ስንክሳር_ዘወርኀ_ጥቅምት 7 - አትሮንስ ሚዲያ - Atrons Media

አትሮንስ ሚዲያ - Atrons Media

ስብኩ ወንጌለ ለኩሉ ፍጥረት ማቴ 16፤15


በቅርብ የተጻፉ

Post Top Ad

Sunday, October 16, 2022

ስንክሳር_ዘወርኀ_ጥቅምት 7

 
 እንኩዋን #ለታላቁ_ገዳማዊ_ቅዱስ_አባ_ባውላ ዓመታዊ የዕረፍት በዓል በሰላም አደረሳችሁ
 በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ ፡፡ አሜን ፡፡ 
 
አባ ባውላ መስተጋድል
 
ቅዱሱን የመሰሉ አባቶች "መስተጋድላን" ይባላሉ በግዕዙ:: ለሃይማኖታቸው እስከ ደም ጠብታና እስከ መጨረሻዋ ህቅታ ድረስ መጋደላቸውን የሚያሳይ ነው:: መጋደል ጐዳናው ብዙ ዓይነት ነው::
 
ከራሱ ጋር የሚጋደል አለ:: ከዓለም ጋር የሚጋደልም አለ:: የቅዱሳኑ ተጋድሎ ግን በዋነኝነት ከ2 አካላት ጋር ነው:: በመጀመሪያ ፍትወታት እኩያትን (ኃጣውዕን) ከሚያመጡ አጋንንት ጋር ሲሆን ሁለተኛው ደግሞ "ሃይማኖቸታችሁን ካዱ: ለጣዖትም ስገዱ" ከሚሉ ከሃድያን ጋር የሚደረግ ትግል ነው::
 
+በተለይ 2ኛው እስከ ሞት የሚያደርስ ውሳኔን ይጠይቃል:: ታላቁ አባ ባውላ ገዳማዊ ጻድቅ እንደ መሆኑ ትግሉ የነበረው ከአጋንንት ጋር ነው:: የዚህን ቅዱስ ሕይወት ለመረዳት ግን አንድ ነገርን ልብ እንድትሉልኝ እፈልጋለሁ::
 
+ያለንበት ዘመን ክርስትና በራድ (ቀዝቃዛ) በመሆኑ የቀደሙ አባቶች የጸና ተጋድሎ አንዳንዴ ግራ ሲያጋባን ተመልክቻለሁ:: ቅዱሳኑ ሁሌም አንድ ነገርን እያሰቡ ይኖራሉ:: ይኼውም በዘመኑ በርካቶቻችን የረሳነው: ወይም ማስታወስ የማንፈልገው ነገር ይመስላል::
 
+ሰማያዊው አምላክ ከዙፋኑ ወርዶ በተዋሐደው ሥጋ በቃል ሊገለጽ የማይችል መከራን ስለ እኛ ተቀብሏል:: ክርስትና ማለት ቀራንዮን በልብ ውስጥ መሳል ነው:: ፍቅረ መስቀሉን: የጌታንም ውለታ የሚያስብ ማንኛውም ሰው: የትኛውም ዓይነት መከራ ቢመጣበት አይታወክም::
 
+ቅዱሳኑም የፍቅራቸውና የትእግስታቸው ምሥጢር ይኼው ነው:: ጌታ "የሚወደኝ ቢኖር የሞቱን መስቀል ተሸክሞ ይከተለኝ" (ማቴ. 16:24) እንዳለው: ቅዱሳኑ ይህንን ቃል በቃል ሲፈጽሙት እነሆ እንመለከታለን::
 
+ታላቁ አባ ባውላ የተወለደው በላይኛው ግብጽ አካባቢ ሲሆን ዘመኑም 4ኛው መቶ ክ/ዘመን ነው:: ከክርስቲያን ወላጆቹ መንፈሳዊ ነገሮችን ተምሮ በወጣትነቱ መንኗል:: ያ ዘመን እልፍ አእላፍ ቅዱሳን የነበሩበት ነውና ወደ ጠመው አካባቢ ሔዶ ምናኔን ተምሯል::
 
+ሥርዓተ ገዳምን ማለትም:- አገልግሎትን: ፍቅርን: ተጋድሎንና የመሳሰሉትን ከተማረ በሁዋላም ደቀ መዝሙሩን አባ ሕዝቅኤልን አስከትሎ ለዋናው የተጋድሎ ሕይወት ወደ በርሃ ወጣ:: አባ ባውላ ዘወትር በፍቅረ ክርስቶስ ይመሰጥ ነበርና የተጋድሎ ምርጫው ልዩ ሆነ::
 
+አንድ ቀንም እንዲህ ሲል አሰበ:- "ጌታ ሆይ! አንተ ለእኛ ለኃጥአን ኃፍረተ መስቀልን ታግሠህ: ሞትን ከሞትክልን እኛ ደግሞ ስለ ንጹሑ አምላክ ስንል እልፍ ሞትን መታገስ አለብን::"
 
+ይህንን ብሎ ከወትሮው በተለየ መንገድ ሊጋደል ጀመረ:: በዚህ እጅግ የጸና ተጋድሎው ምክንያትም 7 ጊዜ ሙቶ 7 ጊዜ ተነሳ::
 
1.እግሩን ከረዥም ዛፍ ላይ አስሮ: ወደ ታች ተዘቅዝቆ ይጸልይ ጀመረ:: እህልም: እንቅልፍም: ዕረፍትም አልነበረውምና ደሙ በአፍ: በአፍንጫው ፈሶ አለቀ:: እንዲህ በሆነ በ40ኛው ቀንም ሞተ:: መልአከ እግዚአብሔር መጥቶ ከሞት አስነሳው::
 
2.ጥልቅ ባሕር ውስጥ ሰጥሞ እንዳስለመደ ይጸልይ ጀመረ:: ከባሕሩ ሳይወጣ: ከቆመ ሳያርፍ: ከዘረጋም ሳያጥፍ ለ40 ቀናት ጸለየ:: በዚያው ሳለም ለ2ኛ ጊዜ ሞተ:: ቅዱስ መልአክ መጥቶ ከሞት አስነሳው::
 
3.እርሱ በሚኖርበት ጠመው አካባቢ ረዥም ተራራ ነበርና ወደዚያ ወጣ:: ከተራራው ጫፍ ሆኖ ወደ ታች ተመለከተ:: የተጠራረቡ ድንጋዮች በየመንገዱ ተሰልፈው ነበር:: በዚያች ቅጽበት የጌታ ኅማማት ከፊቱ ቢደቀንበት ከላይ ወደ ታች ተወርውሮ ሔደ:: በየመንገዱ ያሉት ጥርብ ድንጋዮች ቢቀበሉት አካሉ እየተነተፈና እየተቆራረጠ በየመንገዱ ቀረ:: በዚህም ሞተ:: አሁንም ፈጣሪው ከሞት አስነሳው::
 
4.አንድ ቀን ደግሞ (ዕለቱ ዓርብ ነበር) የጌታን ኅማማት እያሰበ የሚያደርገው ጠፋው:: ከቆመበት አካባቢ ትልቅ ዛፍ ነበርና ወደዚያ ወጥቶ ሲመለከት ከመሬት ላይ የተነጠፈ ትልቅ ድንጋይ አየ:: ከላይ ወደ ታች ሲወድቅና ድንጋዩ ላይ ሲያርፍ ለሁለት ተከፍሎ ሞተ:: አሁንም በፈጣሪ ትዕዛዝ ተነሳ::
 
5.በሌላ ቀን ደግሞ በዕለተ ዓርብ ጭንቅላቱን ከእግሩ ጋር አሥሮ ይጸልይ ገባ:: ያለ ምንም እህል: ውሃና እንቅልፍ ለ40 ቀናት ቆይቶ ሞተ:: እንደገናም ተነሳ::
6.እጅግ ሊመለከቱት እንኩዋ በሚከብድ የጉድጉዋድ ውሃ ውስጥ ገብቶ ለ40 ቀናት እጆቹን ዘርግቶ ቢጸልይ ከጭንቁ ብዛት ነፍሱ ከሥጋው ተለየች::
 
7.አንድ ቀንም እንደዚሁ የጌታን ሕማማት እያሰበ ወደ ጽኑ ቆላ ወረደ:: በአካባቢው ከአሸዋ በቀር ምንም አልነበረምና ቆሞ ሲጸልይ አሸዋው ውጦ ደፈነውና ለ7ኛ ጊዜ ሞተ:: በዚህ ጊዜ ግን ሊያስነሳው የመጣው እንደ ወትሮው ቅዱስ መልአክ ሳይሆን ራሱ የክብር ባለቤት መድኃኒታችን ክርስቶስ ነበር::
 
+ጌታችን አባ ባውላን ከሞተበት አስነስቶ:- "ወዳጄ ባውላ! ስለ እኔ ፍቅር እጅግ ተሰቃየህ" አለው:: ቅዱሱ ግን "ጌታየ ሆይ! የእኔ መከራ በአንተ መከራ ሲታሰብ ኢምንት ነውና እባክህ ስለ ስምህ ሌሎች መከራዎችን እንድቀበል ፍቀድልኝ? ገና ሕማምህን አስቤ አልረካሁምና" አለው::
 
+ጌታ ግን "የለም! መከራው ይበቃሃል:: መጥቼ እስክወስድህ ድረስ ከአባ ብሶይ ጋር ቆይ" ብሎት: ባርኮት ዐረገ:: አባ ባውላም እንደ ታዘዘው በአባ ብሶይ ገዳም ከቅዱስ ብሶይ ጋር ቆይቶ በዚህች ቀን ዐርፏል::
 
+ይህቺውም ዕረፍቱ ለ8ኛ ጊዜ ሆና ተቆጥራለች:: የቅዱሱን ዜና የጻፈው ደቀ መዝሙሩ አባ ሕዝቅኤል ሲሆን ያሰፈረው እንባው እንደ ዥረት እየወረደ ነው:: አባቶቻችን ሊቃውንትስ ታላቁን ጻድቅ ሲያመሰግኑት እንዲህ አይደለምን!
 
"ውስተ ገድል ጽኑዕ ዘአልቦ ምምዐ:
ወደቀ ስብአ: ወተንሳእከ ስብአ::"
 
አምላከ አባ ባውላ በጻድቁ ላይ ያሳደረውን ፍቅሩን ያሳድርብን:: ከበረከቱም ያድለን::
 
ጥቅምት 7 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት
1.አባ ባውላ መስተጋድል
2.አባ ሕዝቅኤል ጻድቅ
3.ቅዱስ ሚናስ ሰማዕት
4.ቅዱስ ሐናሲ ሰማዕት
 
ወርሐዊ በዓላት
1.ሥሉስ ቅዱስ (አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ)
2.አባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ
3.አባ ሲኖዳ (የባሕታውያን አለቃ)
4.አባ ዳንኤል ዘገዳመ ሲሐት
5.አባ ባውላ ገዳማዊ
6.ቅዱስ አትናቴዎስ ሐዋርያዊ
7.ቅዱስ አግናጥዮስ (ለአንበሳ የተሰጠ)
 
 እኔን መከተል የሚወድ ቢኖር ራሱን ይካድ:: መስቀሉንም ተሸክሞ ይከተለኝ:: ነፍሱን ሊያድን የሚወድ ሁሉ ያጠፋታል:: ስለ እኔ ግን ነፍሱን የሚያጠፋ ሁሉ ያገኛታል:: ሰው ዓለሙን ሁሉ ቢያተርፍ: ነፍሱንም ቢያጐድል ምን ይጠቅመዋል? ወይስ ሰው ስለ ነፍሱ ቤዛ ምን ይሰጣል?  (ማቴ. 16:24)
 
 ወስብሐት ለእግዚአብሔር

No comments:

Post a Comment

Post Bottom Ad

Pages