ስንክሳር ዘወርኀ መጋቢት 16 - አትሮንስ ሚዲያ - Atrons Media

አትሮንስ ሚዲያ - Atrons Media

ስብኩ ወንጌለ ለኩሉ ፍጥረት ማቴ 16፤15


በቅርብ የተጻፉ

Post Top Ad

Tuesday, May 23, 2023

ስንክሳር ዘወርኀ መጋቢት 16

 አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም



ግንቦት ዐሥራ ስደስት በዚችም ቀን ወንጌላዊው ቅዱስ ዮሐንስ መታሰቢያው ነው፣ ዕውቀትን ከልቡ ያፈለቀ የኢየሩሳሌሙ ሰው ቅዱስ ኢያሱ ሲራክ ነቢይና ጠቢብ አረፈ፣ ኢትዮጵያዊው ጻድቅ ለአቡነ ሐዋርያ ክርስቶስ ከዚህ ዓለም ከሞት ተሰወሩ፡፡

ቅዱስ ዮኀንስ ወንጌላዊ
ግንቦት ዐሥራ ስደስት በዚችም ቀን የወንጌላዊ ቅዱስ ዮሐንስ መታሰቢያው ነው። በእስያና በኤፌሶን በዙሪያቸው በአሉ አገሮች ሁሉ ስለ መስበኩና ከባሕር በመስጠምም ወደ ፈጣሪያቸው እግዚአብሔር እስከ መለሳቸውና የክብር ባለቤት ጌታችን በእጆቹ ላይ የሚያደርገው ተአምራት በትምህርቶቹም ከሰይጣን ወጥመድ እስከ አዳናቸው ድረስ ጣዖታትን ከሚያመልኩ ከክፉዎች ሰዎች ስለደረሰበት መከራ ነው።
በሸመገለም ጊዜ ወንጌልን ጻፈላቸው ሦስቱ ወንጌላውያን ያስቀሩትን እስከሚጽፍ መንፈስ ቅዱስ አነሣሥቶታልና የወልድንም አኗኗሩንና ሰው መሆኑን ዓለም የማይወስነውንም ተአምራቱን። ከዚህ በኋላም ወደ ሰማይ እንደ ወጣና በሰማይ የሚኖሩ የመላእክት ሠራዊት ሥርዓታቸውን አይቶ አቡቀለምሲስ የሚባለውን ጻፈ።
ለስብከቱም የበዓሉ መታሰቢያ ሊሆን ግብጻውያን ይህን ሠሩ ዳግመኛም በእስክንድርያ አገር ውስጥ ቤተ ክርስቲያኑ የከበረችበት ቀን ነው። (ስንክሳር ዘወርኀ ግንቦት 16)
ተጨማሪ ስለ ቅዱስ ዮሐንስ ወንጌላዊ
ቅዱስ ዮሐንስ ወንጌልን ለመስበክ ዕጣ የደረሰው እስያ ስለነበር ደቀ መዝሙሩን አብሮኮሮስን አስከትሎ ሄደ፡፡ ይኽችውም ኤፌሶን በጥንቱ በታናሽ እስያ በዛሬው የቱርክ ግዛት ውስጥ ከተማ ናት፡፡ ዛሬ ኢያዞሎክ ተብላ የጥንት ታሪኳ ጠፍቷል፡፡ አስቀድሞ ቅዱስ ጳውሎስ ወንጌልን ሰብኮባታል፡፡ ደቀ መዝሙሩን ቅዱስ ጢሞቴዎስንም በከተማዋ ላይ ኤጲስቆጶስ አድርጎ ሾሞት ነበር፡፡ እርሱም በግፍ እስከተገደለበት ጊዜ ድረስ ቅዱስ ዮሐንስን እየረዳው በከተማዋ ብዙ አገልግሏል፡፡ በኋላ ግን በግፍ ገድለውታል፡፡
ቅዱስ ዮሐንስ ወደ ኤፌሶን ለመሄድ በመርከብ ሲሳፈር መርከቡ በማዕበል ተሰበረ፡፡ ደቀ መዝሙሩን አብሮኮሮስን መዕበሉ ወደ አንዲት ደሴት አደረሰው፡፡ ቅዱስ ዮሐንስ ግን በመርከቡ ስባሪ ተንጠልጥሎ በባሕሩ ማዕበል መካከል 40 ቀንና 40 ሌሊት ከኖረ በኋላ ማዕበሉ ተፍቶ አብሮኮሮስ ካለበት ደሴት አደረሰውና ተያይዘው ኤፌሶን ከተማ ገቡ፡፡ የከተማይቱም ሰዎች እጅግ ክፉዎች ስለነበሩ መጀመሪያ ላይ ቅዱስ ወንጌልን መስበክ አልቻሉም ነበር፡፡ እነርሱም እጅግ ክፉዎች መሆናቸውን ስላወቀ ቅዱስ ዮሐንስ ገና ዕጣው ሲደርሰው በሀዘን አልቅሶ ነበር፡፡ አሁንም ከተማው በገቡ ጊዜ ቅዱስ ዮሐንስ ምክንያት በመፍጠር ሮምና ለምትባል ሴት የውሽባ ቤቷ እሳት አንዳጅ ሆኖ አብሮኮሮስም ዕቃ አጣቢ ሆነው ተቀጠሩ፡፡ የቀጠረቻቸው ሴትም እጅግ ታሠቃያቸው ጀመር፡፡ ባሮቿ እንደሆኑ ተስማምተው ስለጻፉላት ትደበድባቸውም ነበር፡፡
እነርሱም በታላቅ ጉስቁልና ውስጥ እየኖሩ እያለ በአንዲት ዕለት የአገረ ገዥው ልጅ ለመታጠብ ወደ ውሽባው ቤት ገባ፡፡ በውሽባ ቤቱም የሰይጣን ኃይል ስለነበረበት የመኰንኑን ልጅ አንቆ ገደለው፡፡ የአገሪቱም ሰዎች ሁሉ ለሞተው የመኰንን ልጅ ሊያለቅሱ ሲሰበሰቡ ቅዱስ ዮሐንስም አብሮ ቆሞ ሲመለከት ሮምና መጥታ ‹‹በጌታዬ ልጅ ሞት ልትደሰት መጣህን›› እያለች ረገመችው፡፡ እርሱም ‹‹አይዞሽ አትዘኚ›› አላትና ወደ ሞተው ልጅ ቀርቦ በመስቀል ምልክት ካማተበበት በኋላ በፊቱ እፍ አለበት፡፡ የሞተውም ልጅ ድኖ ተነሣ፡፡ የሀገሪቱም ሰዎች እጅግ ደነገጡ፡፡ ሮምናም ደንግጣ ‹‹እግዚአብሔር የሚሉት አምላክ አንተ ነህን›› ብላ ጠየቀችው፡፡ ቅዱስ ዮሐንስም ‹‹በፍጹም እኔ አምላክ አይደለሁም፣ እኔ የእርሱ አገልጋዩና ሐዋርያው ነኝ እንጂ›› አላት፡፡ ሮምናም ስለበደለቻቸው በደል ሁሉ መሪር ዕንባን እያለቀሰች ይቅር እንዲሏት ለመነቻቸው፡፡ እነርሱም አረጋጉዋት፡፡ ከሕዝቡም ውስጥ ብዙዎቹ በጌታችን አመኑ፡፡ ቅዱስ ዮሐንስም ሌሎች ብዙ ድንቅ ድንቅ ተአምራትን እያደረገ ወንጌልን እየሰበከ ከጣዖት አገልጋዮች በቀር ሁሉንም አሳምኖ አጠመቃቸው፡፡ አገልጋዮችን ኤጲስቆጶሳትን፣ ቀሳውስትንና ዲያቆናትን ከሾመላቸው በኋላ ወደ ሌሎች አቅራቢያ አገሮች ሄደ፡፡
በመጨረሻም በከሃዲውና በጨካኙ በድምጥያኖስ ዘመን በጣዖት አምላኪዎች ተከሶ ለፍርድ ቀረበ፡፡ በፈላ ውኃ ካሠቃዩት በኋለ በፍጥሞ ደሴት አጋዙት፡፡ በዚያም ሳለ ራእዩን ተመልክቶ ጻፈው፡፡ ድምጥያኖስም ከተገደለ በኋላ ከግዞቱ ተመልሶ ሦስቱን መልእክታቱንና ቅዱስ ወንጌሉን ጽፏል፡፡ ጌታችንም አስቀድሞ ሞትን እንደማይቀምስ ለዮሐንስ ቃል ገብቶለት ነበርና (ዮሐ 21፡22) ጥር 4 ቀን እንደ ኤልያስና ሄኖክ ሞትን እንዳያይ ወደ ብሔረ ሕያዋን ወስታል፡፡ ዛሬ ግንቦት 16 ቀንም ዓመታዊ መታሰቢያ በዓሉ ነው፡፡ ይኸውም በእስያና በኤፌሶን በዙሪያቸውም ባሉ አገሮች ሁሉ ወንጌልን ስለመስበኩና ስለደረሰበት መከራ ስላደረጋቸውም ብዙ ተአምራት ነው፡፡ ዳግመኛም በእስክንድርያ አገር ቤተ ክርስቲያኑ የከበረችበት ዕለት ነው፡፡
ጌታችን ለዮሐንስ ያልነገረው እርሱም ያላስተማረው ምሥጢር የለም፡፡ ወንጌሉን መጻፍ ሲጀምር ‹‹በመጀመሪያ ቃል ነበረ፣ ቃልም በእግዚአብሔር ዘንድ ነበረ…›› ብሎ የጌታችን ነገር ተመራምሮ ለመድረስ ሲል በመሀል መልአኩን በዮርዳኖስ ባሕር ላይ ሲሄድ አገኘው፡፡ መልአኩም የዮርዳኖስን ባሕር በእንቁላል ቅርፊት እየጨለፈ ወደ ውጭ ሲያፈስ ተመለከተው፡፡ ዮሐንስም ተገርሞ ‹‹ምን ማድረግህ ነው›› አለው፡፡ መልአኩም ‹‹የዮርዳኖስን ባሕር ቀድቼ እየደፋሁ ልጨርሰው ነው›› ሲለው ዮሐንስም መልሶ ‹‹ታዲያ በእንቁላል ስባሪ ነውን?›› አለው፡፡ መልአኩም ‹‹አዎን›› አለው፡፡ ዮሐንስም ‹‹በከንቱ ደከምክ›› አለው፡፡ ይህን ጊዜ መልአኩም መልሶ ‹‹አንተስ እንጂ ደግሞ የአምላክን መገኘት፣ አኗኗሩንም ተመራምረህ በጥበብ ለማግኘት ብለህ ‹በመጀመሪያ ቃል ነበረ፣ ቃልም በእግዚአብሔር ዘንድ ነበረ..› ብለህ ጀምረህ የለምን? አንተ ጌታን ተመራምረህ ካገኘህና ከደረስክበት እኔም የዮርዳኖስን ወንዝ በዚህ እንቁላል ቅርፊት ቀድቼ እጨርሰዋለሁ›› አለው፡፡ ዮሐንስም ይህን ጊዜ ደንግጦ ዝቅ ብሎ ‹‹ስሙ ዮሐንስ የሚባል አንድ ሰው ነበረ…›› ብሎ ሀሳቡን ለወጠና ሌላ ታሪክ ቀጠለ፡፡
ቅዱስ ዮሐንስ ጌታችንን እስከ እግረ መስቀሉ ድረስ በመከተሉ ክርስቲያኖችን ሁሉ ወክሎ እመቤታችንን በአደራ የተቀበለ እርሱም ለመቤታችን በአደራ የተሰጠ ሲሆን እመቤታችንን ከወሰዳት በኋላ ለ16 ዓመት እየተንከባከበ ጠብቋታል፡፡ እናቱም በሕፃንነቱ ስለሞተች እመቤታችን ናት እየተንከባከበች ያሳደገችው፡፡ ቅዱስ ዮሐንስ በመልኩም ከጌታችን ጋር ይመሳል ነበር፡፡ ቅዱስ ዮሐንስ ሥዕል የመሳል ተሰጥኦም ነበረው፡፡ ጌታችን በተሰቀለበት ዘመን የነበረው ጢባርዮስ ቄሳር ልጁ በሽተኛ ነበር፡፡ የጌታችንን የማዳን ሥራ እየሰማ እነ ጲላጦስም ስለጌታችን የሚጽፉለትን ይሰማ ስለነበር ልጁን ከጌታችን መቃብር ላይ እንዲያኖሩለት ላከው፡፡ ልጁም ፈጥኖ ተፈወሰለት፡፡ ጢባርዮስ ቄሳርም በልጁ መዳን ምክንያት የጌታችንን ውለታ ማስቀመጥ ፈልጎ የጌታችንን ሥዕሉን የሚሥልለትን ሲያጠያይቅ ዮሐንስን አገናኙት፡፡ ዮሐንስም ጌታችንን ልክ በዕለተ ዓርብ እንደተሰቀለ አድርጎ በመሣል ለጢባርዮስ ቄሳር ሰጠው፡፡ ሲሥለውም በመጀመሪያ ጌታችንን ልክ እንደተሰቀለ ራቁቱን ነበር የሳለው፡፡ ዮሐንስ የሳለው የጌታችን ሥዕልም አፍ አውጥቶ ‹‹በመጀመሪያ አይሁድ በኢየሩሳሌም ራቁቴን ሰቀሉኝ፣ አሁን ደግሞ አንተ ድጋሚ በሮም ራቁቴን ትሰቅለኝን?›› ብሎ ተናገረው፡፡ ዮሐንስም እጅግ ደንግጦ ‹‹እንዴት አድርጌ ልሳልህ?›› ብሎ የሳለውን ሥዕል ቢጠይቀው ሥዕሉም ‹‹ከለሜዳ አልብሰህ ሳለኝ›› አለው፡፡ ዮሐንስም እንዳለው ከለሜዳ አልብሶ ከሳለው በኋላ ሥዕሉን ትኩር ብሎ ተመልክቶ ቢስመው ከንፈሩ አንድ ቀን ተኩል ያህል ተጣብቆ ቆይቷል፡፡ ዛሬም ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን የምትጠቀምባቸውን የጌታችንን ስነ ስቅለት የሚያሳዩ ሥዕሎች መገኛቸው ይህ ወንጌላዊው ዮሐንስ የሳለው ሥዕል ነው፡፡
ቅዱስ ዮሐንስ በተለያዩ ስሞች ይጠራል፡፡ በሕይወቱና በኑሮው ሁሉ ጌታችንን ለመምሰል ይጥር ነበርና ጌታችንም እጅግ ይወደው ስለነበር ‹‹ፍቁረ እግዚእ›› ተባለ፡፡ የታላቁ ያዕቆብ ታናሽ ወንድም ስለሆነና አባቱም ዘብድዮስ ስለሚባል ‹‹ዮሐንስ ወልደ ዘብድዮስ›› ተባለ፡፡ ለጌታችን ባለው ቅናትና ከወንድሙ ጋር ሆነው ባሳዩት የኃይል ሥራ እንዲሁም የጌታችንን አምላክነት በመግለጡ ‹‹ወልደ ነጎድጓድ›› ተብሏል፡፡ ነገረ መለኮትን ከሌሎቹ በበለጠ ሁኔታ አስፍቶና አምልቶ በማስተማሩ ‹‹ነባቤ መነኮት ወይም ታኦሎጎስ›› ተብሏል፡፡ ኃላፊውንና መጻዒውን ጊዜ በራእዩ ስለገለጠ ‹‹አቡቀለምሲስ›› ተባለ፣ ይህም በግሪክኛ ባለራእይ ማለት ነው፡፡ የጌታችንን መከራ መስቀሉን እያስታወሰ 70 ዘመን ሙሉ እያለቀሰ ስለኖረና ፊቱም በሀዘን ስለተቋጠረ ‹‹ቁዱረ ገጽ›› ተብሏል፡፡ ረድኤት በረከቱ ይደርብን፣ በጸሎቱ ይማረን፡፡ (ምንጭ፡- ስንክሳር ዘወርሃ ጥር፣ ቤተ ክርስቲያንህን ዕወቅ፣ የቅዱሳን ታሪክ-30)
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
ቅዱስ ኢያሱ ሲራክ ነቢይና ጠቢብ
በዚህች ቀን ዕውቀትን ከልቡ ያፈለቀ የኢየሩሳሌሙ ሰው የአልዓዛር ልጅ ኢያሱ ሢራክ አረፈ። እርሱም በጥንተ ትንቢቱ የባሕር አሸዋን የዝናም ጠብታን የዘመንን ቁጥር ማን ቈጠረ አለ።
ከአብ ጋራ ስለ አለው አንድነት የጥበብ አኗኗር ከዓለም መፈጠር በፊት ነው ለጥበብ መገኛዋ ለማን ተገለጠ የጥበብ ምክሯንስ ማን አወቀ በእግዚአብሔር ዙፋን ላይ የምትቀመጥ እጅግ የምታስፈራ ናት አለ።
ሁለተኛም እኔ ከልዑል አፍ ወጥቼ ምድርን አንደ ጉም ሸፍንኋት በሰማያትም እኖራለሁ ዙፋኔንም በደመና ምሰሶ ላይ ዘረጋሁ ብቻዬን በሰማይ ዳርቻ ዞርኩ በውቅያኖስም ጥልቅ ውስጥ ማረፊያ እየፈለግሁ በባሕሩ ውኃ ላይ ሁሉ ተመላለስኩ አለች አለ።
ስለ ወልደ እግዚአብሔርም ሰው መሆን እንዲህ አለ እግዚአብሔር በያዕቆብ ዘንድ እደሪ በእስራኤልም ዘንድ ተዋረሺ አለኝ አለች። ደግሞ ስለ መድኃኒታችን ሞትና ስለ አይሁድ መጥፋት በወጥመዱ ይጠመዳሉ የመሞቻቸው ጊዜም ሳይደርስ ይሠጥማሉ አለ። ስለ ንስሓና ከንስሓ በኋላ ወደ ኃጢአት ስለ መመለስ እንዲህ አለ ከታጠቡ በኋላ ቆሻሻን መዳሰስ ምን ይጠቅማል።
ደግሞ ስለ ቤተክርስቲያን መታነፅና ስለ ሕዝብ እንዲህ አለ። አቤቱ በስምህ የተጠሩና በበረከት ያባዛኃቸውን ወገኖችህን ይቅር በል መመስገኛህና ማደሪያህ የሆነች ሀገርህ ኢየሩሳሌምንም ይቅር በል። የቃልህንም በረከት በጽዮንና በልጆቿ ላይ ምላ።
ስለሹማምንትና ስለ ሰባቱ መዐርጋት ሲናገር እንዲህ አለ ሰባቱን ኃይሎች የተቀበለች የሰው ሰውነቱ ጉበኛ ናት። ከዚህም ሁሉ ጋር መንገድህን ያቀናልህ ዘንድ ወደ ልዑል እግዚአብሔር ጸልይ። ስለ ጻድቃንም እንዲህ አለ የጻድቃን ልጆች በዱር ጠል የዱር አበባ እንዲ አብብ እንዲሁ ብቀሉ አብቡም እንደ ሊባኖስም መዓዛ መዓዛችሁ እንዲሁ የጣፈጠ ይሁን።
ዳግመኛም የእግዚአብሔርን ሥራ ሲያስብ እንዲህ አለ የሰማይን ንጽሕናውንና ጽናቱን ብርሃኑንም ያሳይ ዘንድ በሰማይ ገጽ ላይ ፀሐይን ማውጣቱን በቀትርም ጊዜ አገሩን ማቃጠሉን አስቦ። እንደ ምድጃ እሳት የሚነድ ላቦቱን ማን ይቃወመዋል የፀሐይ ዋዕይ ሦስተኛውም ተራሮችን ያቃጥላቸዋል ከእርሱም የእሳት ወላፈን ይወጣል አለ።
ጨረቃም ለዓለም ምልክቱ ነው በእርሱም የዘመናት የበዓላት ምልክት ይታወቃል። ስለ ከዋክብትም የሰማይ ጌጦቿ የከዋክብት ብርሃናቸው ነው በእግዚአብሔር ቅዱስ ፈቃድ እንዲሁ ያበራሉና በሥርዓታቸውም ጸንተው ከልካቸውም ሳይፋለሱ ሳይሳሳቱ ጸንተው ይኖራሉና አለ።
ስለ ቀስተ ደመናም ተናገረ ቀስቱን አየሁ ፈጣሪውንም አከበረ ብርሃኑ መልካም ነውና የልዑል ሥልጣንም ያዘጋጀዋል። ስለ በረድና መብረቅም ተናገረ ስለ እርሱ ትእዛዝም በረድ ይዘንማል በቃሉም መብረቅ ይፈጥናል ደመናትም እንደ አዕዋፍ ይበራሉ ነፋስም በእርሱ ፈቃድ ይነፍሳል የነጐድጓድ ድምፅና ብልጭልጭታው ምድርን ያስፈራታል ዐውሎውና ውርጩ ነፍስን ያስጨንቃታል።
ሰማይን እንደ ብረት ልብስ የሚሸፍነው እንደ ስለታም የብርጭቆ ስባሪ ይብለጨለጫል አለ። ስለ ዝናምም ተናገረ ዝናም የወረደ እንደሆነ ምድርን ድስ ያሰኛታል በትእዛዙም ባሕር ይደርቃል አለ። አባቶችንም በተሰጣቸው ሀብት ሲያመሰግናቸው ኄኖክ እግዚአብሔርን ደስ እንዳሰኘው። ኖኅም ጻድቅ ሁኖ እንደተገኘ።
አብርሃም ታማኝ እንደሆነ ይስሐቅም ለሰው ሁሉ የሚጠቅም በረከት እንደተሰጠው ለያዕቆብም በቸርነቱ እንደ ተገለጠለት ዐሥራ ሁለቱንም ነገድ እንደወለዳቸው በሰውና በእግዚአብሔርም ዘንድ እንደ ተወደዱ። ሙሴንም ስም አጠራሩ የከበረ የምላእክትም ብርሃን መልኩና ስም አጠራሩ የሆነ አለ። ወንድሙ አሮንንም የዘላለም ሕግን እንደ ሠራለት በልብሰ ተክህኖና በወርቅ አክሊል እንዳስደነቀው አለ። ሹመቱ ሦስተኛ የሚሆን የአልዓዛር ልጅ ፊንሐስንም ወደሰ።
የነዌ ልጅ ኢያሱን ለእስራኤል ልጆች የርስታቸውን ምድር እንዳወረሳቸው እጁንም በአነሣ ጊዜ እንደተመሰገነ። ሳሙኤልንም በእግዚአብሔር ዘንድ የተወደደ እንደሆነ ናታንንም በዳዊት ዘመን ትንቢት እንደተናገረ። ዳዊትንም ታናሽ ሁኖ ሳለ አርበኛውን ጎልያድን እንደገደለው አምስግኖታል ሰሎሞንንም በሰላም ወራት እንደነገሠ።
ኤልያስንም ሙት እንዳስነሣ እሳትንም ከሰማይ እንዳወረደ ራሱም በእሳት ሠረገላና በእሳት ፈረሶች እንደዐረገ። ኤልሳዕንም በዘመኑ ጠላቶች እንዳስደነገጡት ሁለት ሙታኖችንም እንዳስነሣ አንዱን በሕይወት ሳለ አንዱን ከሞተ በኋላ።
ሕዝቅያስንም አገሩን አጽንቶ እንደ ጠበቀ የፋርስንም ሠራዊት በጸሎቱ አጥፍቶ ስለ ሀገራቸው ጽዮን የሚያለቅሱትን ደስ እንዳሰኛቸው ርኵሰትንና ኃጢአትንም እንደ አስወገደ ኢዮስያስንም የኢዮስያስ ስም አጠራሩ መልካም ነው እንዳለው።
ኤርምያስንም ከእናቱ ማሕፀን ጀምሮ እንዳከበረው። ሕዝቅኤልም የእግዚአብሔርን ጌትነቱን እንዳየ። ዘሩባቤልንም በቀኝ እጅ እንዳለ ኀቲም ቀለበት ነው እንዳለው።
ዐሥራ ሁለቱ ነቢያትንም በየቦታቸው ዐፅማቸው እንደሚለመልም። ሆሴዕና ነህምያንም የወደቀች ቅጽርን አንሥተው ጠቃሚ ሥራ እንደሠሩ። ዮሴፍንም እርሱን የመሰለ ደግ ሰው እንዳልተወለደ። ኖኅና ሴምንም ክብራቸው ከሰው ሁሉ እንደሚበልጥ። አዳምንም በፍጥረት ሁሉ ላይ ንጉሥ እንደ ሆነ።
ስምዖንን በዘመኑ ቤተ መቅደስ እንደታነፀ በሕዝቡ ከምርኮ መመለስም እንደ ተመሰገነ በመጽሐፉ መጨረሻም። በሁሉ ቦታ ታላላቅ ሥራ የሚሠራና ዕድሜያችንን የሚያስረዝም እግዚአብሔር አምላክን አመስግኑት አለ። ይህንንም ተናግሮ በፍቅር አንድነት አረፈ።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
አቡነ ሐዋርያ ክርስቶስ
በዚህች ቀን ኢትዮጵያዊው ጻድቅ ለአቡነ ሐዋርያ ክርስቶስ ከዚህ ዓለም ከሞት ተሰወሩ፡፡ አቡነ ሐዋርያ ክርስቶስ የትውልድ ሀገራቸው ሸዋ መርሐ ቤቴ ነው፡፡ እንደ እነ ኤልያስና ሄኖክ ተሰውረዋል እንጂ በምድር ላይ ሞትን አልቀመሱም፣ ገና ወደፊት መጥተው በሰማዕትነት ይሞታሉ፡፡ ልደታቸው ሐምሌ 16 ቀን ነው፡፡ የነበሩበት ዘመንም በጻድቁ ንጉሥ በዐፄ ገብረ ማርያም ሐርበይ ዘመን ነው፡፡ ጻድቁን መልአኩ ከሚያገለግሉበት ከወሎ የህላ ሚካኤል ወደ ደብረ በንኮል ገዳም ወስዷቸው እንዲመነኩሱ አድርጓቸዋል፡፡ የቆረቆሩት ‹‹አቡነ ሐዋርያ ክርስቶስ ገዳም›› ወሎ መሐል ተከዜ ውስጥ ይገኛል፡፡ የበዛው ገድላቸው በዝርዝር ተጽፎ አይገኝም፡፡ ተከዜ በረሃ ላይ እጅግ አስደናቂ ትልቅ የአንድነት ገዳም አላቸው፡፡ 12 ክንፍ የተሰጣቸው ታላቁ ጻድቅ አቡነ ሐዋርያ ክርስቶስ በዛሬዋ ዕለት ነው የተሠወሩት፡፡
ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን።

ምንጭ፤ ስንክሳር ዘወርኀ መጋቢት

No comments:

Post a Comment

Post Bottom Ad

Pages