋ የእግዚአብሔርም መልአክ ተገልጦ የተጠራጠርከውን ከድንግል የሚወለደውን እስከምታየውና እስከምትታቀፈው ሞትን አትቀምስም አለው ከዚህም በኋላ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እስከተወለደና በዚች ዕለት ወደ ቤተ መቅደስ እስከ አስገቡት ድረስ ስምዖን ሦስት መቶ ዓመት ኖረ ሕፃኑን ጌታችንንም በታቀፈው ጊዜ ታውረው የነበሩ ዓይኖቹ ተገለጡ ሁለመናውም ሐዲስ ሆነ መንፈስ ቅዱስም የምትጠብቀው የነበረ ሕፃን ይህ ነው ብሎ ነግሮታልና።
እግዚአብሔርንም አመሰገነው። እንዲህም አለ ባርያህን በሰላም አሰናብተው በአንተ ምክንያት በዚህ በኃላፊው ዓለም ሕይወት ታሥሬ ኑሬአለሁና እነሆ አሁን መጥተህ አየሁህ ወደ ዘላለም ሕይወት እሔድ ዘንድ አሰናብተኝ ዓይኖቼ ትድግናህን አይተዋልና። በወገኖችህ ሁሉ ፊት ያዘጋጀኸውን ለአሕዛብ ብርሃንን ለወገኖችህ እስራኤልም ክብርን ትገልጥ ዘንድ።
እመቤታችንን እናቱ ድንግል ማርያምንም እንዲህ አላት ይህ ልጅሽ ከእስራኤል ውስጥ ለብዙዎች ለመውደቃቸውና ለመነሣታቸው በሚፈረድባቸውም ገንዘብ ለምልክት የተዘጋጀ ነው።
ዳግመኛም በመከራው ጊዜ በልቧ የሚያድርባትን ኅዘን አስረዳት እንዲህም አላት በአንቺ ግን በልብሽ የሚከፋፍል ፍላፃ ይገባል ከዚህም በኋላ በሰላም አረፈ። በዚያም የከበረ ወንጌል ያወሳት የፋኑኤል ልጅ ነቢዪት ሐና ነበረች እርሷም ስለርሱ ትንቢት ተናገረች እግዚአብሔርን እያመሰገነች እርሱ ከሰይጣን ባርነት የሚያድናቸው መድኃኒት እንደሆነ ነገረቻቸው።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
በዚህም ዕለት ከአሴር ወገን የሆነች የፋኑኤል ልጅ ነቢዪት ሐና አረፈች፡፡ የእርሷም ዘመኗ አልፎ ነበር በድንግልና ከኖረች በኋላ ከባሏ ጋር ሰባት ዓመት ኖረች። ሰማንያ አራት ዓመት ፈት ሁና ኖረች በጾምና በጸሎትም እያገለገለች ቀንም ሌትም ከምኲራብ አትወጣም ነበር።
ጌታችን ኢየሱስን ከተወለደ በኋላ በአርባ ቀን ወደ ቤተ መቅደስ በአስገቡት ጊዜ በዚያን ሰዓት ተነሥታ አመነች እግዚአብሔርንም አመሰገነችው። የኢየሩሳሌምን ድኅነት ተስፋ ለሚያደርጉ ሁሉ ስለርሱ ነገረች። ከዚህም በኋላ በሰላም አረፈች።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
በዚህችም ቀን የከበረች እመቤት አመተ ክርስቶስ አረፈች ሁለቱም አገልጋዮቿ። ይችም ቅድስት ከቍስጥንጥንያ አገር ሰዎች ውስጥ ናት ከንጉሥ መሳፍንቶችም ባል ነበራት እርሱም በጐልማሳነቱ ሙቶ ዕድሜዋ ዐሥራ ሁለት ዓመት ሲሆናት ፈት አረጋት።
ከጥቂትም ቀን በኋላ ከመንግሥት ታላላቆች ከሆኑት ውስጥ አንድ ሰው በኃይል ወስዶ ሊአገባት ፈለገ እርሷም ጽኑ ደዌ አለብኝ እስከምድን ጠብቀኝ አለችውና ከዚህ በኋላ ገንዘቧን ሁሉ ለድኆችና ለችግረኞች በተነች ወንዶችና ሴቶች ባሮቿን ነጻ አወጣች ሁለት ሴቶች ባሮቿንም ከእርሷ ጋር ይዛ ማንም ሳያያት በሌሊት ወጣች ከኰረብታ በታች ጥልቅ ከሆነ ቦታ ውስጥ ወዳለ ዋሻ ገብታ በዚያ ዐሥራ አንድ ዓመት ኖረች በየዕለቱም ከዕፀዋት ፍሬ አዕዋፍ እያመጡላት ከአገልጋዮቿ ጋር ትመገባለች።
ከዚህም በኋላ በንጉሥ ቈስጠንጢኖስ ዘመን ከጸሐፊዎች አንዱ እንዲህ አለ ግብር እሰበስብ ዘንድ ወደ ምሥራቅ አቅጣጫ ሔድኩ ወደ አንድ ገዳምም ደረስኩ መነኰሳቱና አበ ምኔቱም ተቀበሉኝ እርስበርሳችንም እጅ ተነሣሥተን ተቀመጥን ከዚያ በየአይነቱ ፍሬ ያላቸው ዛፎች አሉ አዕዋፍም ቅርንጫፉን ከፍሬው ጋር እየቆረጡ ይበራሉ እነርሱ ራሳቸው አይበሉም።
እኔም አይቼ አደነቅሁ መነኰሳቱንም ይህ ሥራ ምንድን ነው አልኳቸው እነርሱም እንዲህ ሲያደርጉ ዐሥራ አንድ ዓመት ነው የሚሆነውን ግን አናውቅም አሉኝ እኔስ በተራራ ውስጥ ለሚኖር መነኰሳት የሚወስዱ ይመስለኛል አልኳቸው።
ይህንንም ስናገር ቊራ መጥቶ ቅርንጫፍን ቆርጦ ከፍሬው ጋር ይዞ በረረ ሥራውን አውቅ ዘንድ ከአበ ምኔቱ ጋር ተከተልኩት የሚገባበትንም አየን ወደዚያም ቦታ ደርሰን ደንጋይ ጣልን ክርስቲያኖች ከሆናችሁ አትግደሉን የሚል ቃልን ሰማን እናንተ ከወዴት ናችሁ አልናቸው እኛን ለማየት ከፈለጋችሁ ራቁታችንን ስለሆን ሦስት ልብሶችን ጣሉልን አሉን እኛም ልብሶችን ጣልንላቸውና ወደርሳቸው ጭንቅ በሆነች መንገድ ወረድን በደረስንም ጊዜ ተቀበሉን እርስበርሳችንም እጅ ተነሣሥተን አንዲቱ ከእኛ ጋር ተቀመጠች ሁለቱ ግን በፊቷ ቆሙ።
አበ ምኔቱም እናቴና እመቤቴ ሆይ ከወዴት ነሽ ወደዚህስ አወጣጥሽ እንዴት ነው አላት እርሷም ሥራዋን ሁሉ ከመጀመሪያው እስከ መጨረሻው ነገረችው አበ ምኔቱም የምትፈቅጂ ከሆነ ከገዳም ምግብ እናምጣላችሁና ከእናንተ ጋር በአንድነት እንመገብ አላት። እርሷም ወደዚህ ከመጣን ቅዱስ ቁርባንን አልተቀበልንምና የክርስቶስን ሥጋና ደም አምጥቶ እንዲአቀብለን ቄስን እዘዝልን አለችው።
አበ ምኔቱም ቄስን አዘዘላቸውና አቈረባቸው በማግሥቱም አመተ ክርስቶስ ረጅም ጸሎትን ጸለየችና አረፈች አገልጋዮቿም ተከታትለው አረፉ በዝማሬና በማኅሌት ገንዘው በክብር ቀበሩአቸው።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
በዚህች ዕለት በትሩፋቱ ፍጹም የሆነ ታላቅ አረጋዊ የገዳመ ሲሐቱ ኤልያስ አረፈ። የሚያረጋጋው በትሩፋቱ ፍጹም የሆነ አረጋዊ መነኵሴ እንዲልኩለት በመለመን ጻድቁ ንጉሥ ቴዎዶስዮስ ወደ ገዳመ ሲሐት በላከ ጊዜ ይህን በትሩፋቱ ፍጹም የሆነ ኤልያስን ላኩለት ስለርሱም እንዲህ ብለው ጻፉ "ንጉሥ ሆይ እነሆ በሥራው ኤልያስን የሚመስል ኤልያስ የሚባል ጻድቅ ሰው ልከንልሃል።"
ወደ ንጉሥም በደረሰ ጊዜ ንጉሥ እንዲህ አለው አንተ በገድልህ ነቢይ ኤልያስን እንደምትመስል መነኰሳቱ ስለአንተ ወደእኔ ልከዋል። አረጋዊውም በየውሀትና በትሕትና እንዲህ አለ ፦ "ጻድቅ ንጉሥ ሆይ ይቅርታ አድርግልኝ ሰው ሁሉ በጠባዩና በሥራው ይታወቃል የኤልያስም ገድሉ እንዲህ ነው ስለ ደግነቱ ምግቡን ቊራዎች ያመጡለት ነበር እኔ ግን ምግቤን በፀሐይ ውስጥ ባሰጣው ቊራ ይዞት ይሔዳል" ንጉሡም ሰምቶ ከቃሉ ጣዕም የተነሣ አደነቀ።
ዳግመኛም አባቴ ሆይ ለምን እግዚአብሔር ልጅ አልሰጠኝም አለው አረጋዊውም በምድር ላይ ሃይማኖት የሚከፋፈልበት ዘመን ይመጣል ከመናፍቃን ጋር አንድ እንዳይሆን ስለዚህ እግዚአብሔር ልጅን አልሰጠህም አለው።
ንጉሡም ብዙ ገንዘብን ሊሰጠው ወደደ እርሱ ግን አልተቀበለም። ወደ በአቱም እስከተመለሰ ድረስ እህል እንዳልቀመሰ ስለርሱ ተነገረ በሰላምም አረፈ።
ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በከበሩ ቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።

No comments:

Post a Comment

Post Bottom Ad

Pages