ስንክሳር ዘወርኀ ጷጉሜ 4 - አትሮንስ ሚዲያ - Atrons Media

አትሮንስ ሚዲያ - Atrons Media

ስብኩ ወንጌለ ለኩሉ ፍጥረት ማቴ 16፤15


በቅርብ የተጻፉ

Post Top Ad

Friday, February 23, 2024

ስንክሳር ዘወርኀ ጷጉሜ 4

 በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን።



አባ ባይሞን /ጴሜን/
👉 ይህ ቅዱስ አባት የ4ኛው መቶ ክ/ዘ የቤተ ክርስቲያን ፍሬ ሲሆን ተሰምተው በማይጠገቡ መንፈሳዊ ቃላቱ (ምክሮቹ)ና በቅድስና ሕይወቱ ይታወቃል:: ጥንተ ነገሩስ እንደ ምን ነው ቢሉ:-
በተጠቀሰው ዘመን በምድረ ግብጽ የምትኖር አንዲት ደግ ሴት ነበረች:: አምላክ በፈቀደው ጋብቻ ውስጥ ገብታ ሰባት ወንዶች ልጆችን አፈራች:: ሰባቱም ወንድማማቾች ገና ሕፃን እያሉ አባት በመሞቱ እናት ፈተና ውስጥ ገባች::
ነገር ግን ብርቱ ሴት ነበረችና በወዟ ደክማ አሳደገቻቸው:: ሥጋዊ ማሳደጉስ ብዙም አይደንቅም:: ምክንያቱም ሁሉም እናቶች ይህንን ያደርጉታል ተብሎ ይታመናልና:: የዚህች እናት የሚገርመው ግን ሁሉንም ንጹሐን: የተባረኩ: የክርስቶስ ወዳጆች: የቤተ ክርስቲያንም አለኝታዎች እንዲሆኑ አድርጋ ማሳደጓ ነው::
እነዚህ ሰባቱ ወንድማማቾች:-
1.አብርሃም
2.ያዕቆብ
3.ዮሴፍ
4.ኢዮብ
5.ዮሐንስ
6.ላስልዮስ እና
7.ባይሞን (ጴሜን) ይባላሉ:: ለእነዚህም ዮሐንስ በኩር ሲሆን ባይሞን መቁረጫ ነው::
ሰባቱም ወጣት በሆኑ ጊዜ ወገባቸውን ታጥቀው እናታቸውን ያገለግሉ: ለፈጣሪያቸው ይገዙ ያዙ:: ያየ ሁሉ "ከዓይን ያውጣችሁ::" የሚላቸው: ቡሩካንም ሆኑ:: አንድ ቀን ግን መንፈስ ቅዱስ በሰባቱ ልብ ውስጥ አንድ ቅን ሃሳብን አመጣ:: ሁሉም እንደ አንድ ልብ መካሪ: እንደ አንድ ቃል ተናጋሪ ስለ ምናኔ አወሱ::
ይህንን ዓለም ከነ ኮተቱ ይተውት ዘንድ መርጠዋልና ወደ በርሃ ለመሔድ ተስማሙ:: እናታቸው ምን መንፈሳዊ ብትሆን የትኛዋም እናት ሁሉን ልጆቿን በአንዴ ማጣትን አትፈልግምና አላማከሯትም:: ይልቁኑ እነርሱ ከሔዱ በኋላ እንዳትቸገር የምትታገዝበትን መንገድ አዘጋጅተውላት ተሰወሩ::
ሰባት ልጆቿን በአንዴ ያጣችው እናት ብቻ አይደለችም: ሁሉም አዘነ:: ተፈለጉ: ግን አየኋቸው የሚል ሰው አልተገኘም:: ሰባቱም ቅዱሳን ከቤታቸው እንደ ወጡ ወደ ገዳም ሔደው አንዲት በዓት ተቀበሉ:: ሰባቱም የሚጸልዩ በጋራ: የሚሠሩ: የሚመገቡ: የሚውሉ: የሚተኙም በጋራ ነው::
በአገልግሎታቸውም ሆነ በፍቅራቸው አበውን ደስ አሰኙ:: "እምኩሉ የዓቢ ተፋቅሮ - እርስ በእርስ መዋደድ ከሁሉ ይበልጣል::" እንዲሉ አበው:: ከዘመናት ተጋድሎ በኋላ ግን ዝናቸው ከገዳሙ አልፎ በከተሞች ተሰማ:: ይህንን የሰማችው እናታቸው የእርሷ ልጆች መሆናቸውን በማወቋ ፈጥና ወደ ገዳሙ ገሰገሰች::
"ልያችሁ ልጆቼ?" ስትልም ላከችባቸው:: እነሱ ግን "እናታችን በመንግስተ ሰማያት እንድታይን በዚህ ይቅርብሽ::" አሏት:: ምክንያቱም ሰባቱም የሴትን ፊት ላያዩ ቃል ገብተው ነበርና:: ይህ ለአንድ እናት ከባድ ቢሆንም እርሷ ግን ተረዳቻቸው:: ፈጥናም ወደ ቤቷ ተመለሰች::
ከኮከብ ኮከብ ይበልጣልና (1ቆሮ. 15:41) ከሰባቱ ቅዱሳን ደግሞ ትንሹ አባ ባይሞን የተለየ አባት ሆነ:: ከንጽሕናው: ቅድስናና ትጋቱ ባሻገር ከአንደበቱ የሚወጡ ቃላት ሕይወትነት ያላቸው ሆኑ:: በዘመኑም ከሕፃን እስከ አዋቂ ድረስ ብዙዎች ከመንፈሳዊ ቃላቱ ተጠቅመዋል::
እነዚህ ምክሮቹ ዛሬ ድረስ ለምዕመናንም ሆነ ለመነኮሳት ጣፋጮች ናቸው::
እልፍ አእላፍ ከሆኑ ምክሮቹ እስኪ አንድ አምስቱን እንጥቀስ:-
1."ባልንጀራህ በወደቀ ጊዜ በፍጹም ተስፋ አትቁረጥበት:: ይልቅስ አንቃው: አበረታታው: ሸክሙንም አቅልለት እንጂ::"
2."ለጥሩ ባልንጀራህ የምታደርገውን ደግነት ለክፉው በእጥፍ አድርግለት:: መድኃኒትን የሚሻ የታመመ ነውና:: አልያ ግን ለበጐው ያደረከው ከንቱ ነው::"
3."ባልንጀራህ በበደለ ጊዜ አትናቀው:: ያንተ ተራ በደረሰ ጊዜ ጌታህ ይንቅሃልና::"
4."የማንንም ኃጢአት አትግለጥ (አታውራ):: ካላረፍክ ጌታ ያንተኑ ይገልጥብሃልና::"
5."አንደበትህ የተናገረውን ሁሉ ለመሥራት ታገል:: አልያ ውሸታም ትሆናለህ::"
ሰባቱ ቅዱሳን ወንድማማቾች ለብዙ ዓመታት በፍቅርና በተጋድሎ ኑረው በዚህች ቀን ዐርፈዋል::
✍† ቅዱስ ሊባርዮስ ሊቅ †✍
† ሊቁ ተወልዶ ያደገው በአውሮጳ ሮም ውስጥ ሲሆን የታላቁ ሊቅ ቅዱስ አትናቴዎስ ባልንጀራም ነበር:: በቀደመ ሕይወቱ ምሑርና ገዳማዊ በመሆኑ ሊቃውንት የሮም ፓትርያርክ አድርገው ሾሙት:: ዘመኑ አርዮሳውያን የሰለጠኑበት በመሆኑ ምዕመናንን ከተኩላ ለመጠበቅ እንቅልፍን አልተኛም::
የወቅቱ ንጉሥ ታናሹ ቆስጠንጢኖስ እምነቱ አርዮሳዊ በመሆኑ ቅዱሱን ያሰቃየው: ያሳድደውም ነበር:: ለበርካታ ዓመታትም ከመናፍቃንና ከአጋዥ ነገሥታት ጋር ስለ ሃይማኖቱ ተዋግቶ በዚህች ዕለት ዐርፏል::
† የአባቶቻችን አምላክ መፋቀራቸውንና ማስተዋላቸውን ያድለን:: ከበረከታቸውም ያሳትፈን::
ጳጉሜን 4 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት
1.ቅዱስ አባ ባይሞን (ጴሜን)
2.ስድስቱ ወንድሞቹ (አብርሃም: ያዕቆብ: ዮሴፍ: ኢዮብ: ላስልዮስና ዮሐንስ)
3.ቅዱስ ሊባርዮስ ሊቅ
ወርኀዊ በዓላት (የለም)
"ለእውነት እየታዘዛችሁ: ግብዝነት ለሌለበት ለወንድማማች መዋደድ ነፍሳችሁን አንጽታችሁ እርስ በእርሳችሁ ከልባችሁ አጥብቃችሁ ተዋደዱ:: ዳግመኛ የተወለዳችሁት ከሚጠፋ ዘር አይደለም:: በሕያውና ለዘላለም በሚኖር በእግዚአብሔር ቃል: ከማይጠፋ ዘር ነው እንጂ::" (፩ጴጥ. ፩፥፳፪)
ወስብሐት ለእግዚአብሔር
ስንክሳር ዘወርኀ ጷጉሜ

No comments:

Post a Comment

Post Bottom Ad

Pages