ስንክሳር_ዘወርኀ_ጥቅምት 2 - አትሮንስ ሚዲያ - Atrons Media

አትሮንስ ሚዲያ - Atrons Media

ስብኩ ወንጌለ ለኩሉ ፍጥረት ማቴ 16፤15


በቅርብ የተጻፉ

Post Top Ad

Tuesday, October 11, 2022

ስንክሳር_ዘወርኀ_ጥቅምት 2

 

አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም
ጥቅምት ሁለት በዚች ቀን የአንጾኪያ ሊቀ ጳጳሳት #ቅዱስ_ሳዊሮስ ወደ ግብጽ አገር ተሰዶ የመጣበት፣ #የቅዱስ_አባ_ሕርያቆስ የልደቱና ዕረፍቱ መታሰቢያ ናት፣ የፈጠጋሩ #ቅዱስ_አቡነ_ማትያስ ዕረፍታቸው ነው፡።


ጥቅምት ሁለት በዚች ቀን የአንጾኪያ ሊቀ ጳጳሳት ቅዱስ ሳዊሮስ ወደ ግብጽ አገር ተሰዶ መጣ ።
ይህም የሆነው በመናፍቁ ንጉሥ በዮስጥያኖስ ዘመን ነው እርሱም ንጉሡ በኬልቄዶን ሃይማኖት የሚያምን ነው ሚስቱ ንግሥት ግን ሃይማኖቷ የቀና ነው ቅዱስ አባ ሳዊሮስን ትወደዋለች ታከብረዋለችም ንጉሡም በሥውር ሊገድለው ይሻዋል።
ቅዱስ አባ ሳዊሮስንም በሥውር ይገድለው ዘንድ ንጉሥ እንደሚሻው ንግሥት በአወቀች ጊዜ ከአንጾኪያ አገር እንዲወጣና ነፍሱን እንዲአድን ወደ አባ ሳዊሮስ ላከች። እርሱ ግን መሸሽ አልፈለገም ለንግሥትም እንዲህ አላት እኔ ክብር ይግባውና ስለጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ለሞት የተዘጋጀሁ ነኝ ንግሥቲቱም ብዙዎች ምእመናንም አብዝተው በለመኑት ጊዜ ከሀገር ወጣ ከእርሱም ጋር ከምእመናን አብረውት ወደ ግብጽ አገር የተሰደዱ አሉ።
ንጉሡም በፈለገው ጊዜ አላገኘውም ፈልገውም ወደርሱ ያመጡት ዘንድ ወታደሮቹን ላከ ክብር ይግባውና ጌታችን ስለ ሠወረው እነርሱም በቅርባቸው ሁኖ በመካከላቸው ሲጓዝ አላገኙትም። በአንድ ቦታም አብሮአቸው ሲያድር እርሱ እያያቸው እነዚያ የንጉሥ ጭፍሮች አያዩትም እርሱንም አጥተው ተመለሱ።
ወደ ግብጽ አገርም በደረሰ ጊዜ ከቦታ ወደቦታ ከደብር ወደ ደብር በሥውር የሚዘዋወር ሆነ እግዚአብሔርም በእጆቹ ላይ ታላላቅ የሆኑ ድንቆች ተአምራትን አደረገ።
በአንዲት ቀንም ወደ አስቄጥስ ገዳም ደረሰ በመጻተኛ መነኲሴ አምሳልም ወደ አባ መቃርስ ቤተ ክርስቲያንም ገባ በዚያንም ጊዜ ቄሱ ዕጣንና ቁርባንን ሊአሳርግ ጀመረ እንደ ሥርዓቱም እየዞረ ዐጠነ። የሐዋርያትንም መጻሕፍት የጻፉአቸውን መልእክቶች የከበረ ወንጌልንም ከአነበቡ በኋላ እጆቹን ታጥቦ ማኅፈዱን በገለጠው ጊዜ በጻሕሉ ውስጥ የቊርባኑን ኅብስት አላገኘውም ደንግጦም አለቀሰ።
ከዚህም በኋላ ወደ ሕዝቡ ተመልሶ እንዲህ አላቸው ወንድሞቼ እነሆ የቊርባኑ ኅብስት ተሠውሮ በጻሕሉ ውስጥ አላገኘሁትምና ይህ የሆነ በእኔ ኃጢአት ወይም በእናንተ ኃጢአት እንደሆነ አላወቅሁም።
በዚያንም ጊዜ የእግዚአብሔር መልአክ ተገልጦለት እንዲህ አለው ይህ የሆነ በኃጢአትህ ወይም በሕዝብ ኃጢአት አይደለም ሊቀ ጳጳሳት አባ ሳዊሮስ እያለ መሥዋዕትን ለማሳረግ በመድፈርህ ነው እንጂ ቄሱም መልአኩን ጌታዬ ሊቀ ጳጳሳት መኖሩን አላወቅሁም አለው አባ ሳዊሮስም ወደ ቆመበት ቦታ አመለከተው።
ቄሱም ወደ አባ ሳዊሮስ ሒዶ ከእግሩ በታች ሰገደ ቡራኬም ከእርሱ ተቀበለ። ሊቀ ጳጳሳት አባ ሳዊሮስም የጀመረውን የቅዳሴውን ሥርዓት እንዲፈጽም ቄሱን አዘዘው። እርሱንም በታላቅ ክብር ወደ ቤተ መቅደስ አስገቡት ከዚህም በኋላ ቄሱ ወደ መሠዊያው በወጣ ጊዜ የቁርባኑን ኅብስት በጻሕሉ ውስጥ አገኘው ካህናቱና ሕዝቡም ሁሉ እግዚአብሔርን አመሰገኑት።
የቁርባኑንም ሥርዓት ከተፈጸመ በኋላ ካህናቱና ሕዝቡም ሁሉ ከሊቀ ጳጰሳት አባ ሳዊሮስ ቡራኬ ተቀበሉ። ከዚያም ወጥቶ ወደ ሀገረ ስሐ ሔደ ስሙ ዶርታዎስ ከሚባል እግዚአብሔርን ከሚወድ ባለ ጸጋ ሰው ደርሶ ከእርሱ ዘንድ ተቀመጠ። ምእመናንንም እያስተማራቸውና በቀናች ሃይማኖት እያጸናቸው እስከሚአርፍባት እስከ የካቲት ወር ዐሥራ አራት ቀን ኖረ።


ክርስቲያን ሆኖ እመቤታችንን የሚወድ ሰው ሁሉ ይህንን አባት ያውቀዋል። አባ ሕርያቆስ ተወልዶ ያደገው በምድረ ግብጽ ሲሆን አካባቢው ብህንሳ (ንሒሳ) ይባላል። ይህቺ ቦታ አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስን ጨምሮ በርካታ ቅዱሳንን ያፈራች ናት።
አባ ሕርያቆስን በዚህ ዘመን ነበረ ተብሎ ትክክለኛውን ዓ/ም ለመናገር ይከብዳል። ከቤተ ክርስቲያን ትውፊት መረዳት እንደሚቻለው ግን የነበረበት ዘመን 4ኛው ወይም 5ኛው መቶ ክፍለ ዘመን እንደ ሆነ መገመት ይቻላል።
ቅዱሱ በዘመኑ የተለየ ማንነት የነበረው ሰው ነው። ገና ከልጅነቱ እመ ብርሃንን የሚወዳት በመሆኑ ቅን የዋህና ገራገር ነበረ። መቼም እመቤታችን ይወዳል ሲባል እንደ ዘመኑ በአፍ ብቻ እንዳይመስለን። ቀንና ሌሊት ለፍቅሯ የሚተጋ ማዕበለ ፍቅሯ የሚያማታው ሰው ነበር እንጂ።
የእመቤታችን ድንግል ማርያምን ስም ሲጠራ ምስጥ ብሎ ልቡናው ይሰወርበት ነበር ዘወትር የእርሷን ፍቅር ከማሰብ በቀር ሌላ ሥራ አልነበረውም። የልጅነት ጊዜው ሲያልፍም ድንግልንና ቸር ልጇን ያገለግል ዘንድ መነነ።
ዘመኑ ዘመነ ሊቃውንት እንደ መሆኑ ሁሉም ለትምሕርት ሲተጉ እርሱ ግን ለጸሎትና ለደግነት ብቻ ነበር የሚተጋው። ከትምሕርት ወገንም የሰሞን ጉዋዞችን አንዳንድ ቅዳሴያትንና የዳዊትን መዝሙር ተምሮ ነበር።
በተለይ ግን የዳዊትን መዝሙር እየጣፈጠው መላልሶ መላልሶ ያመሰግንበት ነበር። ከዳዊት መካከል ደግሞ መዝሙር 44ን ፈጽሞ ይወዳት ነበር። ይህቺ ጥቅስ የምትጀምረው "ጐስዐ ልብየ ቃለ ሠናየ" ብላ ነው። የውስጧ ምሥጢርም ስለ ድንግል ማርያምና ስለ ክርስቶስ ነው።
አባ ሕርያቆስ ይህቺን መዝሙር በቃሉ አጥንቶ? ቁሞም ተቀምጦም ተኝቶም ተነስቶም ያለ ማቁዋረጥ ይላት ነበር። እየጣፈጠችው "ልቡናየ በጐ ነገርን አወጣ" እያለ ይዘምር ነበር። በወቅቱ ታዲያ የብህንሳ ኤዺስ ቆዾስ በማረፉ ምትክ ሲያፈላልጉ መንፈስ ቅዱስ አባ ሕርያቆስን መረጠ።
ምንም አለመማሩ ቢያሰጋችቸውም 'በጸሎቱ በደግነቱ ሃገር ይጠብቃል' ብለው ሾሙት ነገር ግን ምንም በሥልጣን የበላያቸው ቢሆን ተማርን የሚሉ ሰዎች ይጠሉት ይንቁትም ነበር። እርሱ ግን እንደ ጠሉኝ ልጥላቸው እንደ ናቁኝ ልናቃቸው ሳይል በፍቅር ያገለግል ነበር።
አንድ ቀን ታዲያ መንገድ ይወጣል:: በበርሃ ብቻውን እየተራመደ "ጐሥዐ ልብየ ቃለ ሠናየ" እያለ እየዘመረ ተመሥጦ ቢመጣበት መንገድ ሳተ። እርሱ በምስጋናው ሲደሰት እግሩ ግን ከገደል ጫፍ ደርሶ ነበር። ገደሉን ልብ አላለውም ነበርና ሳይታወቀው ወደ ገደሉ ውስጥ ተወረወረ።
በዚህ ጊዜ ደንግጦ ቢመለከት እጅግ ጥልቅ በሆነ ገደል ውስጥ ራሱን አገኘው። ነገር ግን አንድም አካሉ አልተነካም። ልብሱም አልቆሸሸም። ለራሱ ተገርሞ ዙሪያ ገባውን ሲመለከት እርሱ ቁጭ ያለበት ብርሃንን የተሞላ የልብስ ዘርፍ ነበር።
"እመ ብርሃን" ብሎ ሲጮህ የሰማይና የምድር ንግሥት የሆነች እመቤታችን ከፊቱ ቁማ ታየችው። እመ አምላክን በገሃድ ቢያያት እንደ እንቦሳ ዘለለ።
የሚገርመው ደግሞ የተቀመጠበት የድንግል ማርያም የቀሚሷ ዘርፍ ነበር። እመቤታችን አነጋገረችው ባረከችው። ፍቅሯ ቢመስጠው ከሰው ሳይገናኝ ምግብም ሳይበላ እዚያው ገደሉ ውስጥ ለ1 ዓመት ያህል በተመስጦ ቆይቷል።
በሁዋላ እመ ብርሃን መጥታ ከገደሉ አውጥታ ወደ ሐገሩ መለሰችው። ከጥቂት ጊዜ በሁዋላም አንድ ፈተና ገጠመው። አንድ ቀን እመቤታችን በተወለደችበት ግንቦት 1 ቀን ቅዳሴ 'ማን ይቀድስ' ሲባል ሰዎቹ 'አባ ሕርያቆስ ይሁን' አሉ።
እርሱ ግን "እኔ አይቻለኝም እናንተ ሊቃውንት ቀድሱ" አላቸው። "አይሆንም"ብለው እርሱኑ አስገቡት። ይህንን ያደረጉት ለተንኮል ነበር። ልክ ወንጌል ተነቦ ፍሬ ቅዳሴ ሲመረጥ እርሱ "እግዚእን (የጌታ ቅዳሴን) ልቀድስ" ቢል እነርሱ "የሚቀደሰው የሊቅ ቅዳሴ ነው" አሉት።
ይህንን ያሉት እርሱ የሊቃውንቱን ቅዳሴ አያውቅምና በሰው ፊት እንዲዋረድ ነው። እንዲህም ብለው ባለመማሩ ተሳለቁበት። አባ ሕርያቆስ ግን እያዘነ ወደ መንበሩ ዞረ። ድንግልንም "እመቤቴ መናቄን መገፋቴን ተመልከች" አላት።
ወዲያው ግን ድንግል ማርያም ወርዳ ቀጸበችው (ጠራችው)። በዘርፋፋው ቀሚሷ ላይም ረቂቅ የሆነ ቅዳሴን አሳየችው። ደጉ ሰው ደስ ብሎት "ጐሥዐ ልብየ" ሲል 2ቱ እግሮቹ ከመሬት ከፍ አሉ። እርሱም "ወአነ አየድእ ቅዳሴሃ ለማርያም" ብሎ እስከ ኃዳፌ ነፍሱ ድረስ አደረሰው።
ሕዝቡና ካህናቱ በሆነው ነገር ሲደነቁ አንዳንዶቹ "ዝም ብሎ ነው የቀባጠረ" አሉ። ቅዱሱ ግን ቅዳሴ ማርያምን በብራና ጠርዞ በሕዝቡ መካከል ድውይ ፈወሰበት። እሳት ሳያቃጥለው: ውሃ ሳይደመስሰው ቀረ።
መጽሐፈ ቅዳሴው ሙትንም አስነስቷል። ከዚህች ሰዓት ጀምሮ በዘመኑ ቁጥር 1 ሊቅሙ ሆነ። ብዙ መጻሕፍትን ሲተረጉም አጠቃላይ ድርሰቶቹም እልፍ (10,000) ናቸው። ሊቁ እንዲህ በንጹሕ ተመላልሶ ዐርፏል። ይህቺ ቀን ለቅዱሱ የልደቱና ዕረፍቱ መታሰቢያ ናት።


ዳግመኛም በዚህች ቀን የፈጠጋሩ አቡነ ማትያስ ዕረፍታቸው ነው፡፡ አቡነ ተክለ ሃይማኖት የበቁ፣ የነቁ፣ ምግባር ሃይማኖታቸው እንደፀሐይ ያበራ፣ ከተጋድሏቸውም ብዛት የተነሣ ከብቃት ደረጃ ላይ የደረሱ ቅዱሳን የሆኑ ደገኛ መምህራንን በማሰልጠን በአንብሮተ እድ ዓሥራ ሁለት ዓሥራ ሁለት አድርገው እየሾሙ ለስብከተ ወንጌል በመላ አገራችን ያሰራጯቸው ነበር፡፡ እነዚህም ንቡራነ እድ ከዋክብት በመላ አገራችን የወንጌልን ብርሃን ያበሩ ቅዱሳን ናቸው፡፡
በመጀመሪያ በተክለ ሃይማኖት በአንብሮተ እድ የሾሟቸው 12ቱ ከዋክብት የወረቡ አኖሬዎስ፣ የሞረቱ ዜና ማርቆስ፣ የጽላልሹ ታዴዎስ፣ የድምቤው ገብረ ክርስቶስ፣ የወገጉ ሳሙኤል፣ የእናርያው ዮሴፍ፣ የዳሞቱ አድኃኒ፣ የወጁ ኢሳይያስ፣ የመንዝ የመራቤቴውና የወለቃው መርቆሬዎስ፣ የመሐግሉ ቀውስጦስ፣ የፈጠጋሩ ማትያስ፣ የደዋሮው ተስፋ ሕፃን፣ የእንሳሮው ዳዊት፣ የዘልዓቱ ናታን ናቸው፡፡
የፈጠጋሩ ማትያስም አቡነ ተክለ ሃይማኖት ከሾሟቸው ከ12 ንቡራነ እድ ውስጥ አንዱ ሲሆኑ ቁጥራቸውም ሁለተኛ ናቸው፡፡ ደብረ ሊባኖስን ያጥኑ የነበረው በሰኔ ወር ሲሆን በገዳሙም 13ኛው አባት በመሆን በመምህርነት አገልግለዋል፡፡ በሀገራችን ተዘዋውረው በትምህርታቸውና በተአምራታቸው ወንጌልን ሲሰብኩ ኖረው በሰላም ዐረፈዋል፡፡
ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በጸሎታቸው ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ይኑር ለዘላለሙ አሜን ።

No comments:

Post a Comment

Post Bottom Ad

Pages