መስከረም ፭ የአባታችን የአቡነ አሮን ዘመቄት በዓለ ዕረፍት በዓል - አትሮንስ ሚዲያ - Atrons Media

አትሮንስ ሚዲያ - Atrons Media

ስብኩ ወንጌለ ለኩሉ ፍጥረት ማቴ 16፤15


በቅርብ የተጻፉ

Post Top Ad

Saturday, October 2, 2021

መስከረም ፭ የአባታችን የአቡነ አሮን ዘመቄት በዓለ ዕረፍት በዓል

አቡነ አሮን ዘመቄት _______________ መስከረም ፭ የአባታችን የአቡነ አሮን ዘመቄት በዓለ ዕረፍት በዓል ነው፡፡የመቄቱ አቡነ አሮን ወላጅ አባታቸው የላስታው ጻድቁ ንጉሥ ዐፄ ገብረ መስቀል ነው፡፡ የላስታ ነገሥታት የዘር ሐረጋቸው ከንጉሥ ሰለሞን ዘር ሲያያዝ የመጣ ነው፡፡ ከ ፲ኛው - ፲፫ኛው መቶ ክፍለ ዘመን (920-1253) ዓ/ም ገደማ በላስታ ቡግና ምድር የነገሡ የላስታ ቡግና ተወላጅ የሆኑ የኢትያጵያ ቅዱሳን ነገሥታት የንግሥናቸው መጠሪ የዛጉዌ ሥርወ መን በመባል ይታወቃል፡፡ የንጉሥ ሰለሞን ዘር የሆነው መራ ክርስቶስ 3 ልጆችን ወለደ፡፡ እነሱም ጠንጠወድም፤ ግርማ ስዩምና ዣን ስዩም ናቸው፡፡ ጠንደውድም ገብረ መስቀልን ወለደ፤ ገቡረ መስቀልም አቡነ አሮን ወለደ፤ ግርማ ስዩም ይምርሐነ ክርስቶስን ወለደ፤ ዣን ስዩም ደግሞ ገብረ ማርያምንና ላሊበላን ወለደ፡፡ ገብረ ማርያም ነዓኩቶ ለአብን ወለደ፡፡ አነዚህ ቅዱሳን ነገሥታት እንደ መልከጸዴቅ ክህነትነን ከንግሥና ቅድስናን ከንጽሕና ጋር አንድ አድርገው በመያዝ እግዚአብሔርንም ሕዝብንም በቅድስናና በንጽሕና አገልግለው አልፈዋል፡፡ ወደ ቀደመ ነገራችን እንመለስ አቡነ አሮን በአምስት ዓመታቸው ሙት አስነስተዋል፡፡ በአስራ ስድስት ዓመታቸው መንነው ዋልድባ ገዳም ገብተዋል፡፡ በሀገራችን እየተዘዋወሩ ወንጌልን ሲሰብኩ የሸዋው ንጉሥ አንኮበር ድረስ ጠርተዋቸው ሄደው ሲመለሱ አዋሽ ወንዝ ሞልቶባቸው አገኙት፡፡ ሲሻገሩ ዳዊታቸውን ወሰደባቸው፡፡ አሁንም በድጋሚ ሌላ ጊዜ በሸዋው ንጉሥ አንኮበር ድረስ ተጠርተው ከ7 ዓመት በኃላ ተመልሰው በአዋሽ ወንዝ ሲሄዱ መልአክ መጣና"መቋሚያህን ወደ ወንዙ ላክ አላቸው፡፡ መቋሚያቸውንም ቢልኩ ዳዊታቸውን ይዘው አወጡ፡፡ ዳዊቱም በውኃው አልራሰም ነበር፡፡ ይልቁንም አቧራውን አራግፈው ፈጣሪያቸውን አመሥግነው ዳዊታቸውን ይዘው ሄደዋል፡፡ ያ ዳዊታቸው ዛሬም ድረስ በጋይንት አብርጎት ቅዱስ ሚካኤል ይገኛል። ሰሜን ወሎ መቄት ወረዳ የሚገኘው እጅግ አስደናቂ ገዳማቸው ፍልፍል ዋሻ ሲሆን ጣራው ክፍት ነው፡፡ ክፍት በሆነው ጣራ በኩል ፀሐይ ሲገባ ሰለሚያቃጥል ጥላ ይይዛሉ ነገር ግን የጻድቁ ግዝት ስላለበት ዝናብ ወደ መቅደሱ ፈጽሞ አይገባም፡፡ አቡነ አሮን በአንቺም ሜዳ በሚባል ቦታ ፀሐይንም ገዝተው አቁመዋታል፡፡ከታች ጋይንት ተነሥተው መንገድ ሲሄዱ በሰንበት ቀን በሬ ጠምዶ ሲያርስ የነበረን ገበሬ ለምን በሰንበት ታርሳለህ ቢሉት ምቀኛ መነኩሴ ብሎ በጅራፉ ቢገርፋቸው በሬዎቹ ግን ፈጽሞ አልንቀሳቀስ ብለው ቆመዋል፡፡በዚህ የተናደደው ገበሬም አቡነ አሮንን መሬት ላይ ጥሎ ገረፋቸው፡፡ እሳቸው ተነሥተው ሲሄዱ ዛፎች ተነቅለው እየተከተሏቸው ቃል አውጥተው በሰው አንደበት አመስግነዋቸዋል፡፡ የህንጻው አይነት ስቁረት ሁለት አምዶች አስራ አራት መስኮት ሰባት አንደኛው ስቁርት ዝናብ የማይገባበት ፀሐይና ጨረቃ እንዲሁም ከዋክብት ብርሃናቸውን የሚሰጡበት ለማየት የሚያስደንቁ ሁለተኛው ብርሃናትም ዝናባትንም ይፈራራቁበታል፡፡ የወረደው ወይም ዝናብም ወዴት እንደሚሄድ ወይም የት እንደሚጠራቀም አይታወቅም፡፡ ይህንን እነደዚህ አድርገው አንፀው ወደ ፈጣሪያቸው አመለከቱ፡፡ ክብር ምስጋና ይግባውና ጌታችን መላእክት አስከትሎ ወርዶ ቤተ መቅደሱን ባርኮ ቃል ኪዳኑን አፅንቶ አስከ ምፃት ድረስ እንዲሁ እያበራች ትኑር ብሎ አርጓል፡፡ አባ አሮን መንክራዊም ቃል ኪዳናቸውን ተቀብለው ትንሽ ጊዜ ከቆዩ በኃላ ወደ በኬ ምድር ለቡራኬ ወጡ መላአክ ጊዜ እረፍታቸው እንደቀረቀበ ነገራቸው ያን ጊዜ ደስ ብሏቸው ወደ ገዳማቸው ሲመለሱ የመጀመሪያይቱ የእሳት ጥላሻት ተሰማያቸው ጎዳና በር እናላቲ የሚባሉ አቀበትና ቁልቁለት አሉ በነዚህ መንገዶች ለመጓዝ በጣም ደከሙና አየተደገፋ ዘለቁ፡፡ ከበሩ ሲደርሱ አሳረፏቸው ከዚያ በኃላ አንደበታቸው በረታ ልሳናቸው ፈታ ማኅበረ መነኮሳቱን አዕናኑ ቃል ኪዳናቸው አበረከቱ፡፡ በገዳሙ ውስጥ የምንኩስና ክብር የተቀበለ ከቤተክርስቲያኑ ስጋ ወደሙ የተቀበለ እጣን ጧፍ ማንኛውም በጎ አድራጎት ለቤተ መቅደሱ የተራዳ በተለይም ይህችን ቦታ የረገጠ ገድልህን የሰማ ያሰማ የጻፈ ያፃፈ እሰከ አስራ አምስት ተውልድ እምርልሃለሁ ብሎ የሰጣቸውን ተስፋ ተናግረው ወደ ገዳሙ ሴት እንዳያልፍ በለው ካሰናበቱ በኃላ ጌታችን መላእክት አስከትሎ የብፁአ አባታችን ነፍስ ለማሳረግ ሲወርድ ታላቅ ግርማ ሆነ፡፡ ከበሩ አንዲት ወይራ ነበረች ወይራይቱም ለፈጣሪዋ ሰገደች፡፡ እሰከአሁን ደርቃ ተጋድማ የወንድና የሴት መለያ ሁና ትታያለች በዚያ ግርማ መላእክት በማህሌት መስከረም 5ቀን ነፍሳቸውን ከስጋቸው ለይተው አሳረጓት ፡፡ስለዚህ መስከረም አምስት የዕረፍታቸው ቀናቸው ነው በረከታቸው ከሁላችን ጋር ይሁን፡፡ የጻድቁ ታላላቅ ገድላት እንደነ ሙሴና አሮን በአምደ ደመና ከመሬት መሰወር፣ እንደ ዳንኤል አናብስት ማሰገድን፣ እንደ ሙሴ ከድንጋይ ላይ ውሃ ማፍለቅ፣ እንደ ኤልሳ ባህርን ሁለት ጊዜ መሻገር፣ እንደ እያሱ ፀሐይ ማቆም፣ እንደ ሐዋርያት ድውይ መፈወስ፡፡ ከቡዙ በጥቂቱ ነው፣ባህሩን የከፈሉበት ውሃ ያፈለቁበት ፀሐይ ያቆሙበት ዳዊታቸውን ያወጡበት በትረ መስቀላቸው ልዩና በቁመቱ በአራት ማዕዘን የተቀረፀ ሲሆን እስካሁን በገዳሙ ያለና ብዙ በሽተኞችን በመፈወስ ላይ ይገኛል፡፡ ህንፃውን ያነፁበትና ጉድብ የተባለው መጥረቢያ ቅዱስ ኡራኤል የሰጣቸው ሶስት መልክ ያለው ይህም እየታጠበ ብዙ ድውያንን በመፈወስ ላይ ይገኛል፡፡ የጻድቁ አባታችን የአቡነ አሮን ምልጃቸው ከሁላችን ጋር ይሁን፡፡ ምንጭ:- መዝገበ ቅዱሳንእና ገድለ አቡነ አሮን

No comments:

Post a Comment

Post Bottom Ad

Pages