ስንክሳር ዘወርኀ ግንቦት 18 - አትሮንስ ሚዲያ - Atrons Media

አትሮንስ ሚዲያ - Atrons Media

ስብኩ ወንጌለ ለኩሉ ፍጥረት ማቴ 16፤15


በቅርብ የተጻፉ

Post Top Ad

Monday, June 5, 2023

ስንክሳር ዘወርኀ ግንቦት 18

 አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም

ግንቦት ዐሥራ ስምንት በዚህች ቀን የክብር ባለቤት ጌታችን ከዐረገ በኋላ በዐሥረኛ ከትንሣኤው በሃምሳኛ ቀን ለደቀመዛሙርቱ መንፈስ ቅዱስን የላከበት በዓለ ጰራቅሊጦስ ነው፣ የአባ አብርሃም ጓደኛ የከበረ አባ ገዐርጊ አረፈ፣ የሰማዕት ሲኖዳ መታሰቢያው ነው በረከቱ፡፡




ቅዱሳን ሐዋርያት ወአርድዕት (በዓለ_ጰራቅሊጦስ)
ግንቦት ዐሥራ ስምንት በዚህች ቀን የክብር ባለቤት ጌታችን ከዐረገ በኋላ በዐሥረኛ ከትንሣኤው በሃምሳኛ ቀን ለደቀመዛሙርቱ ከአብ የሚሠረጽ ሌላ አካላዊ ሕይወት ጰራቅሊጦስን እልክላችኋለሁ ብሎ ተስፋ እንደ ሰጣቸው በሐዋርያት ላይ አጽናኝ መንፈስ ቅዱስ ወረደ።
እናንተም ከአርያም ኃይልን እስከምትለብሱ በኢየሩሳሌም ኑሩ አላቸው። ሁለተኛም ያ እውነተኛ መንፈስ በመጣ ጊዜ ወደ ዕውነት ሁሉ ይመራችኋል አላቸው። ጴጥሮስም እንዲህ አላቸው እርሱም አለቃቸው የሆነ ጌታችን አጽናኚውን ይኸውም መንፈስ ቅዱስ ነው ሊልክልን ተስፋ አስደርጎናል የምናሰማውንና የምናደርገውን ልብ ያስደርገን ዘንድ።
ይህንንም ሲነግራቸው እነሆ የዐውሎ ነፋስ ድምፅ ሰሙ በዓለም ውስጥ እንደርሱ ያለ የማያውቁት ጣፋጭ መዓዛ አሸተቱ። የተከፋፈሉ የእሳት ላንቃዎችም በየአንዳንዳቸው ላይ ሲወርዱ ታዩ። በአዲስ ቋንቋም ተናገሩ ለጌትነቱ እጅ መንሻ ሊሆን አርባ ቀን ጾሙ። ሁለተኛም በሐዋርያት ሥራ መጽሐፍ በዓለ ኃምሣ የተባለውም ቀን በደረሰ ጊዜ ሁሉም በአንድ ልብ ሁነው አብረው ሳሉ። ድንገት ከሰማይ የዐውሎ ነፋስ ድምፅ መጣ ተቀምጠው የነበሩበትም ቤት ሁሉ መላው።
የተከፋፈሉ የእሳት ልሳኖችም ታዩአቸው በየአንዳንዳቸውም ላይ ተቀመጡባቸው ሁሉም መንፈስ ቅዱስን ተመሉ። በየራሳቸውም በሀገሩ ሁሉ ቋንቋ ይናገሩ ጀምር መንፈስ ቅዱስ ይናገሩ ዘንድ እንደ ሰጣቸው። ከሰማይም በታች ካሉ ሕዝብ ሁሉ በጸሎት የተጉ አይሁድ በኢየሩሳሌም ይኖሩ ነበር።
ይህንንም ድምፅ በሰሙ ጊዜ ደንግጠው ሁሉም ተሰበሰቡ በየሀገራቸው ቋንቋ ሲናገሩ ሰምተዋቸዋልና።ተደንቀውም በድንጋጤ እንዲህ አሉ። እነሆ እሊህ የገሊላ ሰዎች አይደሉምን እኛም እያንዳንዳችን የተወለድንበትን የገዛ ቋንቋችንን እንዴት እንሰማለን የጳርቴና የሜድ የኤላሜጤም ሰዎች ስንሆን። በሁለት ወንዝም መካከል በይሁዳም በቀጰዶቅያም በጳንጦስም በእስያም በፍርግያም በጵንፍልያም በግብጽም በቀሬናም በኩል ባሉት በሊብያ ወረዳዎች የምንኖር በሮሜም የምንቀመጥ አይሁድም ወደ ይሁዲነት የገባን የቀርጤስና የዐረብ ሰዎች ስንሆን የእግዚአብሔርን ገናናነት በቋንቋችን ሲናገሩ እነሆ እንሰማቸዋለን።
ሁሉም ደንግጠው የሚናገሩትን አጡ። እርስ በርሳቸውም እንጃ ይህ ምን ይሆን አሉ ሌሎች ግን እያፌዙባቸው ጉሽ የወይን ጠጅ ጠግበዋል አሉ። ጴጥሮስም ከዐሥራ ሁለቱ ጋራ ቆመ ድምፁንም ከፍ አድርጎ እንዲህ ሲል ተናገራቸው። የይሁዳ ሰዎች በኢየሩሳሌምም የምትኖሩ ሁላችሁ ይህ በእናንተ ዘንድ የታወቀ ይሁን ቃሎቼንም አድምጡ።
ለእናንተ እንደ መሰላችሁ እነዚህ የሰከሩ አይደሉም ከቀኑ ሦስተኛ ሰዓት ነውና። ነገር ግን ይህ በነቢዩ በኢዩኤል የተባለው ነው እግዚአብሔር አለ በመጨረሻው ቀን እንዲህ ይሆናል ሥጋ በለበሰ ሁሉ ላይ ከመንፈሴ አሳድራለሁ። ወንዶችና ሴቶች ልጆቻችሁ ትንቢትን ይናገራሉ ጐበዛዝቶቻችሁም ራእይን ያያሉ ሽማግሎቻችሁም ሕልምን ያልማሉ።
ደግሞም በዚያ ወራት በወንዶችና በሴቶች ባሪያዎቼ ላይ መንፈስ ቅዱስን አሳድራለሁ ትንቢትን ይናገራሉ። ድንቆችን በላይ በሰማይ ምልክቶችንም በታች በምድር እሰጣለሁ። ደምም እሳትም የጢስ ጭጋግም ይሆናል ታላቅ የሆነ የጌታ ቀንም ሳይመጣ ፀሐይ ወደ ጨለማ ጨረቃም ወደ ደም ይለወጣል።የጌታን ስም የሚጠራ ሁሉ ይድናል።
ዳዊትም እንዲህ አለ ቅዱስ መንፈስህን ከእኔ ላይ አትውሰድብኝ ደስ የሚያሰኝ ደኅነትህንም ስጠኝ። በጽኑዕ መንፈስህም አጽናኝ ለዝንጉዎች ሕግህን እንዳስተምራቸው። ሁለተኛም መንፈስህን ትልካለህ ይፈጠራሉ አለ። ደግሞ ቅዱስ መንፈስህ በጽድቅ ምድር ይምራኝ አለ።
ደግሞም በእግዚአብሔር ቃል ሰማዮች ጸኑ ሠራዊቶቻቸው ሁሉ በአፉ እስትንፋስ። ኢሳይያስም እንዲህ አለ በእኔ ህልውና ያለ ያዋሐደኝ ሕይወቴ መንፈስ ቅዱስ ለድኆች የምሥራችን እሰብክ ዘንድ ለተማረኩትም ነፃነትን የእግዚአብሔርንም ዓመት የተመረጠ እለው ዘንድ ላከኝ። ጌታችንም እንዲህ አለ ከእናንተ ጋራ ሳለሁ ይህን ነገርኳችሁ። ነገር ግን አብ በስሜ የሚልከው አጽናኝ መንፈስ ቅዱስ እርሱ ሁሉን ያስተምራችኋል እኔም የነገርኳችሁን ሁሉ ያሳስባችኋል። እኔ ሰላምን እተውላችኋለሁ የአባቴንም ሰላም እሰጣችኋለሁ። እኔ የምሰጣችሁ ዓለም እንደሚሰጠው ስጦታ አይደለም።ልባችሁ አይታወክ አትፍሩም ።
እኔ እሔዳለሁ ወደእናንተም ተመልሼ እመጣለሁ እንዳልኋችሁ ሰማችሁ። ሁለተኛ ደግሞ እንዲህ አለ እኔ ከአብ ዘንድ የምልክላችሁ አጽናኝ እርሱም ከአብ የሚገኝ የዕውነት መንፈስ በመጣ ጊዜ እርሱ ስለእኔ ይመሰክራል። እናንተም ደግሞ ከመጀመሪያ ከእኔ ጋራ ኖራችኋልና ምስክሮቼ ናችሁ።
እንዳትሰነካከሉ ይህን ነግሬአችኋለሁ ከምኵራባቸው ያወጡአችኋል ከዚህም በላይ ደግሞ የሚገድላችሁ ሁሉ ለእግዚአብሔር መሥዋዕት እንደሚያቀርብ የሚመስልበት ጊዜ ይመጣል። እኔም ዕውነት እነግራችኋለሁ እኔ ብሔድ ይሻላችኋል እኔ ካልሔድኩ ግን አጽናኙ መንፈስ ቅዱስ ወደ እናንተ አይመጣምና። ከሔድኩ ግን እርሱን እልክላችኋለሁ ።
እርሱም መጥቶ ስለ ኃጢአት ስለ ጽድቅም ስለ ፍርድም ዓለምን ይውቅሰዋል። ስለ ኃጢአት በእኔ አላመኑምና ስለ ጽድቅም ወደ አብ እሔዳለሁና እንግዲህም አታዩኝምና ስለ ፍርድም የዚህ ዓለም ገዢ ይፈረድበታልና አላቸው።
የምነግራችሁም ገና ብዙ አለኝ ነገር ግን ዛሬ ልትሸከሙት አትችሉም እርሱ የዕውነት መንፈስ በመጣ ጊዜ ወደ እውነት ሁሉ ይመራችኋል የሚሰማውን ሁሉ ይናገራል እንጂ ከራሱ አይነግርምና የሚመጣውንም ይነግራችኋል።
እርሱ እኔን ይገልጣል ከእኔም ገንዘብ አድርጎ ይነግራችኋልና ለአባቴ ያለው ሁሉ የኔ ገንዘብ ነውና ስለዚህ ከእኔ ገንዘብ አድርጎ ይነግራችኋል አልኳችሁ። ጥቂት ጊዜ አለ አታዩኝም ደግሞም ጥቂት ጊዜ አለ ታዩኛላችሁ ወደ አብ እሔዳለሁና ።
ደቀ መዛሙርቱም እርስ በርሳቸው እንዲህ ተባባሉ ምንድነው ይህ ነገር ጥቂት ጊዜ አለ አታዩኝም ደግሞም ጥቂት ጊዜ አለ ታዩኛላችሁ ወደ አብ እሔዳለሁና የሚለን። ጌታ ኢየሱስም ሊጠይቁት እንደሚሹ ዐወቀባቸው እንዲህም አላቸው ስለዚህ ነገር እርስ በርሳችሁ ትመራመራላችሁን ጥቂት ጊዜ አለ አታዩኝም ደግሞም ጥቂት ጊዜ አለ ታዩኛላችሁ ስለአልኳችሁ።
እውነት እውነት እላችኋለሁ እናንተ እንደምታዝኑ እንደምታለቅሱ ዓለም ደስ ይለዋል እናንተ ግን ታዝናላችሁ ነገር ግን ኀዘናችሁ ደስታ ይሆናችኋል። ሰው የሆነበትንም ሥራ በፈጸመ ጊዜ ሒዱና አሕዛብን ሁሉ አስተምሩ። ስታጠምቋቸውም በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ በሉ። ያዘዝኳችሁን ሁሉ እንዲጠብቁ አስተምሩአቸው እኔም እስከ ዓለም ፍጻሜ በዘመኑ ሁሉ ከእናንተ ጋር እኖራለሁ አላቸው።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
አባ ገዐርጊ ገዳማዊ
በዚህችም ዕለት የአባ አብርሃም ጓደኛ የከበረ አባ ገዐርጊ አረፈ። ይህም ቅዱስ የክርስቲያን ወገን ነው ወላጆቹ ደጎች ጻድቃን ናቸው። በአደገም ጊዜ የወላጆቹን ከብቶች የሚጠብቅ እረኛ ሆነ። ሁል ጊዜም የምንኵስና ልብስ ይለብስ ዘንድ በልቡ ይመኝ ነበር።
ዐሥራ አራት ዓመትም በሆነው ጊዜ የእግዚአብሔር ጸጋ አነሣሳችው በጎቹንም ትቶ ወደ አስቄጥስ ገዳም ሔደ። እየተጓዘም ሳለ ከሩቅ የብርሃን ምሰሶ አየ ወደ ወንዝ እስከ ደረሰ ድረስ ወደ ርሱ ሔደ ከዚህም በኋላ ያ የብርሃን ምሰሶ ከእርሱ ተሰወረ።
ያንንም ወንዝ በተሻገረ ጊዜ በሽማግሌ አምሳል ሰይጣን ተገለጠለትና ልጄ ሆይ ዕወቅ ስለ አንተ ልብሱን ቀዶ አባትህን አየሁት እርሱም ያዝናል ያለቅሳል ተመልሰህ የአባትህን ልብ ልትአጽናና ይገባሃል። የዱር አውሬ ነጥቆ የበላህ መስሎታልና አለው።
አባ ገዐርጊም ደንግጦ አንድ ሰዓት ያህል ቆመ ከዚህም በኋላ የከበረ ወንጌል ከእኔ ይልቅ አባቱንና እናቱን የሚወድ ለእኔ ሊሆን አይገባውም ደቀ መዝሙሬም ሊሆን አይችልም ብሏል ብሎ አሰበ።
ይህንንም በአለ ጊዜ ሰይጣን እንደ ጢስ ሆኖ ተበተነ።አባ ገዐርጊም ሰይጣን እንደ ሆነ አወቀ በዚያን ጊዜም ያ የብርሃን ምሰሶ ደግሞ ተገለጠለት የእግዚአብሔርም መልአክ በመነኵሴ አምሳል አብሮት ተጓዘ ቅዱሱም መልአኩን ተከተለው እርሱም ከአባ አርዮን ገዳም አደረሰው። አባ ገዐርጊም ከአንድ ጻድቅ ሰው መነኵሴ ጋራ በዚያ ዐሥራ አራት ዓመት ወጥ ሳይቀምስ ወይን ሳይጠጣ የአትክልት ፍሬም ቢሆን በዚህ በዐሥራ አራት ዓመት ያህል ከሚቀመጥ በቀር አልተኛም።
ተጋድሎውንም በጨመረ ጊዜ የእግዚአብሔር መልአክ ተገለጠለትና እንዲህ አለው ሥጋህ እንዳይደክም በመካከለኛ ገድል ተጋደል ብሎሃል ጌታ። ከዚህም በኋላ ሊሠራው የሚገባውን ሥርዓት ሠራለት። ሁል ጊዜም እስከሚመሽ እንዲጾም ትንሽም እንጀራን እንዲበላ ከአራት ሰዓት እስከ መንፈቀ ሌሊት ስለ ሥጋው ዕረፍት እንዲተኛ በቀረው ሌሊት እስቲነጋ ተግቶ እንዲጸልይ።
በዚህም ተጋድሎ ብዙ ዘመናት እየተጋደለ በኖረ ጊዜ በበረሀ ውስጥ ብቻውን ሊኖር ወዶ በጫካ ውስጥ እየተመላለሰ ሁለት ዓመት ኖረ። ከዚህም በኋላ ጌታ ተገልጾለት ወደ ቦታው እንዲመለስ አዘዘው። ያን ጊዜም አምላካዊት ኃይል ከከበሩ መክሲሞስና ደማቴዎስ ገዳም አደረሰችው እርሷም ለደብሩ አቅራቢያ ናት።
ወደ ደብሩም በተመለሰ ጊዜ በዚያን ወቅት አብርሃም ከዓለም ወደዚያ ገዳም መጥቶ ሁለቱም ተገናኙና በአንድነት ተስማምተው የአስቄጥስ ገዳም አበ ምኔት ወደ ሆነ ወደ አባ ዮሐንስ ደረሱ። እርሱም ቦታ ሰጥቷቸው በውስጡ ኖሩ ያ ቦታም እስከ ዛሬ ታውቆ ይኖራል ።
ያቺም ዋሻ በግቢግ ትባላለች የክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ዐለት የሆነ ጣሪያዋን ሠንጥቆ ወደ እነርሱ የወረዳበት ናት። እነርሱም ሰገዱለት ሰላምታም ሰጥቷቸው አጽናንቷቸው ከእርሳቸው ዘንድ ዐረገ።በዚያችም ጌታችን በወረደበት መስኮት ብርሃንን አዩ እስከ ዛሬም የተከፈተች ሁና ትኖራለች።
እሊህ ቅድሳንም ለመነኰሳት የሚሆን ብዙ ድርሳናትንና ብዙ ተግሣጻትን ደረሱ። ለአባቶቹ የሚታዘዘውንና የሚገዛውን አመሰገኑት። ከዚህም በኋላ አባ አብርሃም ጥር ሁለት ቀን አረፈ።ከእርሱ በኋላም የከበረ አባ ገዐርጊ በዚች በግንቦት ወር በዐሥራ ስምንት ቀን አረፈ። መላ ዕድሜውም ሰባ ሁለት ዓመት ሆነ።በዓለም ዐሥራ አራት ዓመት በምንኩስና ኃምሳ ስምንት ዓመት ነው።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
ሰማዕት ሲኖዳ
በዚችም ዕለት የሰማዕት ሲኖዳ መታሰቢያው ነው በረከቱ፡ ሰማዕቱ አቡነ ሲኖዳ ሀገራቸው ግብፅ ብሕንሳ ነው፡፡ መጽሐፍ ሰማዕትም ጻድቅም ይላቸዋል፡፡ ሽኖዳ እየተባሉም የሚጠሩ ሲሆን የአቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ የአክስት ልጅ ናቸው፡፡ ሙሉ ዕድሜያቸውን በገዳም ነው የኖሩት፡፡ በማርቆስ መንበር ላይ ተሹመው በፓትርያርክነት እያገለገሉ እያለ በዘመናቸው ከሃዲው ንጉሥ መክስምያኖስ ነግሦ ስለነበር ክርስቶስን በማመናቸው እጅግ ብዙ አሠቃይቷቸዋል፡፡
ከሃዲው ንጉሥ መክስምያኖስ ወደ እርሱ እንዲመጡ ካደረገ በኋላ በእርሱ ጣዖት እንዲያምኑ ጠየቃቸው፡፡ አቡነ ሲኖዳም በክርስቶስ እንደሚያምኑ ሲነግሩት በምድር ላይ ደማቸው እንደ ውኃ እስኪፈስ ድረስ ጽኑ ግርፋትን አስገረፋቸው፣ ዐይናቸውም ሊወጣ ደረሰ፡፡ በእሥር ቤትም ከጣሏቸው በኋላ የታዘዘ መልአክ መጥቶ ከቁስላቸው ፈውሶ አበረታቸውና ገና እንደሚጋደሉ ነገራቸው፡፡ ንጉሡም ‹‹ሞቶ እንደሆን እዩት›› ብሎ ወታደሮቹን ቢልክም ፍጹም ጤነኛ መሆናቸውን ነገሩት፡፡ ልብሳቸውንም አስወልቆ አይቶ ካረጋገጠ በኋላ ‹‹ታላቅ ሥራይ ነው›› በማለት ዘቅዝቀው እንዲሰቅሏቸውና ከሥር እሳት እንዲያነዱባቸው አዘዘ፡፡ ይህንንም በአባታችን ላይ አደረጉባቸው፡፡ አሁንም ምንም ዓይነት ሥቃይ እንዳልገደላቸው ባየ ጊዜ በብዙ ካሠቃያቸው በኋላ መጋቢት 14 ቀን አንገታቸውን በሰይፍ አስቆርጦታል፡፡
ለጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስም ከቸር አባቱ አዳኝና ሕይወት ከሆነ ቅዱስ መንፈሱ ጋር ጌትነት ክብር ምስጋና ይሁን። እኛንም በቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን።
ስንክሳር ዘወርኀ ግንቦት

No comments:

Post a Comment

Post Bottom Ad

Pages