አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም
እነሆ መላው ምስክርነታቸው ከመንፈሳዊ አባታቸው አባ ሜልዮስ ጋራ በዚሁ ወር በሃያ ስምንት ቀን እንዲህ ተጽፎ ይገኛል።
ቅዱስ ሜልዮስ ሰማዕት ኮራሳት በምትባል አገር በተራራ ባሉ ዋሻዎች ከሁለት አርድእት ጋር ይኖር ነበር፡፡ እርሱም በተጋድሎ ሕይወቱ እጅግ የተመሰገነ ነው፡፡ እግዚአብሔርም በአባ ሜልዮስ እጅ ብዙ አስገራሚ ተአምራትን አደረገ፡፡ ከዕለታትም በአንደኛው ቀን በመንገድ ሲሄድ የሞተ ሰው አገኘ፡፡ የአገሪቱ ሰዎችም አንዱን መነኮስ ‹‹የገደልከው አንተ ነህ›› ብለው ይዘው አስጨነቁት፡፡ የከበረ አባ ሜልዮስም ወደ ጌታችን ከጸለየ በኋላ ሬሳውን ‹‹በውኑ የገደለህ ይኽ መነኩሴ ነውንመንፈስ?›› አለው፡፡ የሞተውም ሰው አፈፍ ብሎ ተነሥቶ ‹‹እርሱስ አልገደለኝም ነገር ግን ብዙ ገንዘቤን ከአንድ ቄስ ዘንድ አደራ አስጠበቅሁ፣ ስለዚህም ገደለኝ፣ ከዚህም ጣለኝ›› ብሎ መሰከረ፡፡ ዳግመኛም አባ ሜልዮስን ‹‹ወደዚያ ቄስ ዘንድ ሄደህ ገንዘቤን ተቀብለህ ለልጆቼ ስጥልኝ›› ብሎ ለመነው፡፡ አባ ሜልዮስም ‹‹እስከትንሣኤ ቀን በሰላም አርፈህ ተኛ›› ብሎት ተመልሶ ዐረፈ፡፡
የኮራት አገር ንጉሥ ሁለቱ ልጆች ሠራዊቶቻቸውን ይዘው ለአደን ወደ ተራራው ቢወጡ የከበረ ቅዱስ አባ ሜልዮስን ማቅ ለብሶ ጠጉሩም የረዘመ ሆኖ አገኙት፡፡ የንጉሡ ልጆችም አባ ሜልዮስን ባዩት ጊዜ ፈርተውት ‹‹ሰው ነህን ወይስ መንፈስ?›› ብለው ጠየቁት፡፡ እርሱም ‹‹በዚህ ተራራ ውስጥ የምኖር ለጌታዬ ለኢየሱስ ክርስቶስ የምሰግድ ሰው ነኝ›› አላቸው፡፡ እነርሱም ይህን ሲናገር ሰምተው ‹‹ከእሳትና ከፀሐይ በቀር አምላክ የለም፣ እንዳንገድልህ ሠዋላቸው›› አሉት፡፡ አባ ሜልዮስም የሰው ፍጥረት ሁሉ እሳትንና ፀሐይን ለፈጠረ አምላክ ብቻ መገዛት እንዳለት ነገራቸው፡፡ የንጉሡ ልጆችም አባ ሜልዮስን ከሁለቱ አርድእቱ ከአባ ኢያሱና ከአባ ዮሴፍ ጋር ይዘው ጽኑ ሥቃይ አሠቃዩአቸው፡፡ ከብዙ አሠቃቂ ሥቃይም በኃላ በዚህ ወር በ13ኛው ቀን የሁለቱን አርድእት አንገታቸውን በሰይፍ ቆረጧቸውና የሰማዕትነታቸው ፍጻሜ ሆነ፡፡
አረጋዊ ቅዱስ አባ ሜልዮስን ግን ለ15 ቀናት ሲያሠቃዩት ኖሩ፡፡ ከዚህም በኋላ ከመካከላቸው አቁመው አንዱ በፊት አንዱ በኋላ ሆነው በፍላጻ እየነደፉ በእጅጉ ያሠቃዩት ጀመር፡፡ አረጋዊ አባ ሜልዮስም ‹‹እኔን በፍላጻዎቻችሁ ለመግደል እንዳሠቃያችሁኝ እናንተም ደግሞ በገዛ ፍላጻዎቻችሁ ትሞቱ ዘንድ አላችሁ›› በማለት ትንቢት ተናገረባቸው፡፡ እነርሱም ቃሉን በመናቅ ነፍሱን እስከሚያሳልፍና ምስክር ሆኖ የሰማዕትነት አክሊልን እስከሚቀበል ድረስ በፍላጻዎች ነደፉት፡፡ እርሱም ሰማዕትትነቱን በዚህ ፈጽሞ የክብር አክሊልን ተቀዳጀ፡፡
አባ ሜልዮስን በግፍ የገደሉት ጭፍሮቹም በማግሥቱ እንደልማዳቸው ለአደን በወጡ ጊዜ የዱር አህያ አገኙ፡፡ ተከታትለውም ቀስታቸውን አስፈነጠሩ፡፡ እግዚአብሔርም ፍላጻቸውን ወደራሳቸው መልሶ ቅዱስ አባ ሜልዮስ እንደተናገረ በራሳቸው ፍላጻ ሞቱ፡፡
የሰማዕታቱ የአረጋዊ አባ ሜልዮስ፣ የአባ ኢያሱና የአባ ዮሴፍ ረድኤት በረከታቸው ይደርብን፣ በጸሎታቸው ይማረን!
(ሚያዝያ 13 የመልአኩ ቅዱስ ሩፋኤል ወርሃዊ መታሰቢያ በዓሉ ነው።)
No comments:
Post a Comment