ስንክሳር ዘወርኀ ግንቦት 17 - አትሮንስ ሚዲያ - Atrons Media

አትሮንስ ሚዲያ - Atrons Media

ስብኩ ወንጌለ ለኩሉ ፍጥረት ማቴ 16፤15


በቅርብ የተጻፉ

Post Top Ad

Monday, June 5, 2023

ስንክሳር ዘወርኀ ግንቦት 17

 አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም

ግንቦት ዐሥራ ሰባት በዚች ቀን የከበረ አባት ታላቅና የተመሰገነ የቆጵሮስ ኤጲስቆጶስ ቅዱስ ኤጲፋንዮስ አረፈ፣ የኢትዮጵያዊው ጻድቅ ገርዓልታና ሐውዜን ላይ እጅግ አስገራሚ ታላላቅ ገዳማትን የገደሙት አቡነ ገብረ ሚካኤል ዕረፍታቸው ነው፡፡


ቅዱስ ኤጲፋንዮስ ሊቅ
ግንቦት ዐሥራ ሰባት በዚች ቀን የከበረ አባት ታላቅና የተመሰገነ የቆጵሮስ ኤጲስቆጶስ ቅዱስ ኤጲፋንዮስ አረፈ።
ይህም ቅዱስ ከቤተ ገብርኤል ዐፀድ አቅራቢያ ነው ወላጆቹም በኦሪት ሕግ የጸኑ አይሁድ ናቸው። እነርሱም ድኆች ናቸው አባቱም ገባር ስለ ነበረ ይህን ቅዱስና አንዲት እኅቱን ሳያሳድጋቸው ሞተ እርሱም አንድ ክፉ አህያ ነበረውና የተወላቸው እርሱን ነው እናታቸውም የኦሪትን ትምህርት በማስተማር አሳደገቻቸው።
እናቱም አህያውን እንዲሸጠውና ከእርሱም እንዲያርፍ በሺያጩም እንዲረዳ ኤጲፋንዮስን መከረችው። ሊሸጠውም ከአህያው ጋራ ሲጓዝ አንድ ክርስቲያን ጻድቅ ሰው ስሙ ፊላታዎስ የሚባል ተገናኘው ያንን አህያ ሊገዛ ወዶ ከኤጲፋንዮስ ጋራ ቁሞ ሲነጋገር ያን ጊዜ አህያው ኤጲፋንዮስን ኵላሊቱን ረገጠው በምድር ላይ ወድቆ ለመሞት ደረሰ። አባ ፊላታዎስም በመስቀል ምልክት ኵላሊቱ ላይ በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ ብሎ አማተበ ቅዱስ ኤጲፋንዮስም ያን ጊዜ ከሕማሙ ድኖ ተነሣ ከቶ ምንም ሕማም እንዳልነካው ሆነ። ከዚህ በኋላም አባ ፊላታዎስ በዚያ ክፉ አህያ ላይ እንዲህ ብሎ ጮኸ ስለ እኛ በተሰቀለው በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስም ትሞት ዘንድ ይገባል ወዲያውኑ ያ አህያ ወድቆ ሞተ።
ቅዱስ ኤጲፋንዮስም እሊህን ሁለት ተአምራት አይቶ በስሙ ተአምራት የምታደርግበት የተሰቀለ ኢየሱስ ክርስቶስ ማነው ብሎ አባ ፊላታዎስን ጠየቀው። እርሱም እንዲህ ብሎ መለሰለት የክብር ባለቤት የእግዚአብሔር ልጅ ኢየሱስ በኢየሩሳሌም አይሁድ የሰቀሉት ነው አለው ይህም ነገር በቅዱስ ኤጲፋንዮስ ልብ ተቀረጸ።
በዚያም ወራት አንድ ባለጠጋ አይሁዳዊ ነበር ኤጲፋንዮስንም ወሰደው የኦሪትንም ሕግ በማስተማር አሳደገው። የሚሞትበትም በቀረበ ጊዜ ልጅ ስለሌለው ጥሪቱን ሁሉ አወረሰው የኦሪትንም ሕግ ትምህርት ሁሉ ተማረ።
በአንዲት ዕለትም ስሙ ሉክያኖስ ከሚባል መነኰስ ጋራ ተገናኘ እርሱም የተማረና የእግዚአብሔር ጸጋ ያደረበት ነው ከእርሱ ጋር ተጓዘ። ሁለቱም በአንድነት ሲጓዙ ድኃ ሰው አገኛቸውና ምጽዋትን እንዲሰጠው ያንን መነኰስ ለመነው። ገንዘብም ስለሌለው የሚለብሰውን የጸጉር ዐጽፍ አውልቆ ለድኃው ሰጠው በዚያን ጊዜ ለዚያ መነኰስ የብርሃን ልብስ ከሰማይ ሲወርድለት ኤጲፋንዮስ አየ።
ስለዚህም ድንቅ ተአምር አደነቀ ከመነኰስ እግር በታች ሰግዶ አንተ ማነህ ሃይማኖትህስ ምንድ ነው ብሎ ጠየቀው እርሱም ክርስቲያን እንደሆነ ነገረው። ደግሞ ክርስቲያን እንዲያደርገው ለመነው መነኵሴውም ኤጲፋንዮስን ወስዶ ወደ አንድ ኤጲስቆጶስ አደረሰው። እርሱም የክርስትና ጥምቀትን አጥምቆ የቤተ ክርስቲያንን ትምህርት ሥርዓቷንም ሁሉ አስተማረው።
ኤጲፋንዮስም ኤጲስቆጶሱን እኔ መነኰስ መሆን እፈልጋለሁ አለው ኤጲስቆጶሱም ብዙ ገንዘብ እያለህ መነኰስ መሆን አይገባም አለው።
ኤጲፋንዮስም ሒዶ እኅቱን አምጥቶ የክርስትና ጥምቀትን አጠመቃት ገንዘቡን ሁሉ ለድኆችና ለምስኪኖች ለባልቴቶችና ለሙት ልጆች ለአብያተ ክርስቲያናትም ሰጠ መጻሕፍትንም ከእርሱ ገዛ።
ከዚህ በኋላ መነኰሰ ለእርሱም ለእኅቱም ለጥምቀት ምክንያት ወደሆነው ስሙ ሉክያኖስ ወደተባለው መነኰስ ገዳም ገባ ዕድሜውም ዐሥራ ስድስት ዓመታት ነበረ።
ከዚህም በኋላ ታላቁን አባ ኢላርዮስን አገኘው እርሱም በዕድሜው ጐልማሳ በገድልም ሽማግሌ ነው። ቅዱስ ኤጲፋንዮስንም ተቀብሎ የምንኵስናን ሕግና የክርስትናን ሥርዓት አስተማረው የእግዚአብሔርም ጸጋ አድሮበት የቤተ ክርስቲያንን ሕግና ሥርዓት የምንኵስናንም ሕግ በጥቂት ቀኖች አጠና።
ከዚህ በኋላ ታላላቅ ተአምራቶችን በመሥራት ሙታንን እስከሚአስነሣቸው ሰይጣናትን ከሰዎች ላይ እስከሚያስወጣቸው ውኃ ከሌለበት ከደረቅ ቦታ ውኃን እስከሚአፈልቅ ያለ ጊዜውም ብዙ ዝናምን እስከ ማውረድ ደርሶ በገድልና በትሩፋት ፍጹም ሆነ።
የትሩፋቱም ወሬ አዋቂነቱም ተሰማ ከእርሱ ጋራም ሊከራከሩ ብዙ አይሁድ ወደ እርሱ መጡ። ስሕተታቸውንም ገለጠላቸው በእርሱ ትምህርት አምነው የክርስትናን ጥምቀት አጠመቃቸው። እንዲሁም ጥበበኞች ዮናናውያን በትምህርቱ ተመለሱ ወደ ክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሃይማኖትም ውስጥ ገቡ።
መምህሩ ቅዱስ ኢላርዮስም በቆጵሮስ ሀገር ኤጲስቆጶስነት እንደሚሾም ትንቢት ተናገረለት። ወደዚያም ሒዶ በታዘዘለት ቦታ በዚያ እንዲኖር አዘዘው። እንዲህም አለው ኤጲስቆጶስነት ሊሾሙህ በፈለጉህ ጊዜ እምቢ አትበል ይህ በእግዚአብሔር ፍቃድ ሆኖአልና።
ቅዱስ ኤጲፋንዮስም ወደ ቆጵሮስ ሒዶ መምህሩ ቅዱስ ኢላርዮስ በአዘዘው ቦታ ተቀመጠ።
የቆጵሮስ ደሴት ኤጲስቆጶስም በአረፈ ጊዜ በዚያን ሰሞን ቅዱስ ኤጲፋንዮስ ምግቡን ሊገዛ ወደ ገበያ ገባ። ከእርሱም ጋራ ሁለት መነኰሳት አሉ። ደግሞም በዚያች ገዳም ጻድቅ የሆነ ሽማግሌ ኤጲስቆጶስ ነበረ ለእርሱም የክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እንዲህ ብሎ ነገረው። ወደ ገበያም ሒድ በእጁም ሁለት የወይን ዘለላ የያዘ መነኰስ ታገኛለህ ከእርሱ ጋራም ሁለት መነኰሳት አሉ ስሙንም ጠይቀው። ስሜ ኤጲፋንዮስ ነው ይልሃል እርሱን ያዝ በእጁ ያለውንም አስጥለህ ከአንተ ጋራ አምጣው።
ያ ኤጲስቆጶስም የክበር ባለቤት ጌታችን እንደ አዘዘው አደረገ በአመለከተውም ቦታ አግኝቶት ይዞ ወደ ቤተ ክርስቲያን ወስዶ ዲቁና ሾመው። በሦስተኛውም ቀን ኤጲስቆጶስነት ሾሙት። ከዚህም በኋላ ሽማግሌው ኤጲስቆጶስ የኤጲፋንዮስን ልብ ደስ ለማሰኘት ሽቶ ስለ ኤጲፋንዮስ ያየውን ራእይ ለሕዝቡ ገለጠላቸው። ስለ ርሱም ታላቅ ደስታ ሆነላቸው።
ይህም ቅዱስ እግዚአብሔር በሚወድለት በሹመቱ ሁኖ በበጎ ሥራ ላይ ጸና። ጥቅም ያላቸውን ብዙ ድርሳኖችንም ደረሰ። ርኅራኄ ስለ ሌለው ሰው በሚሰማ ጊዜ ተመልሶ ቸር እስከሚሆን ድረስ ሁልጊዜ ይገሥጸዋል ይመክረዋል።
በኢየሩሳሌም ኤጲስቆጶስ በአባ ዮሐንስ ላይ ምክንያት ፈጠረ ስለ ርሱ ርኅራኄ እንደሌለው በሰማ ጊዜ ከወርቅ የተሠሩ የማዕዱን ዕቃዎች የሚመገብባቸውን በውሰት ወሰደ። እነርሱም ወርቅና ብር ናቸው ቅዱስ ኤጲፋንዮስም ሸጣቸውና ለድኆችና ለምስኪኖችም መጸወታቸው።
አባ ዮሐንስም እንዲመልስለት በሻ ጊዜ ምንም ምን አልሰጠውም። በክብር ባለቤት ጌታ መቃብር ቤተክርስቲያን ውስጥ ቅዱስ ኤጲፋንዮስን የልብሱን ጫፍ ስጠኝ ብሎ ያዘው። ቅድስ ኤጲፋንዮስም ወደ እግዚአብሔር ጸለየ የአባ ዮሐንስም ዐይኖቹ ያንጊዜ ታወሩ። ከዚህ በኋላም ይምረው ዘንድ በብዙ ልቅሶ ወደርሱ ፈጽሞ ማለደ ዐይኖቹንም ይገልጥለት ዘንድ ለመነው።
ሁለተኛም ቅድስ ኢጲፋንዮስ ጸለየ አንድ ዐይኑንም ገለጠለት የማዕዱንም ዕቃዎች ሸጦ ለድኆችና ለምስኪኖች እንደሰጣቸው ነገረው። ስለ ዮሐንስ አፈወርቅ መሻርና መሰደድ ወደርሷ መጥቶ ይራዳት ዘንድ አውዶክስያ ንግሥት ጽፋ ወደርሱ በላከች ጊዜ ሊአስታርቃቸውና በመካከላቸው ሰላምን ሊአደርግ ሽቶ ወደ ቊስጥንጥንያ ሔደ። ነገር ግን ቅዱስ ኤጲፋንዮስን አልሰማችውም ዮሐንስን ከሹመቱ ካልሻርከው ይህ ካልሆነ አብያተ ክርስቲያናትን እዘጋለሁ የጣዖታትንም ቤቶች እከፍታለሁ አለችው።
ቅዱስ ኤጲፋንዮስም ፈጽሞ እያዘነ ከእርሷ ዘንድ ወጣ። ምን እንደሚአደርግም ያስብና ይጨነቅ ነበር።የንግሥት ባሮቿ ግን እነሆ ቅዱስ ኤጲፋንዮስ ዮሐንስ አፈወርቅን ከሹመቱ ሻረው እያሉ በቊስጥንጥንያ ከተማ በሐሰት አወሩ።
ቅዱስ ዮሐንስም ይህን ወሬ በሰማ ጊዜ ወደ ኤጲፋንዮስ እንዲህ ሲል ላከ። ለምን ያለ ፍርድ በእኔ ላይ ይህን አደረግህ አንተ ወደ መንበረ ሢመትህ እንደማትደርስ ዕወቅ። ኤጲፋንዮስም ለመልእክቱ መልስ እንዲህ ሲል ጻፈ። ስለ አንተ ምንም ምን የጻፍኩትና ከንግሥት ጋራ የተስማማሁት ነገር የለም አንተም ከስደት እንደማትመለስ ዕወቅ።
ከዚህ በኋላም ወደ መንበረ ሢመቱ ሊሔድ ሽቶ ከቊስጥንጥንያ ወጥቶ በመርከብ ተሳፈረ እግዚአብሔርም የዮሐንስን ጽድቅ ሊገልጽ ከመንበረ ሢመቱ ሳይደርስ ቅዱስ ኤጲፋንዮስ በመርከብ ውስጥ አረፈ። እንዲሁም የቅዱስ ኤጲፋንዮስ ክብር እንዲገለጥ ቅዱስ ዮሐንስ በተሰደደበት አረፈ።
የከበረ ኤጲፋንዮስም የሚያርፍበትን ጊዜ አውቆ ተነሥቶ ጸለየ። ለደቀ መዛሙርቱም እነርሱ ኤጲስቆጶሳት እንዲሆኑ ነገራቸው በሰላምታም ተሰናብቷቸው ከዚህ በኋላ በሰላም አረፈ።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
አቡነ ገብረ ሚካኤል
በዚህችም ቀን የኢትዮጵያዊው ጻድቅ ገርዓልታና ሐውዜን ላይ እጅግ አስገራሚ ታላላቅ ገዳማትን የገደሙት የአቡነ ገብረ ሚካኤል ዕረፍታቸው ነው፡፡ እኚህ ኢትዮጵያዊ ጻድቅ በታላቅ ተጋድሎአቸው ይታወቃሉ፡፡ የትውልድ ሀገራቸው ትግራይ ገርዓልታ ነው፡፡ ጻድቁ አቡነ ገብረ ሚካኤል ወንጌልን ዞረው በማስተማርና አስደናቂ ፍልፍል ዋሻ ቤተ መቅደሶችን በማነጽ ብዙ የደከሙ ታላቅ አባት ናቸው፡፡ እጅግ አስናቂው ገዳማቸው ገርዓልታ ጠራሮ ቀበሌ ውስጥ ይገኛል፡፡
ከገርዓልታ በደቡባዊ አቅጣጫ የሚገኘው ይህ የአቡነ ገብረ ሚካኤል አስደናቂ ገዳም እንደ ደብረ ዳሞ በገመድ ብቻ ከሚወጣው ከአቡነ ገብረ ናዝራዊ ገዳም ጋር የሚዋሰን ሲሆን ገዳሙ ለመድረስ የመኪናውን መንገድ ከጨረሱ በኋላ በእግር አንድ ሰዓት ይፈጃል፡፡
በገዳሙ ውስጥ ጻድቁ ይጠቀሙባቸው የነበሩ ብዙ ቅርሶች ይገኛሉ፡፡ የጌታችን የሾህ አክሊል ምሳሌ የሆነውና ጻድቁ ያደርጉት የነበረው የድንጋይ ቆብ፣ መቋሚያቸው፣ የእጅ መስቀላቸውና መጻሕፍቶቻቸው ይገኛሉ፡፡ ሌላው አስደናቂ ነገር ሀገሩ በረሃ ቢሆንም ጻድቁ ከኢየሩሳሌም ዮርዳኖስ ያመጡትና ዋሻው ውስጥ ጉድጓድ ቆፍረው ያጠራቀሙትን ውኃ መነኮሳቱ ሁልጊዜ የሚጠቀሙበት ቢሆንም ውኃው ግን ከዓመት እስከ ዓመት መጠኑ አይቀንስም፡፡ ሊቀ ብርሃናት መርቆርዎስ አረጋ የቅዱሳን ታሪክና ኢትዮጵያውያን ቅዱሳን በሚሉት ሁለት መጽሐፎቻቸው ላይ እንደጠቀሱት በገዳሙ ውስጥ ከዓመት እስከ ዓመት የምትበራው አንዲት ጧፍ ብቻ ናት፡፡ ጧፏ ነዳ የማታልቅ ስትሆን አለቀች ትቀየር ሳትባል አስገራሚ በሆነ ተአምር ከዓመት እስከ ዓመት ትበራለች፡፡
ሌላኛው የአቡነ ገብረ ሚካኤል አስደናቂ ፍልፍል ዋሻ ቤተ መቅደስ ከሀውዜን ከተማ በስተደቡብ አቅጣጫ ከአስደናቂው የአቡነ ይምዓታ ጎሕ ገዳም 16 ኪ.ሜ ርቀት ላይ የሚገኘው ነው፡፡ ጠራሮ ቀበሌ ውስጥ የሚገኘው ይሄኛውም ገዳማቸው በተፈጥሮአዊ አቀማመጡ አስደናቂ ነው፡፡ አቡነ ገብረ ሚካኤል አስደናቂውን ዋሻ ፈልፍለው ከጨረሱ በኋላ ግድግዳውና ዓምዶቹ ላይ የሳሏቸው የሐዋርያትና የቅዱሳን ሥዕላት ከጥንታዊነታቸው በተጨማሪ እጅግ ውብና አስደናቂ ናቸው፡፡ ይበልጥ የሚያስገርመው ደግሞ ጻድቁ ቅዱሳት ሥዕላቱን የሳሏቸው በሸራ ላይ ሳይሆን በአሸዋማው የዋሻው ፍልፍል ግድግዳ ላይ መሆኑ ነው፡፡
ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን።
ምንጭ፤ ስንክሳር ዘወርኀ ግንቦት

No comments:

Post a Comment

Post Bottom Ad

Pages